>

በአዲስ አበባ ላይ የልዮ ተጠቃሚነት መብት ድንጋጌ ይዘት እና አንድምታው

መንበሩ ከመሃል አራዳ

ወያኔዎች ስልጣን ላይ በቆዩባቸው አመታት ያጋጠማቸውን ፈተና ከሚወጡባቸው ስልቶ አንዱ፣ አዲስ አጀንዳ ፈጥሮ የፖለቲካ ተቃወሞውን ትኩረት ማስቀየር ነው። የሚገርመው ነገር ይህ ዘዴ የስርዓቱን አድሜ በማስቀጠል ስኬት ብቻ ሳይወሰን ፣በግራም በቀኝም ያለው የተቃዋሚ ወገን፣ መሰረታዊውን የስርዓት ለውጥ ጥያቄውን ረስቶ፣ ሙሉ ቀልቡን ወያኔ በተወረወረለት አጀንዳ ላይ በመራኮት፣ እርስ በርስ እየተባላ የትግል ግዜውን ያባክናል። ባለፈው አንድ ዓመት መጠነ ሰፊ የህዝብ ተቃወሞ ያደናገጠው ወያኔ፣ ለመሰረታዊው ጥያቄ መልስ ሳይሰጥ፣ በልዩ ጥቅም መብት ሽፋን አዲስ የማደናገሪያ አጀንዳ ይዞ ብቅ ብሎአል።ለእሩብ ክፍለ ዘመን ያህል ሲሰራበት የነበረውን የከፋፍለህ ግዛው ስልት ያልተገለጸላቸው አንዳንድ ጽንፈኛ ወገኖች (ethno-chauvinist) ከወያኔ የተወረወረውን አቅጣጫ ማስቀየርያ አጀንዳ በመቀበል፣ ከስርዓቱ የበለጠ በማስተጋባት ላይ ይገኛሉ።

በህዝቦች እኩልነት እና መፈቃቀር ላይ የተመሰረተ የጋራ ማህበረሰብ እንገነባለን ከሚለው ሰብከትን ለተመለከተ፣ በተቃራኒ እንዲህ አይነት ቁርሾ ቆስቋሽ ድርጊት ጋር እንዴት እንደሚጣረስ ማን በነገራቸው። የዚህ የእብደት ጉዞ መዳረሻው ሌላ ምንም ሳይሆን እልቂት ብቻ ነው፡፡ ትላንት በዳር ሃገር የተፈጸመው ግፍ አልበቃ ብሎ፣ዛሬ በመሃል ሃገር ለመድገም የመወራጨት ምን የሚሉት ብልግና እንደሆነ እናንተው መልሱ። የአዲስ አበባን ወደ ኦሮሚያ መስፋፋትን አምርረው ሲቃወሙ የነበሩ “ጥቂት የኦሮሞ-አክቲቪስቶች”፣(militant oromo ethno chauvinist ) የንጹሃን ደም ከፈሰሰ ዓመት በሁዋላ ከተማዋ ራሷ የእኛ ነች በሚል መፈክር ዙሪያ መንቀሳቀሳቸው ምን ያህል አላማ የለሽ እንደሆኑ አመላካች ነው፡፡

የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ ያለውን ልዩ የተጠቃሚነት መብት ለመደንገግ ተረቀቀ የተባለው አዋጅ ለአዲስ አበባም ሆነ ኦሮሚያ ለሚባለው ክልል፣ እንዲሁም በጠቅላላ የሃገሪቱ ህልውና ላይ የሚኖረው አሉታዊ እንደምታ ቀላል እንደማይሆን ከወዲሁ መናገር ይቻላል።

ሲጀመር ረቂቅ አዋጁ ከአምስት ሚልዮን በላይ የሚገመተውን የአዲስ አበባ ነዋሪን መብት አልባ ያደረገ ብቻ ሳይሆን እንደሌለ በመቁጠር ህልውናውን የካደ ነው።በነገራችን ላይ አምስት ሚልዮን የህዝብ ቁጥር፣ የአንድ ሉአላዊ ሃገር ህዝብ መሆን ይችላል።በመቀጠል ከተማውን አዲስ አበባ ያሰኙ ታሪካዊ፣ባህላዊ፣ኢኮኖሚያዊ እና ስነ- ሰብዓዊ ሁኔታዎች መኖራቸውን ከግምት ውስጥ ያላስገባ አንዳንድ ጠባብ ብሄረተኞች መርቅነው ባነሱት የመሬት ይገባኛል ጥያቄ ላይ የተመሰረተ ነው።በደምሳሳው የአዋጁ መነሻ መንፈስ ከተማውን ሰው-አልባ (no-mansland ) ባዶ የሆነ መሬት እንደሆነ በመቁጠር የተረቀቀ እንደሆነ መናገር ይቻላል። ሌላው የአዋጁ መንፈስ በከተማው ውስጥ ባለሁለት ደረጃ ዜግነት ለመፍጠር ያለመ ዘረኛ እና አግላይ ነው።ሰወች በአንድ ሃገር ዜጎች በመሆናቸው ብቻ ማግኘት የሚገባቸውን መብት እና ጥቅም፣ ለዚህኛው ብሄር ልዩ የሆነ የተጠቃሚነት መብት ይሰጠው ብሎ በአዋጅ መደንገግ፣ መብትን ከአንዱ ነጥቆ (Disposseing ) ለሌላለው የመስጠት ጸረ-እኩልነት ድንጋጌ ነው። 2 የዚህ ልዩ ጠጠቃሚነት መብት ጉዳይ ወደ ሃገራችን ፖለቲካ የገባው የደርግ መንግስት ወድቆ ህወሃት ከኦሮሞ ነጻነት ግንባር ጋር በአጋርነት በፈጠረው የድህረ-ደርግ አዲስ የፖለቲካ አሰላለፍ (Post-Derg New political arrangement ) መሰረት ነው። አላማው ህወሃት በመሃል ሃገር ሊነሳበት ይችላል ብሎ የገመተውን ተቃወሞ ለማዳከም፣ ከኦሮሞ ነጻነት ግንባር ጋር ስልታዊ አጋርነት (tactical alliance ) በመፍጠር ስልጣኑን ማረጋጋት ነበር።

በዚህ የፖለቲካ ስሌት መነሻነት ነው፣ ዛሬ በሃገራችን የሚሰራበትን የክልል አወቃቀር በሁለቱ የብሄር ነጻ አውጪዎች መሃከል በተደረገ ድርድር (ፖለቲካዊ ሰጥቶ መቀበል) የተቀረጸ መሆኑን ግምት ውስጥ ማስገባት ይገባል። የሚገርመው ነገር ከ80 በላይ ብሄር እና ብሄረሰብ ባለበ ሃገር ውስጥ፣ የተፈጸመው ይህ አግላይ ስምምነት ኢ-ዲሞክራሲያዊ ብቻ ሳይሆን፣ በሃገራችን እየተከሰቱ ላሉ የጎሳ ግጭቶች መነሻ ምክንያት ሆኖአል። በዚህ ስምምነት ህወሃት የትግራይን ክልል ከተከዜ አሻግሮ የወልቃይትን እና የሰሜን ወሎ ወረዳዎችን መጠቅለል ቻለ። በተቀረው የኢትዮጵያ ክፍል ላይ ኦነግ ያቀረበው የግዛት ይገባኛል ጥያቄ ተግባራዊ ተደረገ።በሂደቱ የአዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ይካተትልኝ የሚለው የኦነግ ጥያቄ አወዛግቦ እንደነበረ በወቅቱ የነበሩ ሰዎች ያስታውሳሉ። ህወሃት ከኦነግ ጋር የፈጠረውን ስልታዊ አጋርነት ላለመጉዳት በአዲስ አበባ ላይ የኦሮሞ ክልል ልዮ መብትን በተመለከተ ወደፊት በህግ ይደነገጋል በማለት እንዲታለፍ ተደረገ።ከዓመት በኋላ ስልጣኑን በመሃል ሃገር ያረጋጋው (power consolidate) ህወሃት፣ ኦነግን ከጨዋታ ውጪ በማድረግ ብቸኛ ተሃገሪቱ ገዠ ለመሆን ሲበቃ የልዩ መብት ጉዳይ ወደ ጎን እንዲገፋ ተደረገ። የሚገርመው በዚህ ሁሉ ድርድር ውስጥ የአዲስ አበባም ሆነ የተቀረው የሃገሪቱ ህዝብ የተጠየቀውም ሆነ የሚያውቀው ነገር አለመኖሩ ነው።እንግዲህ ከዛ ወዲህ ነው ወደ አምስት ሚልዮን የሚጠጋው የአዲስ አበባ ነዋሪ መሪዎቹን መምረጥ እንዳይችል በእጅ አዙር የህግ ክልከላ ውስጥ የሚገኘው።

እዚህ ጋር መነሳት ያለበት ሌላ ጥያቄ በእርግጥ ኢትዮጵያ የሁላችንም ሃገር ሆና ሳለች፣ ሁለት ጽንፈኛ የብሄር ነጻ አውጪዎች የሁላችንንም እጣ በሚወስን ጉዳይ ላይ የመወሰን መብት (ከጉልበት በስተቀር) እንዴት ሊኖራቸው ቻለ።ከህግ፣ከሞራል እና ከታሪክ አንጻር ተቀባይነቱ እስከምን ድረስ ይሆናል?፣ በሚሉ ጉዳዮች ዙሪያ ብዙ መልስ ማግኘት ያለባቸው ጥያቄ ስላሉ፣እራሱን በቻለ ሌላ ርእስ መዳሰስ ያለበት ሰለሆነ እዚህ ጋር ገታ አድርገን ወደተነሳንበት የአዲስ አበባ ጉዳይ እንመለስ።

አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ከሆነች 130 ዓመታት አስቆጥራለች።በዚህ ከአንድ ክፍለዘመን በላይ ጉዞ ከተማዋ ብዙ ወጣ ውረድ እና ስኬቶችን አስመዝግባለች።እንደማንኛውም የዓለም ከተማ አዲስ አበባ ከነበረችበት ትንሽ መንደርነት፣ወደ ትልቅ ዓለም አቀፍ ከተማነት የማደግ ግስጋሴዋን ቀጥላለች።የዛሬ መቶ ሰላሳ ዓመት በፊት ከነበረችበት በተለየ የራሷ ባህል፣ ቋንቋ እና ስነ-ልቦና በማዳበር የኢትዮጵያ ሃገራዊ ፕሮጀክት ነጸብራቅ ሆናለች። የኢትዮጵያ ርእሰ ከተማ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ ዲፕሎማሲያዊ ማእከልነቷ ባጎናጸፋት እድል የተነሳ ከተማዋ ዓለም አቀፍ ይዘትን በመላበስ ላይ ነች።

ከዚህ ሁሉ ጉዞ በሁዋላ፣ እዚህ ላይ የደረሰችውን የከተማ እድገት ነው፣ የዛሬዎቹ ጽንፈኛ ጠባብ ብሄረተኞች (militant oromo ethno chauvinist) ጉዞዋን የሁዋሊዮሽ በመመለስ ወደ ጎጥ መንደርነት ለመመለስ እየታተሩ የሚገኙት።እዚህ ላይ ህወሃታውያን እና ኦነጋውያን እንዲህ ባሉ ጉዳዮች ላይ ተደጋግፈው የመሄድ ብዙ ልምድ እንዳላቸው ማስተዋል ይገባል። የዚህ ምክንያት አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ሃገራዊ ፕሮጀክት ራእይ መፈጸሚያ በመሆንዋ፣ጽንፈኛ ጠባብ ብሄረተኞች ዋነኛ የጥቃት ኢላማቸው በማድረግ ሊያከስሟት እየሰሩ ነው። ይህ 3 ድርጊታቸውም በከተማዋ ውስጥ የሚንጸባረቀው ህብረ ብሄራዊነት ( multi-cultural cosmopolitanism) ላይ የተቃጣ አደጋም ነው። ሰለዚህም ነው፣ በሰልጣን ላይ ያለው ህወሃት፣ጠባብ የኦሮሞ ብሄረተኞችን ከፈለገ ያስፈራራቸዋል፣ወይንም ያስፈራራባቸዋል።

አክራሪ የኦሮሞ ብሄረተኞች (militant oromo ethno-chauvinists) በወያኔ ተረቆ የቀረበውን ድንጋጌ እንደወረደ ከመቀበል አልፈው፣ያንሰናል ይጨመርልን በማለት የሚያነሷቸውን ክርክሮች ላየ ዘረኝነት በሃገራችን ላይ እየጋረጠ ያለውን አደጋ መገንዘብ ይችላል።አዲስ አበባ የከተመችበት መሬት የኦሮሞ ተፈጥሮአዊ ግዛት ነው፣ የሚለው መነሻ በራሱ አሳፋሪ እና አንገት የሚያስደፋ አስተሰሳሰብ ነው። በሰው ልጆች ማህበረሰብ እድገት ታሪክ ህዝቦች ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በመዘዋወር ህይወታቸውን ይገፉ እንደነበር እንረዳለን።አንድ ህዝብ በተፈጥሮም ሆነ ሰው ሰራሽ ችግር ምክንያት ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ተዘዋውሮ መኖሩ ያለ እና የነበረ ነው።

የኦሮሞ ህዝብ ታሪክም ከዚህ የተለየ አልነበረም። በተለይ ከ15ኛው ክፍለዘመን ወዲህ የአርብቶ አደር የአኗኗር ዘይቤ ይከተል የነበረው የኦሮሞ ማህበረሰብ በተከታታይ 8 ገዳዎች ባደረገው መስፋፋት፣ ከባሌ ጫፍ ተነስቶ ወደ ሰሜን እና ምዕራብ ኢትዮጵያ ተሰራጭቶ መኖር እንደጀመረ በታሪክ እና አርኪዮሎጂ መረጃዎች ጭምር የተረጋገጠ ሃቅ ነው።በዚህ መነሻነት ዛሬ የምንኖርባት ኢትዮጵያ ላይ ሰፍረን የምንገኝ ህዝቦች ሁላችንም መጤ ልንባል የምንችል እንጂ አንዱ ነባር፣ሌላውን መጤ የሚያደርግ ምንም ሰማያዊ ሆነ ምድራዊ ማስረጃ የለም።

አንደ አፓርታይድ አይነት ስርዓት ካልሆነ፣ ለመሆኑ በየትኛው የዓለም ክፍል ነው፣ አንድን ህዝብ ነጥሎ የልዩ መብት ተጠቃሚ የሚያደርግ አዋጅ ሲደነገግ ትክክል ተደርጎ የሚወሰደው።ኦሮሚኛ ተጨማሪ የስራ ቋዋንቋ መሆኑ ላይ የተነሳ ተቃወሞ አስካሁን አላጋጠመኝም፣ ቢሆን መልካም እርምጃ እንጂ የሚከፋ ወገን የለም።ይሁን እና የሌሎችን መብት ደፍጥጠን በልዩ መብት ስም የእኛን የበላይነት እንጭናለን የሚለው አስተሳሰብ ጤነኝነት ሊፈሽ ይገባል።

የአዋጁን መውጣት ተከትሎ ጥቂት በሚባሉ አክራሪ የኦሮሞ ብሄረተኞች (militant oromo ethno-chauvinists) የተንጸባረቀው ሃሳብ የአዲስ አበባ ህዝብ ይህን ባይቀበል የሚጠጣውን ውሃ እናቆምበታለን፣አምስቱምን የከተማይቱ በሮች ዘግተን ምግብ እንዳይወጣ እና እንዳይገባ በማድረግ እናምበረክከዋለን የሚሉ እንደነበሩ ታዝበናል።ይህ አይነት አክራሪ አስተሳሰብ በዩገኦስላቪያ የተከሰተውን እልቂት የሚያስታውሰን ሲሆን፣አዲስ አበባንም የአፍሪካዋ ሳራየቮ በማድረግ የሚጠናቀቅ እንደሚሆን ካሁኑ መተንበይ ይቻላል፡፡ ወደ አዋጁ ስንመለስ ግልጽነት ጎደለው በብዙ አሻሚ አንቀጾችን የታጀለ እና ወደፊት ለሚነሱ ውዝግቦች በር የከፈተ እንደሆነ ገና ከአሁኑ የህግ ባለሙያዎች አስተያየታቸውን መስጠት ጀምረዋል።ልዮ መብት የሚለው የህግ ሃረግ በራሱ የሚፈጥራቸው ለትርጉም አሻሚ የሆኑ ውዝግቦች የበዙ ናቸው።

የዚህ ሁሉ አዋጅ እና ልዮ-መብት ጥቅም እንድምታው ስንመለከት ትላንት በዳር ሃገር ሲፈጸም የነበረውን ብሄርን መሰረት ያደረገ እንግልት እና ማፈናቀል በመሃል ሀገር ለመድገም ነው። የማስታዎስ አቅማችን ካልደከመ በስተቀር፣ ከዛሬ 25 ዓመት ጅምሮ በሃረር-በደኖ፣አርሲ-አርባጉጉ፣ወለጋ-ጊዳኪራሞ፣ጋሙ-ጎፋ ቤንችማጂ የመሳሰሉ ቦታዎች መጤ እና ነፍጠኛ ሰፋሪ ተብለው የተፈናቀሉ ወገኖች ስፍር ቁጥር የላቸውም። አውሮፓ እና አሜሪካ በጥገኝነት እየኖሩ፣በዚህ ክልል የሚኖሩ የሌላ ብሄር ተወላጆች መጤ ሰለሆኑ ይውጡልን ወይንም ሁለተኛ ደረጃ ዜግነታቸውን ተቀብለው ይኑሩ ማለታቸውን መስማት ምጸት ነው።በተለይ ባሳለፍናቸው 25ዓመታት ኦሮሚያ 4 በሚባለው ክልል ነዋሪ የነበሩ ኦሮሞ ባልሆኑ ሌሎች የሃገራችን ዜጎች ላይ የደረሰው በደል እና የተፈጸመው ግፍ ከብዙዎቻችን ህሊና ባልጠፋበት ሁኔታ፣ድርጊቱን በአዲስ አበባ ለመድገም ዳርዳርታው ነቅተን እንድንጠብቅ ይገበባል።

ሃገራችን የባህር በር አጣች፣ ድንብሯ ተደፈረ ወዘተ.. ሰንል፣ዛሬ ዋና ከተማዋን የማጣት አደጋ ውስጥ የገባችበት ሁኔታ ውስጥ ትገኛለች።ስልጣን ካጣን አባልተናችሁ፣አዲስ አበባንም ለኦሮሞ ሰጥተን ወደትግራይ እንሄዳለን የሚለው የወያኔ ዛቻ መፈጸሚያው ቀን የደረሰ ይመስላል።

ለማጠቃለል በአንድ በኩል ህዝባዊ ተቀባይነቱን ያጣ መንግስት እና በሌላ በኩል በዘር ፖለቲካ ሰክረው ዘረኝነትን እንደ እኩልነት መብት በመውሰድ ኢትዩጵያን እና የአፍሪካ ቀንድ አካባቢን አተራማሸ የሆነ አጀንዳ በመግፋት ላይ ያሉ አንዳንድ ጽንፈኛ የኦሮሞ ፖለቲከኞች ቆም ብለው እንዲያስቡ ይመከራሉ። ህግም ሆነ ሌላ የፖለቲካ ስምምነት መደረግ ያለበት ጥቂት ጠባብ ብሄረተኞች በሚያቀርቡት የመሬት ይገባኛል ጥያቄ ላይ ተመስርቶ ሳይሆን፣ የሚመለከተው ነዋሪ ህዝብ አውቆት እና ተወያይቶበት መሆን አለበት።ይህ ባልሆነበት እና አንዱን ለመጥቀም ሌላውን ለመጉዳት (Disposseing) መነሻ በማድረግ የሚወጣ ህግ ፖለቲካዊ እንድምታው ከኢትዮጵያ አልፎ ለታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የሚተርፍ መዘዝ እንዳለው መገንዘብ አስተዋይነት ነው።


መንበሩ ከመሃል አራዳ

Filed in: Amharic