>

የተፈናቃዮች ቁጥር አሁንም እየጨመረ ነው ወደ መቶ ሺህ ደርሷል (ቢቢኤን)

በሰሞነኛው የኦሮሚያ እና ሶማሌ ክልል ግጭት የተፈናቃዮች ቁጥር አሁንም እየጨረመ መሆኑ ታወቀ፡፡ መረጃዎች እንደጠቆሙት፣ የተፈናቃይ ሰው ቁጥር ወደ መቶ ሺህ ደርሷል፡፡ ድርጊቱ የተከሰተው በአጭር ጊዜ ውስጥ በመሆኑ፣ የተፈናቃዩን ሰው ቁጥር ለሰሚ አስደንጋጭ አድርጎታል፡፡ ግጭቱ አሁንም ሙሉ በሙሉ መፍትኤ አለማግኘቱ፣ የተፈናቃዮችን ቁጥር ከዚህም ይበልጥ ሊያንረው እንደሚችል ስጋት ፈጥሯል፡፡ ከአንድ ወር በላይ ለሆነ ጊዜ የዘለቀው የሁለቱ ክልሎች ግጭት፣ አሁን ላይ ሙሉ ለሙሉ መፍትኤ አግኝቷል የሚባልበት ደረጃ ላይ ገና አልደረሰም፡፡


ግጭቱ ከፍተኛ ጉዳት ያስከተለ እና እያስከተለ ሲሆን፣ በተለይ ተፈናቃዮችን በተመለከተ እየወጡ ያሉ መረጃዎች ጆሮ ጭው የሚያደርጉ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ አንዳንድ መረጃዎች በበኩላቸው የተፈናቃዮችን ቁጥር እስከ 120 ሺህ ሲያደርሱት ሌሎች ደግሞ እስከ መቶ ሺህ ይገምቱታል፡፡ ተፈናቃዮችን በተመለከተ የኦሮሚያ ክልል አስተዳደር ትክክለኛ ቁጥር ማስቀመጥ አልቻለም፡፡ በተከሰተው ግጭት ከሁለቱም ወገኖች የተፈናቀሉ ሰዎች ቢኖሩም፣ የላቀውን ወይም ከ95 ፐርሰንት በላይ የሚሆነውን ቁጥር የያዙት ግን የኦሮሞ ተወላጆች ሆነው ተገኝተዋል፡፡


የተፈናቃዮች ቁጥር እንዳለ ሆኖ ደግሞ፤ የሟቾችን ቁጥር በተመለከተም የተለያዩ መረጃዎች እየወጡ ነው፡፡ በተከሰተው ግጭት የተነሳ በጠቅላላው ከሁለቱ ወገኖች እስከ 900 የሚደርስ ሰው ህይወቱን አጥቷል፡፡ ሟቾችን በተመለከተም በመንግስት በኩል ትክክለኛ መረጃ እየተሰጠ አይደለም፡፡ መንግስት ግጭቱ ብዙም ጉዳት አላስከተለም ለሚል ፕሮፓጋንዳ ሲል ብቻ፣ የሟቾች እና ተፈናቃይ ሰዎችን ቁጥር አሳንሶ እየተናገረ ይገኛል፡፡ ሆኖም የመረጃ ምንጮች ግን፣ የሟቾችን ቁጥር 900 ላይ ሲያቆሙት፣ የተፈናቃዮችን ቁጥር ደግሞ እስኪ 100 ሺህ ያደርሱታል፡፡
Filed in: Amharic