>
5:13 pm - Thursday April 19, 3303

ኦነግ በኦሮሚያ የሚደረገውን አድማና ትግል እየመራ መሆኑን አስታወቀ (ዋዜማ ራዲዮ)

ዋዜማ ራዲዮ- የኦሮሞ ነፃነት ግንባር በቅርቡ የተደረገውን ቤት የመቀመጥ አድማ ጨምሮ በኦሮሚያ ወጣቶች በአፋኙ ስርዓት ላይ የሚያደርጉትን ትግል ከፊት ሆኜ እየመራሁት ነው ሲል አስታወቀ።
ድርጅቱ በኤርትራ አስመራ ለአስር ቀናት ያደረገውን ጉባዔ ሲያጠቃልል ባወጣው መግለጫ የኦነግ ክንፍ የሆነው የኦሮሞ ወጣቶች ክንፍ (ቄሮ) እያካሄደ ያለው ትግል ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቡን አስምሮበታል።
ኦነግ ለቄሮ የሚያደርገውን ድጋፍ በሶስት እጥፍ በማሳደግ በቀጣዮቹ ወራት በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት ለማስወገድ እንደሚንቀሳቀስ ተናግሯል።
ለኦሮሞ ነፃነት የሚታገሉ ድርጅቶች ሁሉ ከጎኑ እንዲሰለፉ የጠየቀው ኦነግ የኦሮሞ ነፃ አውጪ ጦርን ወደተግባር ለማስገባት የገንዘብ የቁሳቁስና የሰው ሀይል አቅሙን በከፍተኛ ደረጃ ለማሰደግ እየሰራሁ ነው ብሏል። ደጋፊዎቹም ለዚህ እንዲተባበሩ ጥሪ አቅርቧል።

የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ የጠየውቀው መግለጫው ከሌሎች ከተጨቆኑ የኢትዮጵያ ብሄሮች ጋር ለመተባበር ዝግጁ ነኝ ብሏል።
አስመራ የሚገኘው ኦነግ ከሶስቱ ዋና ዋና የኦነግ አንጃዎች አንዱ ሲሆን በአቶ ዳውድ ኢብሳ ይመራል።
በቅርቡ በኦሮሚያ የተደረገውንም ሆነ ሌሎች አድማና አመፃችን በማስተባበር በውጪ ሀገር ያሉ አክቲቪስቶች በተለይም የኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ስራ አስኪያጅ ጃዋር መሀመድ ሀላፊነቱን ወስዶ ሲሰራ መቆየቱ ይታወቃል።

Filed in: Amharic