>
5:13 pm - Thursday April 20, 2428

ስለራስ መብት መሠለፍ [በዘላለም ክብረት]

Zelalem Kibret (Kilinto)አምስት ዓመት ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ከአንድ ኢትዮጵያዊ አማካኝ ዕድሜ ወደ አንድ አስረኛ ገደማ መሆኑ ነው፡፡ የሕይወትን አንድ አስረኛ ዕድሜ ከሚመስሉ ወዳጆች ጋር ለአንድ ‹‹መልካም ነው›› ብዬ ለማስበው ተግባር መሰለፍ ዕድልም፤ ዕዳም ነው፡፡ የውጥኑ መሳካት ዕድሉ ሲሆን፤ መክሸፉ ደግሞ ዕዳው ነው፡፡ በተለይ እንደኛ አገር መንግሰት ዜጎቹን ‹‹እኔኑ ካልመሰላችሁ›› እያለ በሚያሳድድበት አገር፤ ትንንሽ የደቦ ውጥኖች ሲከሽፉ እያየ ላደገ ሰው የመክሸፍ ስጋት ጋር ሁሌም መኖር የዕየለት እውነታ ነው፡፡

ዞን ዘጠኝን ስንመሰረት ሁሉም የሚሰጋው የመሳደድ፣ የመታሰር፣ ሲብስም ከፍ ያለው ሞት ድረስ የሚያስኬድ መንገድ እንደጀመርን እኔን ጨምሮ የአብዛኞቻችን ስሜት ነበር፡፡ ስጋቱን ሁሉ የሚያጠፋ አንድ መሰረታዊ ጥያቄ ሁሌም ራሴን በመጠየቅ ግን ስጋትን አባርር ነበር፤ ‹‹ሌሎች ሰዎች ለፍተው ባስረከቡኝ ዓለም እንዲሁ ኖሬ መሞት እንዴት ይቻለኛል?›› የምትል ጥያቄ፡፡ ለዚህ ጥያቄ አጭሩ መልስ፤

‹‹እኔም የድርሻዬን መሞከር አለብኝ›› የሚል የሁልጊዜም ሐሳብ ነው፡፡

ይህ ማለት ያለውን ፈተና ማቃለል አይደለም፡፡

ዞን ዘጠኝ ከአምስት ዓመታት በፊት ሲመሰረት የነበረው የነፃ ሐሳብ ገበያ ከሦስት ዓመታት በፊት ለእስርና ስደት ስንዳረግ ከነበረው ገበያ በእጅጉ የተሻለ፣ እንዲሁም ሰፊና ርካሽ ነበር፡፡ ከሦስት ዓመታት በፊት በታሰርንበት እና ለስደት በተዳረግንበት ወቅት የነበረው የአገራችን የሐሳብ ገበያ ዛሬ ካለው (አለ ከተባለ) የሐሳብ ገበያ እጅግ ርካሽና ሸማችን የማይጎዳ ነበር፡፡ እያንዳንዱ አዲስ ቀናት የበለጠ ጭቆናን እና የበለጠ ስጋትን ይዘው የሚመጡ እንደሆኑ ማየት የአምስት ዓመታት ትዝብት ነበር፡፡ በዋናነት በስርዓቱ ፍፁም የስልጣን ቀናኢነትና ‹‹የሚቃወመኝ አይኑር›› ባይነት፤ ማሕበራዊ ሚዲያዎች ለሁሉም ሰው እኩል የጋራ ዕድል የሚፈጥሩ የሐሳብ ገበያ ሕግ (rules of engagement) የማይገዛቸው መድረኮች በመሆናቸው ምክንያት፤ እንዲሁም የማሕበራዊ ድረ ገፆች ተጠቃሚዎች ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ መምጣት ማሕበራዊ ድረ ገፆች የሚታሰበውን ያክል የገንቢ ውይይት መድረኮች እንዳይኖሩ አድርጓቸዋል ብል ይህ ድምዳሜ የእኔ ብቻ እንዳልሆነ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ነገር ግን እንደኛ ላለ ሁሉም ነገር በአንድ ፓርቲ ቁጥጥር ስር ለሚዳክር አገር፤ ሐሳብ ያለው ሁሉ ወጥቶ ሐሳቡን የሚሸጥበት፤ እንዲሁም ከገበያ ያገኝውን የሚገዛበት ትንሽ ቀዳዳም መገኝቱ ደግሞ ትልቅ ዕድል ነው፡፡

ዞን ዘጠኝ በስርዓቱ የተከፈተችለትን ትንሽ ቀዳዳ ትንሽ የተደራጀ በሚመስል መልኩ፤ መሪ እና ተመሪ የሌለበት መዋቅር በመጠቀም ሐሳብን ለገበያ ለማቅረብ የተደረገ ትንሽ፤ ነገር ግን የሚያድግ ሙከራ ነው፡፡ ሁላችንም የምንጽፍበት ምክንያት ብዙና የተለያየ ነው፡፡ እኛ ያገኝነውን እድል ያላገኙ ዜጎች ወደፊት እንዲመጡ ለማስቻል የሚጽፍ ይኖራል፤ የመጻፍ ሱሳችንን ለማብረድ የምንጽፍ እንኖራለን ወዘተ፡፡ በዚህ ሁሉ ጊዜ ከማንም ምንም ሳንጠብቅ በበጎ ገብነት (voluntarily) መስራታችን ትልቁ ስኬት አድርጌ እወስደዋለሁ፡፡ ለገዥው ሥርዓት የራሱን ሕገ መንግስት እንዲከብር ነበር ዋነኛ ጥያቄያችንና የሥራዎቻችን መሰረት፡፡ ማንኛውም የፖለቲካ ድምፅ ራሱን በሰከነና በሚያግባባ ሁኔታ ይገልፅ ዘንድ ፍላጎታችን ነበር/ነውም፡፡

በዚህ ሁሉ ጊዜ ከመንገድ ላይ ታፍኖ ከመደብደብ ጀምሮ ራሳችንን ሳንሱር እንድናደርግ በመንግስት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ሲዛትብን ‹‹ይህችም ሥራ ተብላ ሊያስሩን? አያደርጉትም›› በሚል የራስ ሽንገላና ቸልተኝነት አልፈናል፡፡

‹‹ግን መጻፉ ምን ይጠቅማል?››

የብዙ ሰዎች ጥያቄ ነው፡፡ በተለይም መፃፍ ጦስ ይዞ በሚመጣበት በእኛ አይነት ያልታደለ አገር ይህ ጥያቄ አሁንም አሁንም መላልሶ የሚነሳ ነው፡፡ ብዙ መልስ ከብዙ አቅጣጫ መምጣቱም ያየነው የታዘብነው እውነት ነው፡፡ ‹‹የምጽፈው የድምፅ አልባው ሕዝብ ልሳን ለመሆን ነው›› ሲባል በብዛት እሰማለሁ/አነባለሁ፡፡ ይህ ግን ራስን የሕዝብ ተጠሪ አድርጎ መሾም ከመሆኑም ባለፈ፤ አሩንዳቲ ሮይ እንደምትለን “እንዳይናገር የተሸበበ እንጅ ድምፅ አልባ የሚባል ሕዝብ በሌለበት – ‘There’s really no such thing as the ‘voiceless’. There are only the deliberately silenced, or the preferably unheard”፤ የሌለውን ለመወከል መሞከር ነው የሚሆነው፡፡ ለእኔ የመጦመር/መፃፌ ዋነኛ መነሻ የራሴው ድምጽ መታፈኑ ነው፡፡ በሌላ አባባል የምጽፈው ለሁለት መሰረታዊ ምክንያቶች ነው፡፡ የመጀመሪያው ሳይኮሎጅስቶች ‘Therapeutic Writing’ ከሚሉት ጋር የተቀራረበ፤ ነገር ግን ይሄኛው ራስን በራስ የማከም ሒደት ነው፡፡ የውስጤን የመታፈን ሕመም በመጻፍ የማክምበት፡፡ ሁለተኛውና ዋነኛው ምክንያቴ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዝነኛ እየሆነ ከመጣው ‘Write for Right’ ጋር የተቀራረበ ምከንያት ነው፡፡ ስለመብት መፃፍ፡፡ ስለራሴ መብት፡፡ ሁለቱን አያይዤ ስጠቀልለው ስለራሴ መብት በመጻፍ ራሴን ማከም የመጻፌ ዋነኛ መግፍኤ ነው፡፡

ስለ መብት መጻፍ

‹‹መብት›› በጣም በተደጋጋሚ የሚነገርለት የሚጻፍለት ጉዳይ ነው፡፡ አማርኛው (ከሳቴ ብርሃን መዝገበ ቃላት) መብትን ‹‹ሙሉ የትዕዛዝ ሥልጣን፣ ሙሉ ሹመት ሙሉ ሥልጣን፣ ተሹሞ ማዘዝ ከኹሉ በላይ መሠልጠን›› ብሎ ነገሩን ወደሌላ ይወስደዋል፡፡ እኔ መብት እያልኩ ስጽፍና ስኖር በራሴ ላይ መሰልጠኑን ማለቴ ነው፡፡ በራሴ ፍላጎት ላይ “Your liberty to swing your fist ends just where my nose begins” በሚሉት ብሒል ላይ ተመስርቼ፤ የማንንም አፍንጫ ሳልነካ እጄን መዘርጋቱን ነው ‹መብት› ብዬ የምጽፍለት፤ የምኖርበት፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እዚህ ላይ ነው መንግስት ጣልቃ ገብቶ ‹‹መብትህን እኔ ሰፍሬ ካልሰጠውህ›› የሚለው፡፡

በእስር ወቅት ለምርመራ ተጠርቼ በቀረብኩበት የመጀመሪያው ቀን አንዲት መርማሪ ‹‹መብት ››የሚባለው ጉዳይ ምን ድረስ እንደሆነ ያ(ስ)ረዱኝን መጥቀሱ እዚህ ላይ ተገቢ ነው፡፡ መርማሪዋ፤ ‹‹ስማ አንተ አንድ ግለሰብ ነህ፡፡ ይሄን ማወቅ ይኖርብሃል፡፡ እኛ የሰማኒያ ሚሊዮን ሕዝብ ደሕንነት ነው የሚያሳስበን፡፡ ለሰማኒያ ሚሊዮኑ ሕዝባችን ሲባል የአንተ የአንድ ሰው መበት መጣስ የሚያሳስበን ጉዳይ እንዳይመስልህ፡፡ ማድረግ ያለብንን ሁሉ ልናደርግ እንችላለን፡፡›› አሉኝ፡፡ ከባድ ዛቻ ነው፡፡ ግን ደግሞ መንግስት ስለዜጎቹ ምን እንደሚያስብ ገላጭ እውነት፡፡ እንግዲህ ስለመብት መጻፍ ያልኩት ይሄኑ ነው፡፡ ሰው በመሆኔ ያገኝሁትን ክብር (privilege) ራሱን ‹‹የሌሎች መብት አስከባሪ ነኝ›› ብሎ ከሾመ ቀማኛ ለመጠበቅ መጻፍ፡፡ ሰው በመሆኔ ብቻ ያገኝሁትን መብት ማንም የማንንም ደህንነት ለማስጠበቅ በሚል ምክንያት አይንጠቀኝ ነው የመጻፌ መነሻና መድረሻ፡፡

ነገር ግን ቀላል ቢመስልም፤ ስለመብት መጻፍ ከብዙ አቅጣጫ ይፈትናል፡፡ የእስር ቤት ወዳጆቻችን እያሾፉ ‹‹ጦማሪ ነኝ እያላችሁ ከግድግዳ ጋር ከምትላተሙ፤ ለምን እንደ ሰው አፏግራችሁ (ተቅለስልሳችሁ እንደማለት ነው) አትኖሩም? ምን አደከማችሁ?›› ከሚሉት ጀምሮ፤ ‹‹የጻፈ ሁሉ ከጀርባው ተልዕኮ አንግቧል›› እያለ በእየዕለቱ ደንብሮ እስከሚያስደነብረው መንግስት ድረስ በየደረጃው የመጻፍን ሐጢያትነት በክፉና በበጎ የሚነግሩ በዙሪያችን ብዙ ናቸው፡፡ ነገር ግን ጭቆናና ግፍ የሕይወታችን አካል ሁኗልና እሱን ተቃውመን መጻፍ አማራጭ ያላገኝንለት መንገድ ነው፡፡ መንገዱ የት እንደሚያደርሰን ማየት ደግሞ ለጊዜ የተሰጠ የቤት ሥራ ነው፡፡

ምንጭ:-
http://www.zoneniners.com/2017/05/blog-post_85.html
Filed in: Amharic