>
5:13 pm - Sunday April 19, 4629

‘አጃኢብ’ ያሰኘው የአዜብ መስፍን ወሬ (ክንፉ አሰፋ)

“አከ’ሲ” አለ ያገሬ ሰው፣   ከሰሞኑ ‘አጃኢብ’ ያሰኘውን የአዜብ መስፍን ወሬ ሲሰማ። አዜብ ልምድ ያላት ውሸታም እንጂ  ልምድ ያላት ኮሜዲ አትመስልም ነበር። ከሚሚ ስብሃቱ ጋር  በያዝነው ሳምንት የተወኑት ድራማ ግን ጦሽ አርጎ ያስቃል።  መቼም ጥርስ እንጂ ልብ አይስቅ።  ፈንድሻም’ኮ ልቧ እየተቃጠለ ነው ፊትዋ ሚፈካው።

ሴትየዋ አይኗን ሳይሆን ቅንድቧን በጨው አጥባ “ምንም የለኝም ግን ይወረስ” ነው የምትለው።  መለስ የባንክ ደብተር ይቅርና መንጃ ፈቃድ እንኳ የለውም ስትል የቀለደችበት  ወቅት ሩቅ አይደለም።  እርግጥ ነው አዜብ በራስዋ ስም እንኳን ሕንጻ፣ ሲም ካርድም ሊኖራት አይችልም። ጥሩ ጋዜጠኛ አልገጠማትም እንጂ፣ ቢገጥማት፣  “እመኑኝ ልጃገረድ ነኝ!” ብላ እያለቀሰችም ቢሆን ለማሳመን ትሞክር ነበር።  ልጆቼን እየተበደርኩ ነው የማስተምረው ብላ በተናገረች ሰሞን ኤ.ቢ.ሲ ኢንተርናሽናል የተባለው የማድሪድ ጋዜጣ ወ/ሮ አዜብ መስፍን በአንድ ቀን የግል ግብይት ብቻ 1.5 ሚሊዮን ዶላር እንዳወጣች ዘግቦ ነበር።

የወዲ ስብሃቱ ልጅ አላማ ‘የሙስናዋን ንግስት’ ነጻ ለማውጣት መሞከር ባይሆን ኖሮ ፣  በነካ እጅዋ ሰሞኑን በወደቀ ሂሳብ እየተቸበቸቡ ስላሉ የአዲስ አበባ ሕንጻዎች ጉዳይ ታነሳ ነበር።

የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ጠቅልሎ  የያዘው ኤፈርት አናት ላይ ቁጭ ብላ “ምንም የለኝም” የሚል ነጠላ ቀልድ የለቀቀችው አዜብ 30 ሚሊዮን ብር  ከኪስዋ መዝዛ  ለመቀሌ ስፖርት ክለብ መለገስዋን እንኳ ረስታዋለች። ግብር የማይከፍልና የኦዲት ቁጥጥር የማይነካው ደጀና የተባለው የማፍያ ኩባንያ ከኤፈርት ጋር ተጣምሮ የሃገሪቱን ኢኮኖሚ እኩሌታ ይዟል። ካፒታሉ አፍሪካ አንደኛ  የሆነው የዚህ ጥምር CEO ነኝ ብላናለች አዜብ። ሰማይ አይታረስ፣ ንጉስ አይከሰስ፣ ደሞዝ አይነገር.. ደሞዝ አይጠየቅ! በዛሚ!

“ዛሚ ኤፍ.ኤም “ ተብሎ በሚጠራው የነሚሚ ስብሀቱ ራዲዮ ጣቢያ ከዚህ ቀደም የሞራል ቀውስ ውስጥ ገብተው የሚዋኙ ትናንሾችን እያቀረበ፣  በደረቀ ፕሮፓጋንዳ  ብቻ ብዙ መጓዝ ባለመቻሉ፣  የፕሮግራም ለውጥ ያደረገ ይመስላል። እንደ አዜብ መስፍን አይነቱን ጥያቄና መልስ እያስጠና ተከታታይ ድራማ ማቅረብ ጀምረዋል። የመጀመርያው ሾው  በቴዲ አፍሮ  ተጀመረ ። ገድለው ሃውልት መስራት ለነሱ አዲስ ነገር አይደለምና ጸሃይ የሞቀውን “እርምጃው ፍትሃዊ አይደለም”  እንቶፈንቶ ደጋገመችው።  የቴዲ አፍሮን የአልበም ምረቃ ያገደውን ስውር እጅ  አደባብሳ አለፈችው።  ስለማታውቀው  ፍትህ እና መብት መለፈፍዋ ግን ብዙዎችን ሳያስደምም አልቀረም።

አዜብ በተከታዩ ክፍል ብቅ ብላ፣  “የምተዳደረው በዶሞዝ ነው። መለስም፣ እኔም፣ ልጆቼም ሃፍት የላቸውም።” አለችን።

“ውልና ማስረጃ የሌለው ሃፍት ካላኝ  ቦታውን ያሳዩኝ እና ለኢትዮጵያ ህዝብ ልመልሰው”  የሚለው ሕጻን ልጅን እንኳ የማያሳምን አባባልዋ ትንሽ ያስቃል። ሕዝብ በደቦ ወጥቶ የአዜብና ዘመዶችዋን የልተመዘገበ ንብረት እንዲያፈላልግላት  መጠየቅዋ ነስ ወይንስ የእሷም ህንጻዎች  እንደ  ኮንዶሚኒየሙ “ጠፍተዋል”  ብለው ነገሯት?  ከሠበታ የወሰደችው 1200 ሄክታር መሬት የቀብርዋ ስፍራ መሆኑ ነው። ይህ ደግሞ በነሱ ቋንቋ ሙስና አይባልም።  ሙስናም ቢሆን ለከባባድ ሚዛን የህወሃት አባላት የአገልግሎት ስጦታ ነው።  አቶ አያሌው መንገሻ፣ የቀድሞው የደህነት መ/ቤት ሹም ህብር ሬዲዮ ራይ ቀርበው በሰጡት ቃለ ምልልስ “በሕወሃት ሙስና ወንጀል አይደለም” ብለውናል።

ኮሜዲያን ወደ ውጭ ሲሰደዱ፣ ፖለቲከኞቹ  ቦታቸውን ይዘዋል ልበል?  ከሰሞኑ የህወሃት ካድሬዎች እንደጉድ መቀለድ ጀምረዋል። አዜብ እና ከሚሚ ተደራጅተው የሰሩት ይህ  እየሳቁ-ማንባት ተውኔት ግን ከኮሜዲ መስመር ወጣ ይላል።

ቃለ-ምልልሱ የተጠና ላለማስመሰል እንኳ አለመሞከራቸው፣ ለአድማጭ ያላቸውን ንቀት ያሳያል።  “መኖርያ ቤት ሰርተሻል?” የሚለው የመጀመርያ ጥያቄ ሲቀርብላት ነበር ፣ አዜብ “ከሌላው ጋር አብሬ ልመልሰው” ስትል ተካታዩን ጥያቄም እንዳምታውቀው ያስፎገረችው። መዋሸት አንድ ነገር ነው። ውሸት ለማስመሰል መቻል ደግሞ ማወቅን ይጠይቃል። ይህንን እንኳን ማድረግ አልቻሉም። የዛሚዋ ካድሬ ሚሚ ስብሃቱ አዜብን ለማንጻት ብዙ የታከከች ይመስላል – ለዛሬ ባይሳካም።

አዜብ እውቀት ነጻ ትሁን እንጂ፣  በጣም ደፋር ናት።  የእንግሊዝን መንግስትንም ሆነ  የአውሮፓ ህብረትን ብትጠይቁ  ምንም የሌለኝ  ድሃ መሆኔን ይነግሯችኋል ትለናለች። አዜብ ሃብታም ግን የምትሆነው ህወሃት ወይንም ኤፈርት ሲለቅቃት ብቻ ነው። “ድርጅቴ ሲለቅቀኝ በግሌ ከጉልት ንግድ በመጀመር ሃብታም ሆናለሁ” ስትል አስቃናለች።

ይህንን ያድርግልሽ ብለናል!

Filed in: Amharic