>

መሪዎቹን በማኪያቬሊ መፅሀፍ አጥምቆ ቃለ መሀላ የፈፀመው ኢህአዴግ

የማነ ምትኩ
“ከምትወደድ ይልቅ የምትፈራ፥ ከምትፈቀር ይልቅ የምትጠላ ሁን።” ይላል ማኪያቬሊ “ስልጣን እንዴት ይገኛል፥ እንዴትስ ማስጠበቅ ይቻላል?” በሚል ሃሳብ ዙሪያ ባውጠነጥንበት መፅሀፉ፥ የስልጣን ጥመኞችን ሲመክር። ….የሞራል ለከት የሚባል ነገር ፈፅሞ አይኑርህ። …እስከዛሬ ድረስ ወደ ስልጣን የመጡት በሙሉ፥ መሰረታዊ ስነምግባሮችን ጥሰው ነው። …አንድም ፍፁም ርህሩህ ሁን አሊያም የለየለት አረመኔ ሁን። አማካይ ስፍራ አዋጭ አይደለም። … የሚያሰጋህን ተቀናቃኝ አንዴ በማያዳግም እርምጃ እንዳይነሳ አድርገህ ሰባብረው። …እርምጃህን በአንድ ጊዜ አገባደው። አጥራውና እንደአዲስ ጀምር። … ከቀድሞ ስርዓቶች፥ ገዢዎችና ጊዜ ጋር ቁርኝትና ትዝታ እንዳይኖራቸው ምልክቶችን አጥፋ። ስሞችን ፋቅ። ቅርሶችን አውድም። … መንደሮችን ጎዳናዎችን አዲስ ስያሜ ስጣቸው፥ በአዲስ ስም፥ በአዲስ ታሪክ፥ በአዲስ መንፈስ፥ ሀ ብለህ ሌጋሲህን ገንባ።

ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣኑን ለማስጠበቅ ሲባል ብቻ የማኪን ምክር አንድ በአንድ ከውኗል። ኢህአዴግ መሪዎቹን አንድ በአንድ በዚህ መፅሀፍ አጥምቆ ቃለመሀላ የፈፀመ ነው የሚመስለው። ቀውስ ባጋጠማቸው ቁጥር፥ የሚገልጡት መፅሀፍ ይህን መፅሀፍ እስኪመስል ድረስ፥ ትራሳቸው ስር ቀብረው የሚተኙ እስኪመስል ድረስ፥ መፅሀፉን አሟጠው ተጠቅመውበታል። ሆኖም አንዲት ምክሩን ልብ አላሏትም።

“ቅጣትህን ቶሎ አገባድድ” የምትለዋን። “ማስወገድ ያለብህን በአንድ ጊዜ አስወግደህ ጨርስ። ማወደም ያለብህን በአንድ ጊዜ አውድም። … ቶሎ ወደ መልሶ መቋቋም፥ ወደ ግንባታ፥ ወደ ልማት ግባ። …ካልሆነ እርምጃህ ቀጣይነት ካለው፥ ጠላት እያበዛህ፥ ህዝብን ለማይቀረው አመፅ እያነሳሳህ መሄድህ አይቀርም። ይህ ደግሞ በራስ ላይ ሞትን መደገስ ነው።” ማለፊያ ምክር ነበረች፥ ግን ሳቷት። ለ27 ዓመታት እንደጀመሩ እስኪጨርሱት ድረስ ጥፋቱን ተያይዘውታል።

ምክንያታቸው ደግሞ በጣም ግልፅ ነበር። ከመነሻው ጠላታቸውን ህዝብ አድርገዋል። ህዝብን ደግሞ በአንድ ጊዜ ማስወገድ አይችልም።

Filed in: Amharic