>

ኦህዴድ ለቀድሞ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ መኪና አበረከተ

የሚኪናው ዋጋ 3 ሚሊየን ብር ወጥቶበታል። 

የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሚቴ ለቀድሞ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ተሽከርካሪ እንዲገዛላቸው በወሰነው መሰረት በዛሬው እለት ተሽከርካሪን ተረክበዋል። የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሚቴ በአዳማ ከተማ ለ10 ቀናት አካሂዶት በነበረው ስብሰባው የቀድሞ የኤፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ወርሃዊ የጡረታ ደሞዝን ጨምሮ ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች እንዲሰጣቸው መወሰኑ ይታወሳል።

ያንንም ተከትሎ 3 ሚሊየን ብር ያወጣ ኒሳን 2018 ሞዴል መኪናን ዛሬ በኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ፅህፈት ቤት ተገኝተው ተረክበዋል።

ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ኦህዴድ የገባውን ቃል ጠብቆ መኪናውን በማስረከቡ ደስታ እንደተሰማቸው ገልፀዋል።

ለዶክተር ነጋሶ እስከ ውጭ ሀገር ድረስ ሂደው እንዲታከሙ የህክምና ወጪያቸው እንዲሸፈን መወሰኑም ይታወሳል።

ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስት ፕሬዚዳንት በመሆን በ1987 የተሾሙ ሲሆን፥ ፥ ለ7 ዓመታትም በፕሬዚዳንትነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

ስልጣን ከለቀቁ በኋላም እንደ ቀድሞ ፕሬዚዳንትነታቸው ማግኘት ያለባቸውን ጥቅማጥቅም ለ4 ዓመታት ሲያገኙ ቆይተዋል።

በ1997 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ ላይ በደንቢ ዶሎ የግል ተወዳዳሪ በመሆን ፓርላማ ከገቡ በኋላ ግን ጥቅማጥቅማቸው እንደተቋረጠባቸው ነው ዶክተር ነጋሶ የሚናገሩት።

ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ከወጣትናቸው እድሜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲዘረጋ ሲደረግ በነበረው ሂደት ውስጥ ከፍተኛ ተሳትፎ ነበራቸው።

ለዚህም ከተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በመሰለፍም የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ሲያበረክቱ ቆይተዋል።

በታሪክ ትምህረት ሶስተኛ ወይም ዶክትሬት ዲግሪያቸውን የያዙት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ፥ እንደ ምሁርነታቸው በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገራትም የተለያዩ ግልጋሎቶችን ሲሰጡ ቆይተዋል።

በተማሩት ትምህርትም የኦሮሞን ባህል፣ ታሪክ እና እሴት የሚያንፀባርቁ እና የኢትዮጵያን አንድነት የሚያጠናክሩ የተለያዩ ጥናቶችን አካሂደዋል።

Filed in: Amharic