>

እነ ህሊና መቼ አባታቸውን ያገኛሉ? [በዳዊት ሰለሞን]

Yeshiwassew, Habtamu, Danial

ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣን ዛሬ አነበብኳት ፡፡የጋዜጣዋ ባልደረባ የሆነው በላይ ማናዬ በቅርቡ ለእስር የተዳረገው የሰማያዊ ፓርቲ ብሄራዊ ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢ የሆነው የሺዋስ አሰፋ ቤት ተገኝተው የየሺዋስን ሁለት ህጻናት ልጆች ማግኘታቸውንና ህጻናቱም ስለ አባታቸው የሚያስቡትን እንደነገሩት ይተርካል፡፡

ህሊና የየሺዋስ ሁለተኛ ልጅ ስትሆን የ5 ዓመት ህጻን ናት፡፡‹‹አባቴ ደሴ ሄዷል››እንዳለችው በላይ ይገልጻል፡፡ጋዜጠኛው አባቷ ደሴ እንዳልሄደና ሰው እንዳይጠይቀው ተደርጎ መታሰሩን ቢያውቅም መቼ ነው ከደሴ የሚመለሰው ብላ ስትጠይቀው መልስ ፍለጋ መዋተቱን ይነግረናል፡፡የየሺዋስ የመጀመሪያ ልጅ ከህሊና በእድሜ ከፍ ያለ በመሆኑ ደሴ ሄዷል መባሉን ለመቀበል የተቸገረ ይመስላል፡፡

እንደ ህሊና ሁሉ የጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ ብቸኛ ልጅም አባቱ ‹‹አስተማሪ በመሆኑ ዝዋይ እያስተማረ እንደሆነ ለጠየቀው ሁሉ ይናገራል፡፡ፍትህ ሁልግዜም ወላጅ እናቱን ‹‹አባቴ የሚያስተምረው ትምህርት መቼ ነው የሚያበቃው››በማለት በጥያቄ ይወጥራት እንደነበር ትናገራለች፡፡Wibishet Taye
የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ልጅ የተወለደው እስር ቤት ውስጥ ነው፡፡አባቱ ለዘጠነኛ ጊዜ ለእስር ሲዳረግም ፖሊሶች እስክንድርን ከእጁ ፈልቅቀውት ሲወስዱት ተመልክቷል፡፡ፖሊሶችን በተመለከተ ቁጥር እናቱን ‹‹እኔንም ሊያስሩኝ ነው?››እያለ ይጠይቃት ነበር፡፡አሁን ናፍቆት ከአባቱ በስጋ ተለይቶ አሜሪካን አገር ይገኛል፡፡ናፍቆት እንደ ልጅ የመጫወት ዕድል አላገኘም በማለት ብዙ መስዋዕትነት የከፈለችው ሰርካለም ፋሲል ትናገራለች፡፡Andualem-Eskindir-300x165
አንዷለም አራጌ በድጋሚ ለእስር ሲዳረግና ፖሊሶች ቤቱን ለመፈተሸ ነፍጥ አንግተው ጎራ ሲሉ የአንዷለም ሁለት ልጆች በቤቱ መጋረጃ ተደብቀው ሂደቱን በፍርሃት ይከታተሉ እንደነበር አባታቸው ያልተሄደበት መንገድ በማለት በሰየመው መጽሐፉ መስክሯል፡፡
የአንዷለም ልጆች አባታቸውን ለመጠየቅ ቃሊቲ በሚያመሩበት ወቅት ሁሌም የምትፈቀድላቸው 30 ደቂቃ የምታበቃው በለቅሶ ነው፡፡ልጆቹ አባታቸው እንዲያጫውታቸው እየጠየቁ ሰዓት ማለቁ እየተነገራቸው በእንባ ይመለሳሉ፡፡እናታቸው ህጻናቱን ሳምንቱን በሙሉ ስታባብል ማሳለፍን እየተላመደችው መጥታለች፡፡
ናትናኤል መኮንን ልጆቹን በትምህርት ትልቅ ደረጃ የማድረስ ህልም እንደሁሉም ኢትዮጵያዊ አባት የነበረው ነው፡፡አጠገባቸው ሆኖ ሊመራቸው ባይችልም እናታቸው የአባታቸውን ህልም ልጆቹ እንዲኖሩ ለማድረግ ብዙ ታትራለች፡፡አሁን የናቲ ልጆች የትምህርት ቤታቸው ሰቃዮች ሆነዋል፡፡
የናትናኤልን መኖሪያ ለመፈተሸ መጥተው ከነበሩ ሰዎች መካከል አንዱ ህጻኑን የናቲን ልጅ ይዞ‹‹እንደ አባትህ እንዳትሆን››ይለዋል፡፡ህጻኑ መልሶ ‹‹መሆን የምፈልገው እንደ አባቴ ነው››በማለት መልሶለታል፡፡
ዳንኤል ሺበሺ ትዳር ቢኖረውም ልጅ አልወለደም፡፡የህዝብ ልጅ የሚል ስያሜ ከበጎ አድራጎት ስራው የተነሳ የወጣለት ዳንኤል ሁለት ልጆችን በመኖሪያ ቤቱ ተቀብሎ እያሳደገ ይገኛል፡፡ዳንኤል በመታሰሩ ግን የሚጎድልባቸው ህጻናት ሁለቱ ብቻ አይደሉም፡፡ዳንኤል ለብዙዎች ደራሽ ነበር፡፡
ሐብታሙ አያሌው የልጁን ሁለተኛ ዓመት የልደት በዓል ለማክበር እየተዘጋጀ ሳለ ነበር ለእስር የተዳረገው፡፡ባለቤቱ ልጃቸው የመኖሪያ ቤታቸው በር በተንኳኳና ስልክ በተደወለ ቁጥር የምታሳየውን ናፍቆት እየተመለከተች በእንባ ትዋጣለች፡፡
ሌሎች በጣም ብዙ አባቶችና እናቶች አልያም ለቤተሰቦቻቸው እንደ ልጅ የሚታዩ ዜጎች ሽብርተኛ ተብለው ዘብጥያ እንዲወርዱ ተደርገዋል፡፡አስደሳቹ ነገር ግን እነዚህ አባቶች፣እናቶች፣እህቶችና ወንድሞች የታሰሩት ስልጣናቸውን ያለ አግባብ በመጠቀማቸው፣ሙስና በመፈጸማቸው፣በሀሰት በመመስከራቸው፣ሰው በመግደላቸውና ህሊናቸውን ጥለው ለሆዳቸው በማደራቸው አለመሆኑ ነው፡፡የታሰሩት ይህች አገር ወዴት እያመራች እንደሆነ በመጠየቃቸው ነው፡፡እነ ህሊና አባታቸውን የሚያገኙትም ይህች አገር የጥቂቶች መሆኗ ሲያበቃ ብቻ ነው፡፡ጥቂቶችን ሐይ ለማለት ግን ብዙዎች ከእንቅልፋቸው መባነን ግድ ይላቸዋል፡፡እስከዛው የየሺዋስ ፣የሐብታሙ ፣የያሲን ኑሩ፣የዳንኤል፣የናትናኤልና የሌሎቹም የእኔ ልጆች ናቸው ማለት ይኖርብናል፡፡

Filed in: Amharic