>

በቂሊንጦ ማ/ቤት በደረሰው እሳት ቃጠሎ ወቅት 67 ሰዎች ተገድለዋል/ሞተዋል (የኢሰመፕ ልዩ ዘገባ)

በኢትዮጵያ የፌደራሉ መንግስት ከሚያስተዳድራቸው ቃሊቲ፣ ዝዋይና ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤቶች በተጨማሪ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙ እስረኞችን የያዘው ‹የቂሊንጦ ጊዜ ቀጠሮ ማረፊያ ቤት አስተዳደር› በርካታ ተጠርጣሪዎች (እስረኞች) የሚገኙበት እስር ቤት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህ እስር ቤት 3000 ገደማ እስረኞች የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ግማሽ ያህሉ በሽብር የተከሰሱና ሌሎች የፖለቲካ እስረኛ ናቸው፡፡

ቂሊንጦ እስር ቤት የኦፌኮ ም/ፕሬዚዳንት አቶ በቀለ ገርባ፣ የሰማያዊ ፓርቲ የቀድሞው ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ ጋዜጠኞቹ ካሊድ መሃመድ፣ ጌታቸው ሺፈራውና ዳርሰማ ሶሪ እንዲሁም ሌሎች በርካታ የፖለቲካ አመራሮችና አክቲቪስቶች ታስረው የሚገኙበት ነው፡፡

ይህ እስር ቤት በያዝነው አዲስ አመት ዋዜማ (ነሀሴ 2008) ላይ የእሳት ቃጠሎ ደርሶበት እንደነበር ይታወሳል፡፡ በዚህ ቃጠሎ የተነሳ በወቅቱ የተጎዱ ሰዎች ማንነትና መጠን በታሰበው ፍጥነት ቶሎ ሳይገለጽ ቢቆይም የኋላ ኋላ መንግስት በቃጠሎው ወቅት በእሳት ተቃጥለውና ‹ለማምለጥ ሲሞክሩ የተገደሉ› በሚል 23 ሰዎች መሞታቸውን ገልጾ ነበር፡፡

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት ባደረገው ማጣራት በወቅቱ ከተፈጠረው እሳት ቃጠሎ ጋር በተያያዘ በአጠቃላይ 67 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ከእነዚህ ሟቾች ውስጥ በቃጠሎ የሞቱት 22 ሰዎች ሲሆኑ ቀሪዎቹ 45 ሰዎች ‹‹ሊያመልጡ ሞክረዋል›› በሚል በመንግስት ታጣቂዎች (የማ/ቤቱ ጠባቂዎች) የተገደሉ ናቸው፡፡

በወቅቱ ህይወታቸውን ካጡ ተጠርጣሪዎች በተጨማሪ የአካል ጉዳት የደረሰባቸው፣ በጭስ ታፍነው የጤና መታወክ የገጠማቸው በርካቶች ናቸው፡፡ ለአብነትም በእነ ከድር መሃመድ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ቀርቦበት በጊዜ ቀጠሮ ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ ዳርሰማ ሶሪ የመተንፈሻ አካሉ ላይ በገጠመው የጤና መታወክ ህክምና ላይ ይገኛል፡፡

ከቃጠሎው ማግስት

በቂሊንጦ የደረሰውን ቃጠሎ ተከትሎ የእስረኛ ቤተሰብ፣ ዘመድና ጓደኞች ለቀናት የጭንቅ ቀናትን አሳልፈዋል፤ እያሳለፉም ነው፡፡ በወቅቱ በደረሰው ቃጠሎ ወቅት የእስረኞችን በህይወት መኖርና አለመኖር ማረጋገጥ አዳጋች ሆኖ፣ ያለምንም መረጃ ቤተሰብ በየዕለቱ ወደቂሊንጦ ሲንከራተቱ ቆይተዋል፡፡ ይህን በማድረጋቸውም ጭንቅ ላይ የሚገኙ የእስረኛ ቤተሰቦች ላይ ‹ለምን ትጠይቃላችሁ› በሚል ድብደባና እስር ደርሶባቸዋል፡፡

መንግስት በወቅቱ በቂሊንጦ የነበሩ (በህይወት የተረፉትን) እስረኞችን ወደተለያዩ እስር ቤቶች ለማዘዋወር ተገድዷል፡፡ ይህንንም ዘግይቶም ቢሆን ለእስረኛ ቤተሰቦች አሳውቋል፡፡ ሆኖም የእስረኛ ቤተሰቦች ከቃጠሎው ወዲህ የሚደርስባቸው እንግልት አልቆመም፡፡ ከዚህ የከፋው እንግልትና የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየተፈጸመ ያለው ግን በእስረኞች ላይ ነው፡፡
ወደ ዝዋይና ሸዋሮቢት እንዲዘዋወሩ የተደረጉት እስረኞች የተለያዩ የሰብዓዊ ክብርን የሚያዋርድ ተግባር እንደተፈጸመባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ዝዋይ የተዘዋወሩት እስረኞች ለአስር ቀናት ያህል ካቴና ከእጃቸው ሳይፈታ በእስር አሳልፈዋል፡፡ እነዚህ እስረኞች ሁለት፣ ሁለት ሆነው በአንድ ካቴና ታስረው መጸዳጃ ቤት ሲሄዱም፣ ሲመገቡና ሲተኙ ሳይቀር በእስር አንድ ላይ ሆነው እንደነበር ተረጋግጧል፡፡
እስረኞቹ ከምግብ ሌላ ማናቸውም ነገሮች እንዳይገቡላቸው ተከልክለው፣ ጠያቂዎቻቸውን ከ3 ደቂቃ በላይ እንዳያነጋግሩ ተደርገው ሰንብተዋል፡፡ በተለይም እየደረሰ ያለውን ግፍ በተመለከተ የተናገረ ሰው አሸዋ ላይ ራቁቱን ሆኖ ግርፋት ይፈጸምበት ነበር፡፡ አሸዋ ላይ የሚገረፈው እስረኛ ውሃ እየተደፋበት ሰውነቱ አሸዋውን እንዲይዘው ተደርጎ፣ ከዚያም ሰውነቱን እንዳይታጠብ ተገድቦ በስቃይ እንዲቆይ ይደረጋል፡፡ በጠባብ ክፍል ውስጥ በርካታ እስረኞችን በማጨቅ ሰው በሰው ላይ ተደራርቦ እንዲተኛ ተገድዶ ነበር (በተለይ ዝዋይ)፡፡
ሸዋሮቢት የተዘዋወሩትም ቢሆን ተመሳሳይ በደል እንደተፈጸመባቸው ነው ማረጋገጥ የተቻለው፡፡ በዚሁ እስር ቤት የቆይ እስረኞች አንዳንዶቹ ላይ ከፍተኛ ድብደባ ከመፈጸሙ ጋር በተያያዘ ቤተሰብ ሊጠይቃቸው በሄደ ወቅት አንድ ክፍል ውስጥ አስቀምጠው በመስኮት ከወገብ በላይ ብቻ እየታዩ ‹አለሁ› እንዲሉ መገደዳቸውን ከቤተሰቦቻቸው ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡

የእስረኞቹ ወደቂሊንጦ መመለስ
ጥቅምት 2009 ዓ.ም መግቢያ ጀምሮ ወደተለያዩ እስር ቤቶች ተበትነው የነበሩ ተጠርጣሪዎች ወደ ቂሊንጦ መመለስ ጀምረዋል፡፡ ሆኖም ግን የቂሊንጦ ማ/ቤት አስተዳደር እስረኞችን ፍ/ቤት እያቀረበ አይደለም፡፡ ይህ ሪፖርት እስከተዘጋጀበት ዕለት ድረስ እስረኞች በፍ/ቤት ቀጠሯቸው መሰረት ፍ/ቤት ሊያቀርቧቸው አልቻሉም፡፡ ለምሳሌ ጥቅምት 9/2009 ዓ.ም ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት ቀጠሮ የነበራቸው እነ ከድር መሃመድ (20 ሰዎች) እና እነ ትንሳኤ በሪሶ (10) ሰዎች ፍርድ ቤት እንዳልቀረቡ ተረጋግጧል፡፡
ጥቅምት 14/2009 ዓ.ም ቀጠሮ የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬም በተመሳሳይ በቀጠሮው ዕለት ፍ/ቤት አልቀረበም፡፡ ለዚህም ከማ/ቤቱ አስተዳደር ተጠርጣረውን ላለማቅረቡ በቂ ምክንያት ለፍርድ ቤቱ አላቀረበም፡፡

አሁን ላይ ወደ ቂሊንጦ የተመለሱት ታሳሪዎች በአንጻራዊነት የተሻለ ሁኔታ ላይ ናቸው ለማለት ቢቻልም አሁንም ግን የመጠየቂያ ሰዓት ገደብ አለባቸው፡፡ ቢበዛ ለ10 ደቂቃ ብቻ ነው ቤተሰቦቻቸውን እንዲያነጋግሩ የሚፈቀድላቸው፡፡ ከምግብ ሌላ ማናቸውም ነገር እንዲገባላቸው አይፈቀድም፡፡ የጥርስ ሳሙናና ቡርሽ፣ ቫዝሊን፣ በሶ እና የመሳሰሉት አስፈላጊ ነገሮች እንኳ አይገቡላቸውም፡፡

መንግስት እስረኞችን ተጠያቂ ሊያደርግ ስለመሆኑ
የኢትዮጵያ መንግስት በቂሊንጦ ለደረሰው አደጋ እስረኞችን ተጠያቂ በማድረግ ክስ ሊመሰርት መሆኑ ታውቋል፡፡ መንግስት በቁጥር የበዙ እስረኞችን በተጠርጣሪነት ይዞ ምርምመራ በማድረግ ላይ እንደሆነና ምስክሮችንም እያዘጋጀ እንዳለ የታወቀ ሲሆን፣ ተጠርጣሪዎቹ በቂሊንጦ ለደረሰው አደጋና ይህንንም ተከትሎ ለጠፋው የሰው ህይወትና ንብረት ተጠያቂ ናችሁ ሊባሉ እንደሚችሉ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ መንግስት ይህን እያደረገ የሚገኘው የደረሰው ቃጠሎ መንስኤና ቃጠሎውን ተከትሎ የደረሰው ጉዳት በገለልተኛ አካል ተጣርቶ ባልተገለጸበት ሁኔታ ነው፡፡ መንግስታዊው “የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን” ማጣራት አደርጋለሁ ማለቱና በሚቀጥለው ሳምንት ለፓርላማ ሪፓርት አቀርባለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡

(በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት ተዘጋጀ)

Filed in: Amharic