>

ሰደን ፖስት [አንዷለም በዕውቀቱ ገዳ]

(ይህ ፖስት ለማ መገርሳ እና ጓደኞቹ በኢሬቻ በአል ላይ የተፈጁትን “ወገኖቻቸውን” ሞት ምክንያት “ሰደን ዴዝ” ብለው በሃውልቱ ላይ በመጻፋቸው እና በሌሎች አንዳንድ ነገሮች “ኢንስፓየርድ” የሆነ ነው)

ይሄን ፖስት ለመፖሰት በእውነቱ ምንም አይነት ጊዜ አልነበረኝም…ያው ብዙም (ከሳምንት  በላይ )ያላሰብኩበትና ያልተዘጋጀሁበት በቃ አለ አይደል እነ ለማ መገርሳ “ሰደን ዴዝ” የሚሉት አይነት ክስተት ስላጋጠመኝ  የፖሰትኩት ነው  ፡፡
ሰላም ናችሁ ግን ?!
እሺ ለማንኛውም እንዴት መሰላችሁ !?
ያው ጥዋት ሁሌም እንደማደርገው “ሰደንሊ” ወደ ስራ እየሄድኩ ሳለ አንድ ጓደኛዬን መንገድ ላይ አገኘሁት …ሊፍት ሰጥቼው እያወራን እሱም በአጋጣሚ እኔ ወደ ምሄድበት ቦታ “ሰደንሊ” ይሄድ ኖሮ(በእርግጥ አብረን ነው የምንሰራው)  እግረ መንገዳችንን (በእርግጥ በመኪና ነው) ብዙ ነገር እየተጨዋወትን  ሄድን…ስለ ግል ህይወታችን አንድም ቀን አውርተን አናውቅም ነበር….አንድ ቦታ እየሰራን የአምስት አመት ፍቅረኛዬን ሰደንሊ አግብቼ ሰደንሊ  ሁለት ልጆች እንደወለድኩ እስከዛሬ አለማወቁ ግርም አለኝ…..የእርሱ ኑሮ እንኳን ድሮ ካምፓስ ከነበረው ብዙም ባይለወጥም….አራት አመት በካንሰር ሲማቅቁ የኖሩት አባቱ  ባለፈው ሳምንት ከአምስት ወራት የሆስፒታል ቆይታ በኋላ  ሰደንሊ እንደሞቱ ነገረኝ……አባቱን እወዳቸው ስለነበረ ነው መሰለኝ ቢሮ እንደገባሁ ስራ አስጠላኝ …ከዛ ሰደንሊ  “ለምን ፖስት አላደርግም?” የሚል ሃሳብ መጣልኝ…..
የመጀመሪያው ትችት በአሮሚያ ክልል የፌዴራል መንግስት ተወካዮቸን ይመለከታል፡፡እንግዲህ አቶ አለማየሁ አቶምሳ መርዝ በልተው(ወይም አል በልተው)  አምስት አመት ማቀው ማቀው “ሰደንሊ” ከሞቱ እና ወደ ገነት/ሲኦል/ ካመሩ በኋላ አቶ ሙክታር ደግሞ የሙከራ ጊዜያቸውን ባግባቡ ሳያጠናቅቁ ህዝባዊ እምቢተኝነት በመነሳቱ እና የክልሉ የበላይ ጠባቂ የሆነው አቶ ጃዋርም እንዲቀየሩ ስላዘዘ በአሁኑ ሰአት ብሄርተኛ የሚመስሉ (ወይም የሆኑ) ከአቶ አለማየሁ በኋላ “ጠንካራ” የሚባሉ በዛ ላይ መርዝ ያልበሉ ጤነኛ መስተዳድር እነ አቶ አዲሱ አረጋን ይዘው ወደ ፒክቸሩ መጥተዋል፡፡

እኒህ አጭር ሰው በአጭር ግዜ ውስጥ(አቶ ጃዋር እስከፈቀዱላቸው ድረስ) ከፍተኛ ተቀባይነት እያገኙ እንደመጡ አያጠራጥርም….በተለይ በሶሻል ሚዲያ ያላቸው ተቀባይት ከፍተኛ ነው በተለይ ደግሞ  በትጋራዋይ ፖስተኞች እና ብሎገሮች  ማለቴ ነው፡፡ ቃል አቀባያቸው አቶ አዲሱ አረጋ አንዳንዴ የሚጽፉት ነገር በእርግጥ የመንግስት ሃሳብ ይሁን የራሳቸው ቢያጠራጥርም (ይህን አይነት “ፊሊንግ” ድሮ በአቶ ጌታቸው ረዳ ቃል አቀባይነት ዘመን ያጋጥመኝ ነበር) አንዳንዴ ደግሞ የጃዋርን ፖስት ሁላ ሼር ያደረጉ ቢመስለንም  ጅማሮው ጥሩ ነው ብለን እየተከታተልናቸው ቆይተናል……ያው በሲሪየስ ወስደናቸው ሳይሆን እንደ መደበሪያ አሪፍ ናቸው በሚል ነው…..ግን አንዳንዴ ልክ እንደዚህ እንደ በቀደሙ  “ሰደን ዴዝ” አይነት ሰደን ድድብና ሲሰሩ ብሽቅ ያደርገኛል…..ምናልባት “ሰደን” የሚለውን ቃል ካለማወቅ የመጣ ይሆን !? ኦክስፎርድ ዲክሽነሪ ….”ሰደንን” …ሲፈታው
….ሃፕንኒንግ, ካሚንግ ,ኪውክሊ,….ዊዝ አውት ዋርኒንግ…ይለዋል
እስቲ በየትኛው  አረዳድ ነው የኢሬቻው “ማሳከር” “ሰደን ዴዝ” ሊባል የሚችለው ወገን!?…….ምን ሊመጣ እንደሚችል እየታወቀ…. …..የታጠቀ የፖሊስ ሃይል ተሰልፎ ….. ህዝቡ ተቃውሞ እንደሚያሰማ እየታወቀ…….. አረ ተው አታሹፉ!….ከፊታችን አሁንም ሌላ ኢሬቻ አለ …..እንግዲህ ያ ሰደን ዴዝ በድጋሚ ሰደንሊ ለአለመከሰቱ ምን ዋስትናስ አለ?…..ሰው ከሞተ በኋላስ እንደዚህ አይነት የሚያሙ ቃላትን በመጠቀም በቁስሉ ላይ እንጨት ከመስደድ አርፎ መቀመጥስ ማንን ገደለ ጃል…?!

እድሜ ለኦፒዲኦ  በዚህ ሃውልት የተነሳ ደህና የማውቀው የእንግሊዝኛ ቃል ትርጉሙ ተምታታብኝ…..አሁን ሳልፈልግ ወደ …አእምሮዬ እየመጡ ያሉ ቃላት …..የ1896ቱ የአድዋው ሰደን ዴዝ፡ ጣሊያን አመድ ያደረግንበት የዶጋሊው ሰደን ዴዝ፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ወንድማማች ህዝቦች የተሰውበት የባድመው ሰደን ዴዝ፡ ሰላማዊ ህዝብ ያለቀበት የሃውዜኑ ሰደን ዴዝ፡….የ19 14ቱ የመጀመሪው የአለም ሰደን ዴዝ፡ …በጀርመን ቆስቋሽነት የተነሳው ሁለተኛው የአለም ሰደን ዴዝ፡…..አረቦች ያስነሱት የመስቀል ሰደን ዴዝ፡.በሰሜን አሜሪካ በ19 ኛው ክለፍለ ዘመን የተካሄደው የአሜሪካው ሲቪል ሰደን ዴዝ ….ብቻ ብዙ “ሰደን ዴዞች” በሃሳቤ  እየመጡ ነው…..እስቲ እናንተም የምታውቋቸውን “ሰደን ዴዞች” ወዲህ በሉ…..

ሶሪ! ከዚህ በላይ ብጽፍ ደስ ይለኝ ነበር…ነገርግን ባለፉት ሶስት ሳምንታት ስሰጥ የነበረው ስልጠና በመደበኛ ሰአቱ ሰደንሊ  5፡00 ላይ ስለሚጀምር ልለያችሁ ነው፡፡

ይ መ ቻ ች ሁ

Filed in: Amharic