>

የቴዎድሮስ ስንብት በመቅደላ (ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን)

እሳት ወይ አበባ

ተስፋ ባጣ ምድረ በዳ
ያንድ እውነት ይሆናል እዳ።
እና ትንፋሼ አልሆነሽም፥ሆኜብሽ መራር መካሪ
“ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ፣”
እውነት ላንቺ መች ተስፋ ናት፥ጉስቁል ልሳንሽን ነክሳሽ
ክንድሽን ካዘለ ቅርስሽ፥መጠላለፍ ሲሆን እጣሽ
ከእንግሊዝ የሞት አማልክት፥መተናነቅ ሲሆን ድርሻሽ
መልመጥመጡ፥መሽቆጥቆጡ መስሎሽ ድንገት የሚያዋጣሽ
የኔ እውነት ሆነብሽ እዳሽ። – – –
ወራሪም ፈጣሪን ላያውቅ
የጣለውን በስሏል እንጂ፥ወድቋል ብሎ ግፉ ላያልቅ
መች ትተርፊሃለሽ ኢትዮጵያ፥ሕዋስሽ አብሮሽ ካልሠራ
አንገትሽ ብቻ መቅደላ፥አፋፍ ወጥታ ብታበራ
የቀረው ሠራ-አካላትሽ፥በየጥሻው ተዘርሮ
ከአባት በወረስሽው ንፍገት፥ነብዞ ደንዝዞ ተቀብሮ
በአጉል ወጌሻ ታጅሎ
እጅና እግርሽ ታሽቶ ዝሎ
እኔን ለጥንብ አንሳ ጥሎ
ከደቀቀ ከደከመ፥ክንድሽ አልነሳ ካለ
ሞት እንጂ ለኔስ ምን አለ?- – –
ሆኖም ጎስቋላ አልምሰልሽ፥የሚያዝንልኝ አልፈልግም
ጠላትሽን በክንድሽ እንጂ፥በእንባሽ ወዝ ባላሸንፍም
የልቤን ፍቅር በስተቀር፥እማወርስሽም ውል የለኝ
የኮሶ ሻጭ ልጅ ደሃ ነኝ። – – –
ደሞም ያለአንቺ የለኝምና
ድሌም የተስፋ ጎሕ ባይሆን፥ከሞት ጋር ትግል ነውና
ከዚህ ሌላ ትእዝብት ውረሽ፥ሳይነጋ እንዳስመሸሽብኝ
ጊዜና ትውልድ ይፍረደን፥ሳልነቃ እንዳስመሸሽብኝ።
ያም ሆኖ ለራስሽ እንጂ ለኔ ከቶም አታልቅሺ
አንቺ ነሽ እንባ እምትሺ። – – –
የእምነትሽ መተሣሰሪያ፤ውልሽ ለተላቀቀብሽ ላንቺ
ነው እንባ እሚያስፈልግሽ።
አሆን፥ይኽን እወቁልኝ፥ምስክር ሁኑኝ ሰማዕታት
ለህርሷ ነው እንባ የሚያስፈልጋት።
ከጠላቶቹ ጭብጥ ውስጥ፥ትንፋሼን ስነጥቃት
ሞቴን ከመንጋጋቸው ውስጥ፥መንጭቄ እኔው ስሞታት
ለአገሬ ብድር ልከፍላት
የነፈገችኝን ፍቅር፥በራሴ ሞት ልለግሳት! – – –
ያኔ ነው እንባዋ የሚያጥራት።
ስለዚህ ለራስሽ እንጂ፥ልቅሶሽ ለኔ ምን ሊረባ
ብቸኛ ምሬት ነው ኃይሉ፥ወኔ መሰለቢያው ነው እንባ።
እና ለራስሽ እዘኚ
እንጂ ለኔ ከቶ አትባክኚ። – – –
ይልቅስ ተረት ልንገርሽ፥የተላከ ከእንግሊዝ ዘንድ
እጅህን ስጥ አለኝ ፈረንጅ፥እጅ ተይዞ ሊወሰድ፥
ምን እጅ አለው የእሳት ሰደድ?
አያውቅም ክንዴ እንደሚያነድ። – – –
ዳዊት እንዲያ በበገናው፥ማልቀስ ማላዘን መያዙ
ይኸ የጎሊያድ ውላጅ፥ቢበዛበት ነው መዘዙ
ምንጩ እንደአሽን እየፈላ፥አገሩን ምድሩን ማንቀዙ
ቸግሮት ነው፥መጋፈጡ፥ከስንቱ መወናጨፉ
በባላንጣው ሳቢያ ምክንያት፥የራሱን ወገን ማርገፉ። – – –
ታዲያ እንግዲህ አንቺ ኢትዮጵያ፥እኛስ ልጆችሽ ምንድነን?
አመንኩሽ ማለት የማንችል፥ፍቅራችን የሚያስነውረን
እዳችን የሚያስፎክረን
ግፋችን የሚያስከብረን
ቅንነት የሚያሳፍረን፥ቂማችን የሚያስደስተን
ኸረ ምንድነን? ምንድነን?
አሜከላ እሚያብብብን፥
ግፍ የሚለመልምብን፥
ከአረም ጋር ያፈራን ጊንጦች፥ከእንክርዳድ ያልተለየን ዘር
ግንዱ ከምርቱ ተማጥቆ፥ከቶ ያልተበራየን መከር
ምንድነን? ምንድነን እኮ?
አረጋዊውን ከወኔ ጣር፥ካልፈታን ከፍርሃት ምርኮ
እንደ ወዶ ገባ ወደል፥መጠለሉን ከሴት ታኮ – – –
ካቃተን፥ ምንድነን እኮ?
አየሽ አንቺ እማማ ኢትዮጵያ፥አየሽ አንቺ እናት ዓለም
ቃል የእምነት እዳ ነው እንጂ፥የአባት የእናት እኮ አይደለም። – – –
ያም ይቅርና መርዶ ላርዳሽ፥ስሚው እኔ እንደሰማሁት
እርም በልተሽ ከምትቀሪ፥ስሚው ገብርዬንም ጣሉት። – – –
እስኪ እንግዲህ በይ ፍረጂኝ፥ከእንግዲህ እኔ ፍሬ አላይም?
“ዘርቶ መቃም ወልዶ መቃም”
አባባል ለኔ አይባልም?
እስቲ ገብርዬን መሰል ዘር፥ፍሬው ከቶ አይለመልምም?
እኔስ ዘር ዘራሁ አልልም? – – –
ምነው ፍንጭትክን ገብርዬ፥ያን ፍንጭትክን አጨለሙት
እንደ ሬት ልግ አከሰሉት
እንደ ኮሶ አስመረሩት? – – –
ከጡቶችሽ እቅፍ ነጥቀው፥ከማኅፀንሽ ፍቅር ቆርጠው
እውነትን ሲገሉ እንዲህ ነው፥ፈገግታውን አጨልመው።
እስቲ እባክህ ገብርዬ፥የዛሬን እንኳ ስቀህ ሙት
በዕድል ጥቀርሻ እንደአጀሉት
እንደ ወላድ ጣውንት ጡት
አርማጉሳ እንደቀለሙት
ፈገግታህን አያጥቁሩት።
እምቢ በላቸው ገብርዬ፥የአባት ሤራ እንዳስረገዙት
በመሃል እንዳሳገዱት
የነብስህን ጮራ ብርሃን፥ከገፅህ እንደቀበሩት
ዘለዓለም ላያጨልሙት
ወንድምዬ እምቢ በላቸው ፥የዛሬን እንኳ ስቀህ ሙት። – – –
ያለፈ ጥረታችንን፥ሳስታምመው ትዝ ሲለኝ
ከሞከርነው ነገር ይልቅ፥ያልሞከርነው ነው የሚቆጨኝ።
እና በኔ ይሁንብህ መጣሁ፥ስቀህ ተቀበለኝ
እኔም ላዋይህ አድምጠኝ – – –
እጅህን ስጥ አለኝ ፈረንጅ፥ እጅ ተይዞ ሊወሰድ
ምን እጅ አለው የእሳት ሰደድ?
አያውቅም ክንዴ እንደሚያነድ። – – –

Filed in: Amharic