>

የመጨረሻው መጀመሪያ (ኤርሚያስ ለገሰ)

የሕውሓት አገዛዝ የመጨረሻውን መጀመሪያ ጐዳና ጀምሮታል። ይህ ምዕራፍ እውነተኛው የስርአቱ ባህሪ በማያወላዳ መንገድ የሚገለጥበት ሆኗል ። በተለይም የትግራይ ተወላጆችን በፍራቻ በመሸበብ ከሌሎች ኢትዬጲያውያን ጋር ደም እንዲቃቡ የማይቆፍረው ጉድጓድ እንደማይኖር በግልፅ የታየበት ነው። የሰሞኑ አስደንጋጭ ክስተቶች ዝም ብለው የመጡ ሳይሆን ከአገዛዙ ውስጣዊ ባህሪ የሚመነጩ ናቸው።

ሰለሆነም የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያደርገው የስርአት ለውጥ ትግል ህውሓት ትግሉን ወደ ሌላ አቅጣጫ በመውሰድ እንዳይቀለብሰው የሚያደርጉ ስትራቴጂ እና ስልቶችን መከተል እንደሚያስፈልግ ግላጭ የወጣበት ሆኗል። ለዛሬው በኦሮሚያ እየተካሄዱ ያሉ ሕዝባዊ ትግሎችን ለማገዝ ይረዳሉ የምላቸውን ጥቂት ቁምነገሮች ለመጠቆም እፈልጋለሁ።

# የቅድሚያ ቅድሚያው ህዝባዊ እምቢተኝነቱንና ተቃውሞውን አጠናክሮ መቀጠል ይሆናል። ሰልፎችን አለማቋረጥ፣ መንገድ መዝጋት፣ የቀበሌና ወረዳ እንዲሁም የመንግስት ቢሮዎችን ማጨናነቅ፣ የፓርቲ ጽሕፈት ቤቶችንና ኩባንያዎችን ማገት ያስፈልጋል። ከህውሓት/ ኢህአዴግ ጋር ባላቸው የጥቅም ትስስር የሚንቀሳቀሱ ባለሃብቶችን ንብረት ቆጠራ ማካሄድና ከአገዛዙ ጋር ያላቸውን ትስስር ፍቺ እንዲፈጽሙ ማስጠንቀቅ ያስፈልጋል። የኤፈርት ምርቶችን የሚቀበሉ ነጋዴዎች ውላቸውን እንዲያቋርጡ ማስጠንቀቂያ መላክ ያስፈልጋል። የጉና ኢንተርፕራይዝ የጅምላ እና ችርቻሮ ሱቆች ተለይተው መዘጋት ይኖርባቸዋል። የአንበሳ፣ ወጋገን ባንክና የአፍሪካ ኢንሹራንስን ህዝቡ እንዳይጠቀም ማድረግ ያስፈልጋል። እንደዚህ አይነት እርምጃዎች ተጠናክረው መቀጠል ያለባቸው ነው። በተከታታይ ተጠናክረው መቀጠል ካልቻሉ ህውሓት ትንፋሽ የመሰብሰቢያ ጊዜ እንዲያገኝ ያደርገዋል። ከዚህ በተጨማሪም ከህውሓት ጋር አብረው አገር ማፍረሻ አሳብና መሳሪያ ሲያቀብሉ የነበሩት እነ ለማ መገርሳ ከሁሉም የበለጠ ከሃዲዎች ሊሆኑ እንደሚችሉ መገንዘብ ያስፈልጋል። በሕዝባዊ ማዕበል ተወጥረው ካልተያዙና የሚወስዷቸው አስገዳጅ እርምጃዎች የሚያመላክቱ የተቆጠሩ እቅዶች ካላቀበልናቸው አስደንጋጭ ሁኔታ አጭር ጊዜ ውስጥ ሊከሰት ይችላል። በውስጣቸው ያለው አድርባይነት የወለደው ደካማ አቋም አገንግኖ የህዝቡን ትግል ለማጨናገፍ ሊሯሯጡ ይችላሉ። በመሆኑም በህዝባዊ ተቃውሞ እንዲናጡና ወገባቸው እስኪጐብጥ ማስጨነቅ ያስፈልጋል።

ሕዝባዊ ተቃውሞው እንዲቀዘቅዝ የሚያደርጉ ማንኛውም አካላት ፀረ ለውጥ መሆናቸውን ተገንዝቦ ሊጋለጡ ይገባል። በግራ እጁ ከተቃውሞ ወደ አብዬት ተሸጋግረናል የሚል ነጋሪት ጐስሞ ሲያበቃ በቀኝ እጁ የሌለበትን የሕዝብ ማእበል ሊደፍቅ የሚመጣ ቡድን ታሪክና ህዝብ ሊወቅሰው ይገባል። የትግሉ ባለቤት ማንም ሳይሆን ህዝቡ ነው። ትግሉ ደግሞ የስርአት ለውጥ እስኪያመጣ ተጠናክሮ ያለማቋረጥ ይቀጥላል። ትግሉ ያለማቋረጥ ባይቀጥል ኖሮ ኦቦ በቀለ ገርባ አይፈታም ነበር።

ህውሓት ከመካከለኛ እና ረጅም ጊዜ አኳያ የትግራይ ህዝብ ጠላት መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። ለማንም ግልጥ እንደሆነው አምባገነን ስርአቶች ፈሪና ድንጉጦች ናቸው።ፈሪዎች ደግሞ ሁሉንም ጠላት ያደርጋሉ።ሁሉም ሰው በጠላትነት ይፈልገኛል የሚል በሽታ ይጠናወታቸዋል። ስለዚህ ሁሉንም ለመጥረግ ይፈልጋሉ። መጥረግ የሚጀምሩት ደግሞ በቅርባቸው ከሚገኘው ሰው ነው።ህውሓት ከፍጥረቱ ጀምሮ የትግራይ ሕዝብን እየጨፈጨፈ መምጣቱ የታሪክ እውነታ ነው። ይሁን እንጂ ወደ ስልጣን ከመጣ ጀምሮ ለትግራይ በማድላት በኢንዱስትሪ ፣ በማህበራዊ ተቋማት ፣ መሰረተ ልማት ግንባታና የሰው ሃይል ልማት ትኩረት ሰጥቶ ተንቀሳቅሷል። የፓለቲካ፣ ደህንነት እና ወታደራዊ ስልጣኑንም በትግራይ ተወላጅ የሆኑ የሕውኃት አባላት የበላይነት እንዲመራ ማድረጉ የአደባባይ ሚስጥር ነው። እነዚህን የመሳሰሉ ኢፍትሐዊ ድርጊቶች በትግራይ ተወላጆችና ሌላው ኢትዬጵያዊ መካከል መተማመን እንዳይኖር አድርጓል። በዚህ ምክንያት በብዙ ኢትዬጲያውያን ዘንድ ሁሉንም የትግራይ ተወላጆች መጠራጠርና ህውሓት በፈለገው መንገድ የሚታዩበት ሁኔታ ተፈጥሯል። እንዲህ አይነት የጭፍለቃ አተያይ አደገኛ ከመሆኑም ባሻገር የትግል ዘመኑን ከማራዘም ውጭ የሚፈይደው ነገር የለም። በመሆኑም የትግራይ ሕዝብና ህውሓትን ነጣጥሎ የሚመለከት አቅጣጫ ቀይሶ መንቀሳቀሱ ለነገ የሚባል አይደለም። በሌሎች የኢትየጵያ አካባቢዎች የሚካሄደው ሕዝባዊ እምቢተኝነት ተጠናክሮ መቀጠል እዛው ሳለ በሕውኃት እና በትግራይ ህዝብ መካከል ያለውን ልዩነት የበለጠ ያሰፋዋል።ስለዚህ አሁንም ወሳኙ ነገር ሕዝባዊ ማዕበሉን አጠናከሮ መቀጠል ነው።

የደህንነት ተቋሙ ዋነኛ ክንፍ የሆነው የትግራይ ልማት ማህበር በኦሮሚያ ወረዳ፣ዞንና ከተሞች ያሉትን ጽሕፈት ቤቶች በአስቸኳይ መዝጋት። እነዚህ ጽሕፈት ቤቶች ከላይ ከላይ ሲታይ ለትግራይ ክልል ልማት ገንዘብ የሚያሰባስቡ ቢመስልም ዋነኛ ስራቸው ስለላ ማካሄድ ነው። የሕውኃት የበላይነትን የሚጋፋ ፣ በአገዛዙ ላይ ተቃውሞ የሚያስነሱ ሰዎች የሚታሰሩት፣ ደብዛቸው የሚጠፋው በልማት ማህበሩ አባላት ጥቆማ ነው። በተቃራኒው ደግሞ ለህውሓት እንደ እንዝርት የሚሾሩ ጥቅመኛ እና አድርባዬችን ወደ ሹመት የሚያመጡት የትግራይ ልማት ማህበር አመራርና አባላቶች ናቸው። በእነዚህ አካባቢዎች የትግራይ ልማት ማሕበር አባል ሆኖ የሕውሓት አባል ያልሆነ የለም። በመሆኑም በየአካባቢው የተከፈቱትን የትግራይ ልማት ማህበር ቢሮዎች መዝጋት፣ በማህበሩ ስም የሚካሄዱ ማናቸውም ስብሰባ እንዳይኖር ማገድ የቅድሚያ እርምጃ ሊሆን ይገባል።

በኦሮሚያ የሚኖሩ የሕውሓት አባላት በሚኖሩበት ቀበሌ ሄደው የታጠቋቸውን የጦር መሳሪያዎች ፣ በቤታቸው የሚገኙ ማንኛውም ወታደራዊ ቁሳቁሶች ማስረከብ ይኖርባቸዋል። በሂደትም በፍቃደኝነት ህውሓትን አውግዘው አባልነታቸውን በመሰረዝ፣ የአባልነት መታወቂያቸውን ቀዳዶ በመጣል ከህብረተሰቡ ጋር የሚቀላቀሉበት ሁኔታ ማመቻቸት ያስፈልጋል። እንደዛ እስኪሆን ድረስ ሁሉም የሕውኃት አባላት በየሳምንቱ ቀበሌ እየሔዱ ሪፖርት ማድረግና መፈረም ይኖርባቸዋል።

የደህንነት መዋቅሩ ሌላኛው ክንፍ የሆኑትን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኤዜአ )፣ የዋልታ እና ሬዲዮ ፋና ወኪል ጵህፈት ቤቶችን መዝጋት። እንደ ጅማ ከተማ የመሳሰሉ የፋና FM ሬዲዮ ጣቢያዎችን አገልግሎት ማቋረጥ።

Filed in: Amharic