>

የኢትዮጵያ ሕዝብ በክፋታቸው እጅግ የባሱ አመራሮች ስልጣን መያዛቸውን አውቆ ትግሉን ማፋፋም አለበት ተባለ (በወንድወሰን ተክሉ)

ከሁሉም የበለጠ ጨቃኝ፣ሙሰኛ እና ጎጠኛ የሆነው የህወሃት አመራር ስልጣን ይዞ ተለውጫለሁ ማለት ስላቅ ነው ሲሉ አቶ ገብረመድሃን አርዓያ ተናገሩ

 

የሰሞኑ የህወሃት የስልጣን ሹም ሽር በፓርቲውም ሆነ በመንግስት ደረጃ ያለውን ችግር ይበልጥ የሚያባብስ እንጂ የሚፈታ አመራር ወደ ስልጣን አልመጣም ሲሉ አቶ ገብረመድህን አርዓያ ለኢሳት ዛሬ ገለጹ።
ከህወሃት መስራች አመራሮች ውስጥ አንዱ የሆኑትና ከድርጅቱ በ1980 ላይ ከአቶ አብርሃም ያየህ ጋር የተለዩት አቶ ገብረመድህን ለኢሳት እንደገለጹት “የኢትዮጵያንና የትግራይን ሕዝብ ለከፍተኛ ስቃይ የሚዳርጉ የባንዳ እና ጸረ ኢትዮጵያ አቃም ያለው የአቶ ስብሃት ነጋ ቡድን ወደ ስልጣን ወጥታል” ሲሉ ተናግረዋል።

ላለፉት ሁለት ወራት አንዴ በአዲስ አበባ ቀጥሎ ደግሞ በትግራይ መቀሌ በር ዘግቶ ሲመክር የሰነበተው የህወሃት ማእከላዊ ኮሚቴ አመራር እነ አቶ አባይ ወልዱ፣ወ/ሮ አዜብ መስፍን እና የአቶ መለስን ራእይ እንተገብራለን የሚሉትን ሃይሎች ከስልጣን በማውረድ በአቶ መለስ ተገፍተናል የሚሉ የእነ አቶ ስብሃት ነጋ ቡድን ወደ ስልጣን በመምጣት ስብሰባው ለግዜው መደምደሙ ይታወቃል።

ህወሃትን በ1972 ህወሃትን እንደተቀላቀሉና በፈዳይነት[ነፍስ ገዳይነትና ሽብርነተኝነት] ስራ ላይ የተሰማራውና ሃላም የደህንነቱን ክፍል የተቀላቀለው ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤልን የድርጅቱ ዋና ጸሃፊ በማድረግ እና ሞንጆሪኖን [ወ/ሮ ፈትለወርቅ ]በም/ል ሊቀመንበርነት በመምረጥ ተሃድሶ መውሰዱን እና መጠናከሩን ድርጅቱ ማስታወቁም ይታወሳል።

እነዚህ ወደ ስልጣን የመጡት አመራሮች ከትግሉ ግዜ ጀምሮ በስልጣን ቆይታቸውም ጎጠኝነት፣ በጨፍጫፊነት፣በሙስና ከማንኛቸውም አመራሮች በይበልጥ የተጨማለቁ መሆናቸውን በመግለጽ ድርጅቱ ታድሻለሁ ማለቱ የኢትዮጵያን ህዝብ ለማታለል ነው ሲሉ አቶ ገብረመድህን ዓርዓያ በአጽንኦት ተናግረዋል።

“ህወሃት ከአፈጣጠሩ ጸረ-ሕዝብ፣ጸረ-ሀገር፣ጸረ-ዲሞክራሲ፣ጸረ-ፍትህ የሆነ ድርጅት ነው” ያሉት አቶ ገብረመድህን “ድርጅቱ በ35ቀናት ውስጥ ተሰብስቤ ታድሻለሁ ሲል አይደለም በ35ቀናት በ35ዓመታትም መታደስም ሆነ መለወጥ ያልቻለ ነው” ሲሉ ድርጅቱ ከቶም ቢሆን የመታደስ ሁኔታን አይቀበልም ሲሉ ይናገራሉ።
ዶ/ር ደብረጺዮን፣ወ/ሮ ፈትለወርቅ[ሞንጆሪኖ]አቶ ጌታቸው አስፋና አቶ ስብሃት ነጋ በትውልዳቸውም ጭምር ከፊል ኢትዮጵያዊ ያልሆኑና የባንዳነት ታሪክ ያላቸው አመራሮች መሆናቸውን በዝርዝር ያስረዱት አቶ ገብረመድህን ስብስቡ እወክለስዋለሁ የሚለውን የትግራይን ሕዝብ ለከፍተኛ አደጋ ያጋለጠ ሙሰኛ፣ጎጠኛና ኢ-ዲሞክራት የሆነ አመራር ነው ሲሉ ገልጸዋል።
“የኢትዮጵያ ሕዝብ ታድሻለሁ ከሚለው ህወሃት ምንም የተሻለ ነገር ሳይጠብቅ ይልቁንም በግመግደልና በመዝረፍ የሚያምን አመራር እንደመጣባት በማወቅ ትግሉን እጅግ አጠናክሮ መቀጠል አልበት “ሲሉ አቶ ገብረመድን ሕዝቡን አስገንዝበዋል።

Filed in: Amharic