>
5:13 pm - Monday April 20, 1733

በዘ-ህወሀት የውሸት ምድር የማወንበጃ መረጃ ዘመቻ፡ ቀጣፊው በኢትዮጵያ ዉሸትን እዉነት ነው እያለ ሲሰብክ? [ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

የጸሐፊው ማስታዋሻ፡ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ውስጥ እየተጠናከረ የመጣውን የዘ-ህወሀት (ዘራፊ ህወሀት) የመረጃ ማወናበጃ ዘመቻ ለማጋለጥ ሲባል በተከታታይ እያቀረብኩ ካለሁት ትችት ይህ ሶስተኛው ክፍል ነው፡፡ እ.ኤ.አ መስከረም 5/2016 አቅርቤው በነበረው ትችት በኢትዮጵያ ውስጥ ተንሰራፍቶ የሚገኘውን የዘ-ህወሀትን የጭቆና አገዛዝ በመቃወም እየተስፋፋ እና እየተጠናከረ የመጣውን ሕዝባዊ የእምቢተኝነት አመጽ አሳንሶ እና አኮስሶ ለማቅረብ በሚል እኩይ ምግባር ዘ-ህወሀት በቅርብ ጊዜ ውስጥ የመረጃ ማወናበጃ ዘመቻውን ይጀምራል በማለት አሳስቤ ነበር፡፡

እ.ኤ.አ መስከረም 18/2016 አቅርቤው በነበረው ሁለተኛው ትችቴ ዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ ውስጥ አስፈሪ እና የማይቀር የዘር ማጥፋት ዘመቻ እውን ይሆናል በማለት አቅርቦት የነበረውን የቅጥፈት የመረጃ ማወናበጃ ዘመቻ መሰሪ ፕሮፓጋንዳ ሀሰት እና ተራ ቅጥፈት መሆኑን አጋልጫለሁ፡፡

በመስከረም መጀመሪያዎቹ አካባቢ አቅርቤው የነበረው የዘ-ህወሀት የመረጃ ማወናበጃ ዘመቻ በአሁኑ ጊዜ ተጠናክሮ በመቀጠል ላይ እና በተሟላ ቁመና ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ ትችቴ ደግሞ የዘ-ህወሀት ዋና የመረጃ ማወናበጃ ቆሮ/ዋና ኃላፊ (መማቆ) የሆነውን የደብረጽዮን ገብረሚካኤልን የተዛባ እና መሳቂያ የሆነ የቅጥፈት ፕሮፓጋንዳ በማጋለጥ አቀርባለሁ፡፡ “እራሱን በራሱ ዉሸት ካሳመነ ሰው ጋር በፍጹም አትከራከር“ የሚለውን ጥንታዊ አባባል በሚገባ እገነዘባለሁ፡፡ ጭራ የቀራቸዉን ቀጣፊ ውሸታሞች በፍርድ ቤት በፍትሕ አደባባይ በመስቀለኛ ጥያቄ ማፋጠጡን የምመርጥ ቢሆንም ቅሉ ያ የፍትሕ አደባባይ የሚለው ነገር በሀገሪቱ ውስጥ ከቶውንም የሌለ እና ዳብዛው የጠፋ በመሆኑ ምክንያት በዓለም ህዝብ ህሊና ዳኝነት ክርክሬን ቀጥላለሁ።

በእኔ ዘመን ሳሙና የሆኑ አእምሮአቸው በዉሸት የተበከለ ቀጣፊዎችን  አጋጥመዉኛል፡፡ እናም አንድ ቁልጭ ያለ እና በግልጽ የማስታውሰው ነገር ቢኖር እነዚህ አእምሮአቸው የታመመ ቀጣፊዎች እራሳቸዉን  እንጂ ሌላ ሰው ስያታለሉ አላየሁም፡፡ ይልቁንም እነርሱ የቅጥፈት ባለሞያዎች የሆኑት እራሳቸውን በማታለል ነው፡፡ ሆኖም ግን ውሸት በሚነሳበት ጊዜ የመረጃ ማወናበጃ ቆሮ (መማቆ) የሆነው ደብረጽዮን እና ሌሎች የዘ-ህወሀት ወሮበሎች የአንበሳውን ድርሻ ይይዛሉ፡፡ እነዚህ ፍጡሮች የውሸት፣ የቅጥፈት እና የተራ አሀዛዊ ቅጥፈት ቀፍቃፊ ጌቶቸ ናቸው፡፡

መማቆ ደብረጽዮን በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ ለበርካታ ሳምንታት የመረጃ ማወናበጃ ዘመቻ በመክፈት ማወናበድን በመቀጠል ረገድ 3ኛው ትልቅ ጠብመንጃ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የዘ-ህወሀትን የጭቆና አገዛዝ በመቃወም እንደ ሰደድ እሳት ተቀጣጥሎ በሚገኘው ሕዝባዊ አመጽ እና መገዳደር ከጥቂት ሳምንታት በፊት አባይ ጸሀይ እና ስዩም መስፍን ከዘ-ህወሀት የአውሬዎች ዋሻ መካከል በድንገት ብቅ ብለው በመውጣት በሕዝብ ላይ የዘር ፍጅት ያወጁ እና የጮኹ ተኩላዎች ናቸው፡፡

የዘ-ህወሀት የመረጃ ማወናበጃ ጨዋታ ግልጽ ይመስላል፡፡ በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ የቁማርና ካራምቦላ (እያጋጩ  ማለት) ጨዋታ በመጫወት ላይ ይገኛሉ፡፡

አባይ ጸሀይ እና ስዩም መስፍን ፍጹም በሆነ መልኩ ምክንያታዊ ያልሆነ እና እርባናቢስ የሆነ የዘር ማጥፋት ወንጀል ይፈጸማል በማለት ፍርሃት ለመፍጠር ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ “ሰማይ ይወድቃል” እያለ በሕዝብ ላይ ምዕናባዊ ፍርሀት በመልቀቅ እንደሚባለው በተመሳሳይ መልኩ አባይ ጸሀይ እና ስዩም መስፍን በኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት ድርጊት ይፈጸማል በማለት ሕዝቡን በማስፈራራት እና በማደናገር ላይ ይገኛሉ፡፡

እንዲያው ለመሆኑ ይህንን አዲስ ነገር አድርገው እንደበቀቀን እየደጋገሙ የሚለፈልፉት ባለፉት 25 ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ምን ሲያደርጉ ነው የቆዩት? በአማራው፣ በኦሮሞው፣ በጋምቤላው፣ በሶማሊው፣ በሲዳማው፣ በአፋሩ፣ በቤንሻንጉሉ፣ ወዘተ ሲፈጽሙት የቆዩትን የዘር ማጥፋት ወንጀል እስቲ ዘወር ብለው ይመልከቱት፣ ዘወር ብሎ የሚያይ አንገት ካላቸው፡፡ ምኑ ነው አሁን አዲስ የሚሆነው፡፡ ይልቁንስ አሁን የእነርሱ ማብቂያ እና መውደሚያ መሆኑን ስለተገነዘቡት ይሆናል የአቦን ቅጠል እንደቀመሰች ፍየል በመለፍለፍ ላይ የሚገኙት፡፡

ነው? ወይስ ያብየን ለምዬ?

መማቆ ደብረጽዮን የዘር ማጥፋት ወንጀል አይኖርም ይላል፡፡ በእርግጥ የራሱ ቃላት እንዲህ የሚሉ ሆነው ይገኛሉ፣ “በኢትዮጵያ ውስጥ የሕዝብ ለሕዝብ ግጭት (የዘር ማጥፋት ወንጀል) ሊኖር አይችልም፡፡ በጥቂት ወንጀለኞች እና ችግር ፈጣሪዎች ሊቀሰቀሱ የሚችሉ የተነጣጠሉ ሁከቶች እና ግጭቶች (አመጾች ሳይሆኑ) ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ እነዘህ ደግሞ የዘር ማጥፋት ወንጀሎች አይደሉም“ በማለት ሳያውቀው አምኗል፡፡

እንግዲህ ወገኖቼ ከነዚህ ባለመንታ ምላስ እባቦች የትኛውን እንመን? አባይ ጸሀይን፣ ስዩም መስፍንን ወይስ ደግሞ ደብረጽዮን ገብረሚካኤልን?

መማቆ ደብረጽዮን በመጠኑም ቢሆን ተቀባይነት ያለው ለማስመሰል እና እራሱን ከሌሎቹ አስበልጦ እንዲታይ የማድረግ ቁመናን ለመላበስ ሙከራ አድርጓል፡፡ በስተቀኙ በኩል የዘ-ህወሀትን ባለኮከብ እርማ ሰንደቅ ዓላማ በማንጠልጠል የዘ-ህወሀት መልካም አድራጊ መስሎ መቅረብ ሞክሯል። ግን ያለው አስተሳሰብና ያደርገው ድርጊቶች ለኢትዮጵያ ህዝብ  አርሱም ዘ-ህወሀትም  ደንታ እንደሌላቸው አረጋግጧል። መማቆ ደብረጽዮን  የኢትዮጵያ ህዝቦች በዓለም ላይ ታይተው የማያውቁትን ነገሮች ቀይ እና ሰማያዊ ላም እንዲሁም ቀይ ዝሆን አየን እያሉ ይናገራሉ፡፡ ዝም ብለው ይቀባጥራሉ እናም እንዲሁ በፈጠራ ወሬዎች ጭንቅላታቸውን ሞልተው ይገኛሉ ነበር ያለው፡፡

መማቆ ደብረጽዮን ሁሉም ነገር አንዳለ ሳይሆን አንደተመለከቱቱ ነው ይላል። ሲያስረዳም ፣ “አንድ ሰው የጠራውን ቀን ጨለማ ነው  ደጋግሞ ካለ ሕዝቡ ያንን የጠራ ቀን ጨለማ ነው የሚል ሀሳብን ይይዛል ማለት ነው“ ነበር ያለው፡፡

ከዚህ አንጻር በዘፈቀደ አመንኩ፡፡ እጄን ሰጠሁ!

ስለጨለማ እራሱ የጨለማው  ልዑል ከሆነው አስመሳይ ፍጡር በላይ ማን ሊያውቅ ይችላል?

ስለጨለማ የጨለማው ጌታ ከሆነው ከንቱ ፍጡር በላይ ማን የበለጠ ሊያውቅ ይችላል?

ስለጭለማ መማቆ ደብረጽዮንን የመሞገት ችሎታ የለኝም።

ስለጨለማ በብርሀኑ በኩል ያሉት ሰዎች ሳይሆኑ የጨለማው ጌታ የበለጠ ያውቃል።

በሚያስገርም ሁኔታ መማቆ ደብረጽዮን የእርሱን የጨለማ ተመሳስሎ የተዋሰው እንዲህ ከሚለው እና የናዚ ጀርመን የፕሮፓጋንዳ ሚኒስትር ከነበረው ከጆሴፍ ጎቤልስ ነው፣ “ታላቅ ውሸት ከዋሸህ እና ይህንንም ውሸት ደግመህ እና ደጋግመህ ተግባራዊ ካደረግኸው በመጨረሻ ሕዝብ እውነት ብሎ ያምናል፡፡

ሆኖም ግን መማቆ ደብረጽዮን እንዲህ የሚሉትን የጎቤልስን አብረው የነበሩትን ቃላት ሆን ብሎ ዘሏቸዋል፡

“መንግስት ሕዝቡን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና/ወይም ወታደራዊ የሆኑ ውሸቶች ከሚፈጥሯቸው እንቅስቃሴዎች ለመከላከል ሲል ውሸቶች ለእንደዚህ ላለ ጊዜ ብቻ ሊቆዩ ይችላሉ፡፡ በዚህም መሰረት እውነት የሚሞተው የውሸት ጠላት በመሆኑ እና የዚህም ተቀጽላ እውነት የመንግስት ታላቁ ጠላት በመሆኑ መንግስት ሁሉንም ኃይሉን ሰላማዊ ሰዎችን ለመጨቆኛነት የሚጠቀምበት ዋናው አስፈላጊው መሳርያ ነገር ነው፡፡“

እውነት የመንግስት የመረጃ ማወናበጃ ዋና ጠላት ነው፡፡

የመማቆ ደብረጽዮን ቃለመጠይቅ፣

Debretsion Gebremichael

ደብረጽዮን ገብረሚካኤል

በቪዲዮ በተቀረጸው ቃለመጠይቅ መማቆ ደብረጽዮን በበርካታ ጉዳዮች ላይ በተደጋጋሚ ሲደነፋ ( ሲንተባተብ አላልኩም) እና የኢትዮጵያ ሕዝቦች ስለዘ-ህወሀት እውነተኛ ምንነት መግለጽ የማይችሉ ደንቆሮዎች እና ደደቦች መሆናቸውን ተናግሯል፡፡ በቁስል ላይ እንጨት እንዲሉ በውሸት ላይ ያሉ ሕዝቦች በማለት እራሱን ከፍ ከፍ እያደረገ መሰረተቢስ የሆነውን የማታለል ንገግር አድርግዋል ፈጽሟል፡፡ ለመማቆ ደብረጽዮን ኢትዮጵያ ሕዝቦች በምዕናባዊ ሀሳብ እና በእውነት መካከል ያለውን ልዩነት ለይተው የማያውቁ የዋሀን ናቸው፡፡ በእርሱ ድሁር አስተሳሰብ የኢትዮጵያ ሕዝቦች የሚያዩት ነገር በተጨባጭ የሚያዩት እና የሚመለከቱት ነገር አይደለም፡፡ ሆኖም ግን ምንም ዓይነት እውነታነት የሌለው በድድብና የተሞላ ምዕናባዊ ነገር ነው፡፡ እውነታውን እንዲያውቁት እንዲመለከቱት ተደጋጋሚ የሆነ ትምህርት ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ይህንን ትምህርት እንዲሰጥ እና ስራውን እንዲሰራ ለብዙሀን መገናኛ ጥሪ መቅረብ አለበት ነው ያለው መማቆው !

የመማቆ ደብረጽዮን ቃለመጠይቅ እንዲህ የሚሉ በርካታ የሆኑ የፕሮፓግንዳ እና የፖለቲካ ዓላማዎችን ለመጎናጸፍ በግልጽ የተዘየደ ዕቅድ ነው፡

1ኛ) በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ውስጥ ተቀጣጥሎ የሚገኘው መጠነ ሰፊ ሕዝባዊ ተቃውሞ በጎንደር ላይ ተወስኖ የሚገኝ ትንሽ ነገር ነው፡፡

2ኛ) በጎንደር ውስጥ የተፈጠረው ሁከት ጥቂት የውጭ ኃይሎች እና ወንጀለኞች ስራ ነው፡፡ በጎንደር ውስጥ ወይም ደግሞ በሌላ በማናቸውም ቦታ እና አካባቢ ውስጥ ምንም ዓይነት ሕዝባዊ አመጽ የለም፡፡

3ኛ) በጎንደር የተቀሰቀሰው ሁከት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ባልተወጡ የስራ ኃላፊዎች እና  በአካባቢው አመራር ብቃትየለሽነት እና የአስተዳደር ጉድለት የተፈጠረ ነው፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ተወግደው በሌላ መተካት ይኖርባቸዋል፡፡

4ኛ) በኢትዮጵያ ሕዝቦች ፖለቲካ እና ማህበረሰብ ውስጥ የትግራይ የበላይነት የሚለው ነገር አውዳሚ የሆነ የሰዎች የተሳሳተ ምዕናባዊ ሀሳብ ነው፡፡ የትግራይ የበላይነት በልብወለድ ውስጥ ያለ በምዕናባዊ ሀሳብ የሚኖር እንጅ በነባራዊ እውነታ በተጨባጭ የሌለ ነገር ነው፡፡

5ኛ) የኢትዮጵያ ሕዝብ የትግራይ የበላይነት የሌለ መሆኑን እንዲያውቅ ትምህርት ያልተሰጠው በመሆኑ ከግንኙነት ውድቀት የመነጨ ነው፡፡ የእራሳቸው የግንዛቤ ምዕናባዊ እሳቤ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች በብርሀን እና በጨለማ መካከል ያለውን ልዩነት መናገር የማይችሉ እንደዚህ ያለ የትግራይ የበላይነት የሚባል ነገር ያለ መሆኑን መናገር የማይችሉ እና ትምህርት የሚያስፈልጋቸው ደንቆሮዎች ናቸው፡፡

6ኛ) ትግራውያን በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ የጎሳ የበላይነት እየተገበሩ ላለመሆናቸው ሊያስገነዝብ የሚያስችል የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ታላቅ የብዙሀን መገናኛ ፍላጎት አለ፡፡

7ኛ) የኢትዮጵያ ፖለቲካ ነባራዊ እውነታ የሚያሳየው ነገር ቢኖር እያንዳንዱ የጎሳ ቡድን በእራሱ ክልል (ባንቱስታን) የበላይ ነው፡፡

8ኛ) ለጎሳ ታላቅነት እና የበላይነት የጎሳ ፌዴራሊዝም የመጨረሻው ጠባቂ ኃይል ነው፡፡

9ኛ) ብቸኛው እውነታ የዘ-ህወሀት እውነታ ብቻ ሲሆን ሌላው ግን ተራ ምዕናባዊ ሀሳብ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ስለኢትዮጵያ ሕዝቦች መልካም ነገር እና ጥቅም ተልዕኮው ተነግሮ ስለማያልቀው ስለዘ-ህወሀት የተሳሳተ ግንዛቤ አለው፡፡

10ኛ) የኢትዮጵያ ሕዝቦች ዘ-ህወሀት ደም የተጠማ ወንጀለኛ የወሮበሎች ስብስብ እንደሆነ አድርገው የሚነግሯቸውን የሚዋሹ ዓይኖቻቸውን እና ጆሮዎቻቸውን ማመን የሚያቆሙ ከሆነ የዘ-ህወሀትን ደግ፣ ጓዳዊ፣ የተረጋጋ፣ ለጋሽ፣ አፍቃሪ እና ሰብአዊ ፍጡርነት ይገነዘባሉ፡፡“

በሰጠው ቃለመጠይቅ መማቆ ደብረጽዮን በቅርቡ በጎንደር የተፈጠረውን ሁከት (ሕዝባዊ አመጽ) እና ትግራውያንን ማፈናቀል እየተባለ የቀረበውን ውንጀላ ጨምሮ የትግራይ የበላይነት የሚለው መሰረተቢስ ውንጀላ እንደሆነ እና የጎሳ ፌዴራሊዝም የኢትዮጵያ የፖለቲካ እና የማህበራዊ ቀውሶች ሁሉ ፈዋሽ መድኃኒት አድርጎ በርካታ ጉዳዮችን እንደሚከተለው አቅርቧል፡

መማቆ ደብረጽዮን አንደተናገረው (ከእንግሊዘኛው አንደተተረጎመ)

“በጎንደር ስለተከሰተው “ግጭት”፣ “ሁከት” ሁኔታ፣

…እንደ ቁንጮ አመራር እኔ ብቻ ስለሁኔታው አውቃለሁ፡፡ የግጭቱን ዝርዝር ሁኔታ የሚያውቁ የተለያዩ አካላት ናቸው፡፡ ያንን ሁኔታ በቅርበት አልከታተልም…በሱዳን እና ከሱዳን በተመለሱት መካከል ግጭት እንዳለ አውቃለሁ፡፡

ይህንን እንዴት መመልከት እንዳለብን፡ በተለየ መልክ እንደተገለጸው ዋናው ነገር ይህ ሁኔታ የሕዝብ ለሕዝብ ጉዳይ (ግጭት) አይደለም፡፡ ከትግራይ ጥቂት የእኛ ሰዎች እና ከሌሎች ቦታዎች በጎንደር ውስጥ በተፈጠረው አመጽ እየተሰቃዩ እና ጉዳት እየደረሰባቸው ይገኛሉ፡፡ የተቀጣጠለውን እሳት (ግጭት) ለማስፋፋት የሚፈልጉ ጥቂት ሰዎች እንዳሉ እንገነዘባለን፡፡ በጎንደር የሚኖሩ የአማራ ሕዝቦች ናቸው፡፡ ሌሎችን (አማራ ያልሆኑትን) እንደሚከላከሉላቸው እና ጉዳት እንደማይደርስባቸው እንገነዘባለን፡፡ የተፈጸሙ በርካታ ድርጊቶች (ወንጀሎች) አሉ፡፡ በጣም ጥቂት የሆኑ ሰዎች በጎንደር በሚኖሩ ትግራውያን ንብረቶች ላይ ጉዳት ለማድረስ ይፈልጋሉ፡፡ ስለሆነም እነዚህ ድርጊቶች የአብዛኛው የጎንደር ሕዝብ ድርጊቶች አይደሉም፡፡ በየትኛውም ቦታ ትግራውያንን ለማጥቃት ተብሎ የሚደረግ እንቅስቃሴ የለም፡፡ ሆኖም ግን በትግራውያን ላይ ወንጀሎችን ለመፈጸም የሚንቀሳቀሱ ጥቂት ሰዎች እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ጥቂት ግለሰቦች በትግራውያን ላይ የወንጀል ድርጊቶችን እንደፈጸሙ እናውቃለን፡፡ ይህ ሁኔታ የጥቂቶች ድርጊት እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ከእራሳቸው ዓላማ ጋር የሚደረግ እንቅስቃሴ አለ፡፡ የፌዴራል መንግስት እና የክልሉ መንግስት ይህንን ሁኔታ በቅርብ በመከታተል ላይ ይገኛሉ፡፡

ሆኖም ግን ይህ ጥያቄ መጠየቅ ያለበት ጥያቄ አይደለም፡፡ ከትንታኔው መገንዘብ እንደሚቻለው መፍትሄው በግጭቱ (መጋፈጥ) ላይ በማተኮር ብቻ ሊገኝ አይችልም፡፡ በአካባቢው አመራር፣ ለሕዝቦች መልካም አስተዳደር ማቅረብ ያልተቻለበትን፣ ለሚቀርቡት ጥያቄዎች ሁሉ በወቅቱ ምላሽ ያልተሰጠበትን፣ ችግሮች ያሉ መሆናቸውን ያለማስተዋል እና ሌሎችን እንደዚህ ያሉትን ሁኔታዎች ሰፋ ባለ መልኩ መመልከት አለብን፡፡ እናም በዚህ ጉዳይ ዙሪያ እንቅስቃሴዎች ይኖራሉ፡፡ ይህ በእራሱ ችግሮችን ፈጥሯል፣ እናም በዚህ ዙሪያ ያሉትን ችግሮች የምንፈታ ከሆነ ሌሎችን ችግሮችም አብረን እንፈታለን፡፡ ሌሎች አስተዳደራዊ ችግሮችን፣ የልማት ጥያቄዎችን እንፈታለን ማለት ነው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ የፖለቲካ ጥያቄዎችን ማንሸራሸር እና መፍታት እንችላለን፡፡ እኛ እንግዲህ የምንመለከተው በዚህ ዓይነት መንገድ ነው፡፡ 

በጎንደር የተከሰተው ግጭት አንድ ውሱን ጉዳይ ነው፡፡ ሁሉንም አጠቃላይ ሁኔታ የሚያሳየን አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች በተለያዩ መድረኮች ላይ እየተካሄዱ ባሉት ውይይቶች ላይ በጣም አዝነዋል፡፡ ይህ ኢህአዴግ ያመጣው ነገር አይደለም፡፡ የጎንደር እና የትግራይ ሕዝብ ለበርካታ ጊዚያት አብረው ኖረዋል፡፡ በአንድ ላይ መኖር ብቻ አይደለም ሆኖም ግን እርስ በእርስ በመጋባት እንደ አንድ ቤተሰብ ሆነዋል… ሆኖም ግን ሕዝብ ለሕዝብ ግጭት (የጎሳ ግጭት) ለመፍጠር ዓላማ አድርገው የሚንቀሳቀሱ ጥቂት ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ህገወጥ ተግባር ነው፡፡ ጉዳቶች ተፈጥረዋል…እንግዲህ በቅርብ ጊዜ ውስጥ እየተደረገ ያለው ውይይት ስለዚህ ጉዳይ ነው፡፡ 

የሕዝብ ለሕዝብ (የጎሳ) ግጭት ሊኖር አይችልም… በጎንደር ስለተፈጸመው ትንሽ ግጭት የተለየ ልዩ የሆነ መፍትሄ የለንም፡፡ በአንድ በትግራውያን ላይ ለደረሰ ጉዳት መፍትሄ የለም፡፡ ዋናው ነገር ስለሰላም እና መረጋጋት ጉዳይ ነው፡፡ ይኸ ጉዳይ በሚገባ ከተመለሰ ሌላው (የጎሳ ግጭት) ጉዳይ በእራሱ ይፈታል፡፡ 

በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ ስለትግራይ የበላይነት ሁኔታ፣ 

አልጋ በአልጋ የሚሆን ነገር የለም፡፡ ውጣ ውረድ አለ፡፡ እውነታ የማይመስል አንድ  ምዕናባዊ አስተሳሰብ እውነት ይሆናል፡፡ ለምሳሌም ያህል አሁን በዚህ ክፍል ውስጥ ብርሀን አለ፡፡ ነገር ግን አሁን በዚህ ክፍል ያለው ጨለማ ነው የሚባል እና የሚደገም ከሆነ ሕዝብ ጨለማ ነው ብሎ ያምናል፡፡ ብርሀን መኖሩ የሚታወቅ ቢሆንም እንኳ ጨለማ ነው፡፡ ምዕናባዊው ሀሳብ ወደ ተጨባጭ እውንነት ተለወጠ ማለት ነው፡፡ ይህም የሆነበት ዋና ምክንያት አንድ የተረሳ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ትክክለኛው ምላሽ ለኢትዮጵያ ሕዝብ አልተሰጠም ማለት ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ በብዙሀን መገናኛዎች ውጤታማ የሆነ ስራ አልተሰራም ማለት ነው፡፡ ማንኛውም እውነት ሆኖ ያልተገኘ ነገር ሁሉ (ምክንያቱም ስለትግራይ የበላይነት እየተነገሩ የቆዩ ውሸቶች እስከ አሁን ድረስ ተግዳሮት ስላልገጠማቸው) አሁንም እውነት አይደለም፡፡ 

እውነት በእራሱ አይናገርም፡፡ እውነታውን በተለያዩ መንገዶች በብዙሀን መገናኛ እና በሌሎች መግለጽ ይቻላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ የመንግስት ሜዲያ ተገቢ የሆነ ስራ መስራት አለበት፡፡ ድክመት፣ እድገት ወይም ደግሞ ወደኋላ የመንሸራተት እና ሌሎችም ጉዳዮች ካሉ የመንግስት ሜዲያ ነው እውነታውን ማቅረብ ያለበት፡፡ ሆኖም ግን ሜዲያው እውነትን ማንጸባረቅ (ማሰራጨት) አለበት፡፡ 

በፌዴራሊዝም መኖር ምክንያት የትግራይ የበላይነት ሊኖር አይችልም፡፡ ፌዴራሊዝም ማለት ሁሉም ሕዝቦች እኩል ናቸው ማለት ነው፡፡ እያንዳንዱ ሕዝብ እራሱን በእራሱ ያስተዳድራል፡፡ አንድ ጎሳ የበላይ ወይም የበታች የሚባል ነገር የለም፡፡ የጎሳ ቡድኖች ትልቅ ወይም ትንሽ አባላት ስለመኖር ጉዳይ አይደለም፡፡ ትግራውያን እራሳቸውን ያስተዳድራሉ፡፡ ኦሮሞዎች እና የደቡብ ሕዝቦች እንዲሁም የሶማሊ ሕዝቦች እራሳቸውን በእራሳቸው ያስተዳድራሉ፡፡ ይህም ማለት የእራሳቸውን መንግስት በባለቤትነት ይይዛሉ ማለት ነው፡፡ መሰረቱ እኩልነት ነው፡፡ ይህ ማለት የእራስህን አስተዳደር አስተዳድር ማለት ነው… 

በአማራ ክልል ውስጥ ትግራውያን አስተዳዳሪዎች ሊሆኑ አይችሉም፡፡ በጋምቤላ ውስጥ አስተዳዳሪው ትግራዊ ሊሆን አይችልም፡፡ እንደዚህ ያለው የጎሳ ፌዴራሊዝም አወቃቀር አንዱ ጎሳ በሌላው ላይ የበላይ እንዲሆን አያደርግም፡፡ አንድ ዓይነት የጎሳ ማንነት ያላቸው እራሳቸውን ያስተዳድራሉ፡፡ ትግራውያን እዚህም እዚያም የበላይ (አለቆች) ናቸው የምትል ከሆነ መሰረትየለሽ ነገር ነው፡፡ ሆኖም ግን በየቦታው እስከ ቀበሌ መዋቅር ድረስ ሁሉም ነገር እውነትነት የሌለው ምዕናባዊ ሀሳብ ነው፡፡ የትግራውያን የበላይነት እውነታነት የለውም፡፡ እንደዚህ ያለ ውንጀላ ማቅረብ መሰረተቢስ ነው፡፡ ብርሀን እየበራ እያለ ባለበት ሁኔታ ጨለማ ነው እንደማለት ያህል ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህንን በደጋገምከው ጊዜ ሌሎችም አዎ ጨለማ ነው ሊሉ ይችላሉ፡፡ በፌዴራሊዝም ሀገሪቱ እንዴት መተዳደር እንዳለባት ስለፌዴራሊዝም የኢትዮጵያን ሕዝቦች አላስተማርናቸውም፡፡   

ያ እውነታ ለህዝቡ እንዲተላለፍ አልተደረገም፡፡ ትግራውያን በየቦታው የበላይ ናቸው ማለት እውነታ አይደለም፡፡ ያ ዜሮ ነው፡፡ ዜሮ፡፡ ከትግራይ ክልል ውጭ ትግራውያን ሰው ካለ የመዋዕለ ንዋይ አፍሳሽ ኢንቨስተር ሆኖ እንደማንኛውም ሰው ይኖራል፡፡ ስለሆነም ሕዝቡን ያለማስተማር የግንዛቤ ችግር አለብን፡፡ የትግራይ የበላይነት እውነት አይደለም ሆኖም ግን የእኛ ብዙሀነን መገናኛዎች ጉድለት አለባቸው፡፡ የትግራይ የበላይነት እንደሌለ ብዙሀን መገናኛዎች እውነቱን የማሰራጨት ኃላፊነት አለባቸው…

መማቆ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል፡ መንታ ምላስ እና ሁለት ተጻራሪ እምነቶችን በመያዝ የመረጃ ማወናበጃ ዘመቻን ማካሄድ፣

ጆርጅ ኦርዌል “ፖለቲካ እና የእንግሊዝኛ ቋንቋ“ በሚል ርዕስ ባዘጋጀው ድርሰቱ እንዲህ በማለት ጽፏል፡

በእኛ ጊዜ የፖለቲካ ንግግር እና መጻፍ በአብዛኛው መከላከል ለማይደረግላቸው መከላከያዎች ናቸው፡፡ የፖለቲካ ቋንቋ… ውሸቶችን ለመፈብረክ እና እውነት ለማስመሰል የተዘጋጀ እና የተከበሩትን ለመግደል ምንም ዓይነት ጥንካሬ በሌለበት በባዶ ነፋስ ውስጥ ጥንካሬ እንዳለ አድርጎ የማቅረብ ድርጊት ነው…“ ነበር ያለው፡፡

ከደብረጽዮን መንታ ምላስ የሚወጡ ዉሸቶችና እና ተጻራሪ እምነት የሚብሱ ብዙ የሉም፡፡

የአዞ እንባ አንቢው ደብረጽዮን በመንግስት ላይ መንግስት ላዋቀረው እና ማንኛውንም ነገር የሚቆጣጠረው የዘ-ህወሀት ፖለቲካ አጧዛዥ አድራጊ ፈጣሪ ነው፡፡ በዘ-ህወሀት አገዛዝ ውስጥ በርካታ የኃላፊነት ቦታዎችን ይዞ ቆይቷል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የኮሙኒኬሽን እና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጅ ሚኒስቴር ኃላፊ (በትክክለኛ አጠራር የመረጃ ማወናበጃ ቆሮ (መማቆ)/ Chief Disinformation Officer (CDO) እና ከሶስቱ የዘ-ህወሀት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች አንዱ በመሆን በማገልገል ላይ ይገኛል ይባላል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን የቦርድ ሊቀመንበር እና የቀድሞው የኢትዮጵያ የኢንፎርሜሽን እና ኮሙኒኬሽን ልማት ኤጀንሲ/Ethiopian Information and Communication Development Agency (EICTDA)፣ ቴክኖሎጂ የደረሰበትን የብሮድባንድ ኔትዎርክ ለመገንባት እና የአካዳሚክ እና የምርምር ኔትወርኮችን ለመደገፍ፣ የኢንፍርሜሽን ኮሙኒኬሽን ኔትዎርክ እና ልማትን በማሳደግ  የአካዳሚክ ተቋማትን የግል ዘርፉን ለማሻሻል ተቋቁሞ የነበረው ድርጅት ዳይሬክተር ጀኔራል ነበር ይባላል፡፡

በአዋጅ ቁጥር 691/2010 ድንጋጌ መሰረት የተቋቋመው የኮሙኒኬሽን እና የኢንፎረሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የEICTDA፣ የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒከኬሽን አጀንሲ/ETA እና የዘ-ህወሀት የትራንስፖርት እና ኮሙኒኬሽን ሚኒስቴር ጥምረቶች ነው፡፡

መማቆ ደብረጽዮን የዘ-ህወሀት ተቃዋሚ በሆኑት በኢትዮጵያ ዲያስፖራዎች ላይ ስለላ ለሚያካሂደው እና ከጣሊያን አገር የሳይበር ደህንነት ድርጅት ምርመራ ቡድን/cybersecurity firm Hacking Team የተገዛው ሶፍት ዌር በስለላ ተግባር ላይ እንዲውል እና ለኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲ እና ሰብአዊ መብት ድፍጠጣ ዕኩይ ምግባር ዋና መሀንዲስ ሆኖ ሲያገልግል የነበረ ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ2014 የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሬፐብሊክ ከዩኤስ አሜሪካ የቴሌፎን መስመር ጋር በማገናኘት የስለላ ተግባራትን በማካሄድ ሕግን መጣስ የሚል ውንጀላ በዩኤስ ፌዴራል ፍርድ ቤት ተመዝግቦ በፋይል ተያዘ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ጉዳዩ በሕግ ማሻሻያ ሂደት ውስጥ ሲሆን በቀጣዮቹ ጥቂት ዓመታት ውስጥ ለዩናይትድ ስቴት አሜሪካ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ይደርሳል፡፡

እንደ አንድ ዘገባ ከሆነ መማቆ ደብረጽዮን በጫካ ውስጥ የዘ-ህወሀት ሬዲዮ ጣቢያ የነበረውን ድምጺ ወያኔን ከመሰረቱ ግለሰቦች መካከል አንዱ ነው ይባላል ፡፡ ሚኒያፖሊስ አም ኤን እየተባለ ከሚጠራው የድረገጽ ዩኒቨርስቲ የዶክትሬት ዲግሪውን እ.ኤ.አ በ2011 እንዳገኘ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ “በኢትዮጵያ ድህነት ላይ የአይሲቲ ማዕከል ተጠቃሚዎችን የአይሲቲ ውጤታማነት መፈተሽ/Exploring the perception of users of community ICT centers on the effectiveness of ICT on poverty in Ethiopia“ በሚል ርዕስ ባዘጋጀው የዶክትሬት ዲግሪው የጥናት መሟያ የመመረቂያ ጽሁፍ ምናልባትም ኢንፎርሜሽን እና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ (አይሲቲ) የልማት መገልገያ መሳሪያ እንደሆነ መርምሮ ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን በሚያስገርም ሁኔታ በድህነት ላይ ያለውን የህልዮት ግንዛቤ በተመሳሳይ መልኩ ለፕሮፓጋንዳ እና ለመረጃ ማወናበጃ ዘመቻ ስራ እንደሚውል አድርጎ እምነት ያሳደረ ይመስላል፡፡

መማቆ ደብረጽዮን አሁን በህይወት እንደሌለው እንደ ወሮበላ ዘራፊው መለስ ዜናዊ (ወዘመዜ) ሁሉ የኦርዌልን ባህሪ የተላበሰ ገጽታ ያለው ሰው ነው፡፡ እንደ ወዘመዜ ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ መማቆ በኢትዮጵያ ሕዝቦች፣ በአበዳሪዎች፣ በለጋሽ ድርጅቶች እና በዓለም አቀፍ የድህነት አቃጣሪዎች ላይ የቁማር ጨዋታን መጫወት ይወዳል፡፡

እንደ ታላቅ ወንድሙ እንደ ወዘመዜ ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ መማቆ እርሱ እና የእርሱ ዘ-ህወሀት ወሮበላ ዘራፊዎች በእውነት እና በእውነታዋ ዓለም ላይ የሚኖሩ እና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ደግሞ በህልም እና በጨለማ ምዕናባዊ ዓለም እንዲሁም በሀሳብ እና በቅዠት ዓለም ውስጥ የሚኖር ነው በማለት ያምናሉ፡፡

በዘ-ህወሀት የኦርዌሊያን ፕላኔት “ጦርነት ሰላም ነው፡፡ ነጻነት ባርነት ነው፡፡ ድንቁርና ጥንካሬ  ነው፡፡ አምባገነንነት ዴሞክራሲ ነው፡፡ የጎሳ ፌዴራሊዝም የጎሳ እኩልነት ነው፡፡ የጎሳ የበላይነት ሕገወጥ ሴራ ነው፡፡ የዘ-ህወሀት ባለሀብቶች አገዛዝ ማለት ሁሉም ሕዝቦች እኩል የፖለቲካ ስልጣን አላቸው ማለት ነው፡፡“

መማቆ ደብረጽዮን የኢትዮጵያን ሕዝቦች እንደሚያታልሏቸው፣ ጆሮዎቻቸው እንደሚዋሹባቸው እንዲያምኑ እና ጉድለት ያለው አእምሮ እንዳላቸው አድርገው እንዲያምኑ ይፈልጋል፡፡

ስለዘ-ህወሀት ፕላኔት መረጃ ማወናበጃ ዘመቻ ከብዙ ጊዜ ጀምሬ ስጽፍ ቆይቻለሁ፡፡

እ.ኤ.አ ወደ 2009 መለስ ብለን ስንቃኝ ከ3.6 ሚሊዮን የአካባቢ ምርጫዎች መቀመጫዎች ባለፈው ዓመት (2008) ከሶስት መቀመጫዎች በስተቀር ሁሉንም ማሸነፍ ፍጹም የሆነ ዴሞክራሲያዊ ነው፣ እናም ዴሞክራሲ ስለሂደት ነው፣ ስለውጤት አይደለም… ሂደቱ ንጹህ ከሆነ ስህተት ዜሮ ነው ነበር ያለው መለስ ዜናዊ ፡፡

ዛሬ መማቆ ደብረጽዮን እንዲህ ይላል፣ “የጎሳ ፌዴራሊዝም እኩልነት ነው፡፡ የዘ-ህወሀት የበላይነት ምንም ዓይደለም ግን ዱለታ ነው፡፡ ትግራውያን በየቦታው የበላይ ናቸው ማለት እውነታን የሚያመላክት አይደለም፡፡ ያ ዜሮ ነው፡፡

የሚያስገርመው ነገር መማቆ እና ወዘመዜ ስለዜሮ አንድ ነገር አላቸው፡፡

ዘሮን በጣም ይወዱታል፡፡ በተለይም የዜሮ ድምር ምርጫ ጨዋታዎችን (ሁልጊዜ ሁሉንም ነገር እንደሚያሸንፉ እና ሌላው እያንዳንዱ ሰው ግን ሁሉንም ነገር እንደሚያጣ እና እንደሚሸነፍ) በጣም ይወዷቸዋል፡፡ ላለፉት 25 ዓመታት ከአንድ የዜሮ ድምር ጨዋታ ሌላ የዜሮ ድምር ጨዋታ እየተገለባበጡ በመጫወት ሁልጊዜ በተከታታይ ሲያሸንፉ ኖረዋል፡፡

እስቲ ጉዳዩን ግልጽ ላድርገው፡፡ እ.ኤ.አ ግንቦት 2015 በዘ-ህወሀት ፓርላማ መቀመጫዎችን መቶ በመቶ ያሸነፈው ማን ነው? ይኸ ነው እንግዲህ የዜሮ ድምር ጨዋታ ማለት!

ቀደም ሲል እ.ኤ.አ በ2008 ተካሂዶ እንደነበረው የአካባቢ ምርጫዎች ወዘመዜ ኢትዮጵያውያን ስለዘ-ህወሀት የተሳሳት ግንዛቤ አላቸው እንዳለው ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ መማቆ ደብረጽዮን ዛሬ እንደዚሁ በማለት ላይ ይገኛል፡፡

ወዘመዜ ኢትዮጵያውያን ስለዴሞክራሲ የተሳሳተ ግንዛቤ አላቸው ብሏል፡፡ ስለምርጫዎች፣ የሕግ የበላይነት፣ መልካም አስተዳደር እና ስለፌዴራሊዝም የተሳሳተ ግንዛቤ አላቸው፡፡

መማቆ ደብረጽዮን ስለዘ-ህወሀት ዴሞክራሲ፣ ፌዴራሊዝም፣ ስለትግራይ የበላይነት፣ ስለልማት፣ ስለመልካም አስተዳደር እና ስለዴሞክራሲ የተሳሳት ግንዛቤ አላቸው ይላል፡፡

መማቆ ደብረጽዮን ኢትዮጵያውያን ከእንቀልፋቸው ተነስተው የፈላዉን ቡና ያሽትቱ ይላል፡፡

በዘ-ህወሀት ፕላኔት ውስጥ የተጻራሪ እምነቶች እና መንታ ምላሶች ውጤት፡ “ጦርነት ሰላም ነው፡፡ ነጻነት ባርነት ነው፡፡ ድንቁርና ጥንካሬ ነው፡፡ አምባገነንነት ዴሞክራሲ ነው፡፡ ድህነት ባለጸግነት ነው፡፡ ረሀብ ጥጋብ ነው፡፡ የመንግስት ስህተቶች የሰብአዊ መብቶች ናቸው፡፡ የተጭበረበሩ እና የተዘረፉ ምርጫዎች የሕዝቦች ምርጫዎች ናቸው፡፡ ሕዝቦችን ማስፈራራት ለእነርሱ የደስታ ምንጭ ነው፡፡ እናም የተደራረቡት የውሸቶች ቁልሎች የእውነት ማዕበሎች ናቸው፡፡“

የዘ-ህወሀት መንታ ምላስ እና ተጻራሪ እምነቶች ምርጫዎች ስለሂደት የሚዘግቡ ናቸው፡፡ የሕግ የበላይነት ማለት በዘፈቀደ የዜጎችን ህይወት የመቅጠፍ፣ የነጻነት እና ንብረት ክልከላ ሂደት ነው፡፡ አስተዳደር ስለተጠያቂነት እና ግልጸኝነት አይደለም፡፡ በላም ጡት ላይ ተጣብቆ እንደሚኖር መዥገር በስልጣን ኮርቻ ላይ ተጣብቆ መኖር ማለት ነው፡፡ ሕገ መንግስት ስለሕግ የበላይነት አይደለም፡፡ ስለሕገወጥ አገዛዝ ነው፡፡ ፌዴራሊዝም ስለግልጽ ሕገመንግስታዊ የስልጣን ክፍፍል አይደለም፡፡ ሆኖም ግን አምባገነናዊ አገዛዝን ለማጠናከር ጥልቅ የሆነ የጎሳ፣ ባህላዊ እና ክልላዊ የጎሳ ፌዴራሊዝም እየተባለ ስለሚጠራው ምዕናባዊ ሂደት ነው፡፡

መንታ ምላስ እና ተጻራሪ እምነቶች እንደ መረጃ ማወናበጃ ስልቶች፣

እ.ኤ.አ በ1984 ኦርዌል እንዲህ በማለት ጽፏል፡

ተጻራሪ እምነት ሁለት ተጻራሪ እምነቶች በአንድ ሰው አእምሮ ውስጥ በአንድ ጊዜ የሚያዙበት እና ሁለቱንም መቀበል ማለት ነው… በቅንነት የሚያምኑበትን ሆን ብሎ ውሸቶችን ለመናገር እና የማይመቹ የሚመስሉትን እንዲረሱ የማድረግ እና አስፈላጊ ከሆነም ብዙ ጊዜ የቆየ እና የተረሳ ቢሆንም ነባራዊውን እውነታው መካድ እና አንድ ሰው የካደውን እንዲይዝ የሚደረግበት ሁኔታ ነው- ይኸ ሁሉ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ተጻራሪ እምነቶች የሚለውን ቃል መጠቀም ቢኖርም ተጻራሪ እምነቶችን መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡ ቃሉን ለመጠቀም አንድ ሰው ከእውነታው ጋር መጋፈጥ ይኖርበታል፡፡ አዲስ በሆኑ ተጻራሪ እምነቶች ይህንን እውቀት ለማጥፋት እና ወሰን በሌለው መልኩ ሁልጊዜ ውሸቱ ከእውነቱ በአንድ እርምጃ ወደፊት ይሄዳል፡፡

 መማቆ ደብረጽዮን እና የእርሱ ዘ-ህወሀት ወሮበላ ዘራፊዎች ሁሉንም ነጻ ጋዜጠኞች በማሰር እና እነርሱን ለመተቸት ድፍረቱ ያላቸውን ፕሬሶች እንዲዘጉ አድርገዋል፡፡ አሁን ደግሞ የመገናኛ ብዙሀኑ የዘ-ህወሀትን እውነተኛ አፈጻጸም ለሕዝቡ በመዘገቡ ረገድ ደካማ አፈጻጸም ነው ያስመዘገቡት በማለት ቅሬታውን በመግለጽ ላይ ይገኛል፡፡ ስለዘ-ህወሀት የብዙህን መገናኛ ደካማ ስራ ቅሬታ የሚያቀርብ ከሆነ የተሳሳተ የአስተሳሰብ መስመርን መከተል ማለት ነው፡፡ አሁን ማንም ኢትዮጵያዊ (ምናልባትም ከዘ-ህወሀት ታዛዥ ሎሌዎች በስተቀር) ለዘ-ህወሀት መገናኛ ብዙሀን ትኩረት አይሰጥም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች በዘ-ህወሀት ውሸቶች፣ ቅጥፈቶች እና ተራ አሃዛዊ አሀዛዊ ቅጥፈቶች ታመዋል፣ ደክመዋልም!

መማቆ ደብረጽዮን ምንም ዓይነት አዲስ ነገር እየተናገረ አይደለም፡፡ የእርሱ ቀደምት የሆነው አስቂኙ በረከት ስምኦን ማንም ቢሆን የዘ-ህወሀትን ቴሌቪዥን ወይም ሌሎችን መገናኛ ብዙሀን አይመለከትም በማለት በየጊዜው ቅሬታውን ያቀርብ ነበር ፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝቦች ከኢሳት ጋር ተጣብቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ከኢሳት ሬዲዮ ጋር እራሳቸውን አዋህደዋል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ኢሳትን በገንዘብ እና በሌላም መደገፍ እንዲችሉ ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡

መማቆ ደብረጽዮን በጎንደር እና በሌሎች ሁከቱ በተቀሰቀሰባቸው አካባቢዎች ያለው ችግር  ስር የሰደደ ሙስና፣ ስልጣንን ከሕግ አግባብ ውጭ የመጠቀም እና ክልሎችን (ባንቱስታን) የሚያስተዳድሩ ባለስልጣኖች የአስተዳደር ጉድለት አለባቸው ይላል፡፡ ከዘ-ህወሀት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የላቸውም፡፡

እውነታው ፍርጥርጥ ተደርጎ ሲታይ ግን  እንደ እንግሊዝ የቅኝ ግዛት ጌቶች እና እንደ ደቡብ አፍሪካ የጥቂት ነጮች ዘረኛ የአፓርታይድ አገዛዝ ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ ዘ-ህወሀት በክልሎች (ባንቱስታንስ) ውስጣዊ ቅኝ ግዛትን በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ ዘ-ህወሀት ለእርሱ ታማኝ የሆኑ ብቸኛ የክልሉ ኗሪ የክልል ባለስልጣናትን ፈጥሯል፡፡ ዘ-ህወሀት የእርሱን ወኪሎች፣ አሻንጉሊት የአካባቢ መሪዎች በስልጣን ላይ ያስቀምጣል፣ እናም ምዕናባዊ የእራስ ገዝ እና የእራስ አስተዳደር መብት ይሰጣቸዋል፡፡ ሆኖም ግን በክልል መንግስታት ላይ ጥብቅ የሆነ ቁጥጥር ያደርጋል፡፡ የክልል ባለስልጣኖች የእራሳቸውን መንግስት በነጻነት መምራት ይቅር እና ከዘ-ህወሀት ፈቃድ ውጭ ከቢሯቸው እንኳ መንቀሳቀስ አይችሉም፡፡ ሆኖም ግን መማቆ ደብረጽዮን በክልል የሚገኙትን ባለስልጣናት በማባረር ዘ-ህወሀትን ነጻ ሊያደርግ ይፈልጋል፡፡

መማቆ ደብረጽዮን ዘ-ህወሀት በጣም ወሳኝ እና አስፈላጊ በሆኑ የፖለቲካ እና የማህበራዊ ተቋማት ውስጥ ዘ-ህወሀት ትንሽ ወይም ደግሞ ምንም ዓይነት ቁጥጥር እንደማያደርግ ይክዳል፡፡

ይህንን ጉዳይ እንዲህ በማለት በሌላ መንገድ ላስቀምጠው፡ እ.ኤ.አ ግንቦት 2016 ተካሄደ የተባለውን የይስሙላ የፓርላሜንታሪ የቅርጫ ምርጫ መቶ በመቶ ያሸነፈው ማን ነበር? በኢኮኖሚው ላይ የበላይነት ያለው ማን ነው? በወታደራዊ ኃይሉ ሙሉ በሙሉ ቁጥጥር ያለው ማን ነው? በሲቪል ሰርቪሱ ላይ ፍጹም የሆነ ቁጥጥር ያለው ማን ነው? የደህንነት አገልግሎቱን እና የፍትህ ሂደቱን ሙሉ በሙሉ የሚቆጣጠረው ማን ነው? የአበዳሪ እና የእርዳታ ሰጭ ድርጅቶችን እንዲሁም የዓለም አቀፍ የደህንነት አቃጣሪዎችን ሙሉ በሙሉ የሚቆጣጠረው ማን ነው?

ለእነዚህ ጥያቄዎች የሚቀርብ ጥያቄ ቢኖር አስፈላጊ የሆኑ መረጃዎችን ለማቅረብ እና በማንኛውም ጊዜ ለመከራከር እርግጠኞች ነን፡፡

በመማቆ ደብረጽዮን የተደረገ አስደናቂ የእምነት ቃል፣

ለአስር ዓመታት ያህል የዘ-ህወሀት የጎሳ ፌዴራሊዝም ስርዓት እና የእርሱ የክልል መንግስታት ሸፍጠኞች እና ስለደቡብ አፍሪካ (ባንቱስታን) ስርዓት የጭብጥ ክርክሬን ሳደርግ እና መረጃዎችን ሳቀርብ ቆይቻለሁ፡፡

በአሁኑ ጊዜ የዘ-ህወሀት ክልል (የጎሳ ፌዴራሊዝም) ስርዓት የአፓርታይድ ባንቱስታን ወይም ደግሞ መኖሪያ ሀገር ስርዓትን በሚመለከት ከደብረጽዮን አፍ ማጠቃለያ ማስረጃ አለ፡፡

አሁን ባለፈው ሚያዝያ “ባንቱስታናይዜሽን (ክልላዊነት) በኢትዮጵያ“ በሚል ርዕስ አቅርቤው በነበረው ትችት በዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጠረው እና እየተጠበቀ ያለው ስርዓት ከደቡብ አፍሪካ ጥቂት ነጮች ዘረኛ አገዛዝ ጋር እንደሚመሳሰል እና እ.ኤ.አ በ1994 የብዙሀኑን ጥቁር አገዛዝ ከመመስረቱ በፊት ከነበረው ጋር አንድ ዓይነት እንደሆነ ከምንም ጥርጣሬ በላይ አሳይቻለሁ፡፡

መማቆ ደብረጽዮን በቃለ ምልልሱ እንዲህ ብሎ ነበር፡

“በአማራ ክልል ትግራውያን አስተዳዳሪዎች ሊሆኑ አይችሉም፡፡ በጋምቤላ ውስጥ አስተዳዳሪው ትግራውያን ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ (የጎሳ ፌዴራሊዝም ስምምነት) ለሌሎች የበላይነት ዕድል አይሰጥም፡፡ አንድ ዓይነት ጎሳ ያላቸው እራሳቸውን በእራሳቸው ያስተዳድራሉ፡፡ ትግራውያን እዚህም እዚያም የበላይ (አለቆች) ናቸው የምትል ከሆነ መሰረተቢስ ነው“ ነበር ያለው፡፡ 

ይኸ ነበር እንግዲህ በአፓርታይድ ባንቱስታን ሀገር በግልጽ የተፈጸመው!

በክዋዙሉ ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው ዙሉስ ሕዝብ ብቻ ነበር፡፡

በሲስኬይ እና በትራንስኬይ ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው የኮሳ ሕዝብ ብቻ ነበር፡፡

በቦትስዋና ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው የትስዋና ሕዝብ ብቻ ነበር፡፡

በሌቦዋ ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው የፔዲ እና የሰሜን ድበሌ ሕዝብ ብቻ ነበር፡፡

በቬንዳ ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው የቬንዳ ሕዝብ ብቻ ነበር፡፡

በጋዛንኩሉ ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው የሻንጋን እና የሶንጋ ሕዝቦች ብቻ ነበሩ፡፡

በክዋ ክዋ ሀገር ስልጣን የሚይዝ እና የመንግስቱን ስራ ሊያንቀሳቅስ የሚችለው የባሶቶስ ሕዝብ ብቻ ነው፡፡

ሆኖም ግን በደቡብ አፍሪካ የመጨረሻውን ስልጣን የያዘው ማን ነው? የጥቂት ነጮች የአፓርታይድ አገዛዝ ነው፡፡

በደቡብ አፍሪካ ያሉ ሕዝቦች ነጻነት ምን ያህል ነጻ ነው?

እንዲያው ለነገሩ ያህል ዘ-ህወሀት ነጻ ናቸው ይላል፡፡

የኢትዮጵያ 9ኙ ባንቱስታንስ ምን ያህል ነጻ ናቸው? ዘ-ህወሀት እንዲያው ለነገሩ ያህል ነጻ ናቸው ይላል፡፡

በእውነተኛ የፌዴራሊዝም ስርዓት ዘር፣ ጎሳ፣ ጾታ፣ ኃይማኖት፣ ርዕዮተ ዓለም፣ ወዘተ የፖለቲካ መብቶችን ከመተግበር ጋር በተያያዘ መልኩ ምንም ዓይነት ጠቀሜታ የላቸውም፡፡

ለምሳሌም ያህል ሂላሪ ክሊንተን ከኒዮርክ የዩኤስ አሜሪካ የምክር ቤት አባል ከመሆኗ በፊት የሞያ ህይወቷን ያሳለፈችው በአርካንሳስ ግዛት ነበር፡፡ ሚት ሮምነይ የተወለደው በሚችጋን ሲሆን የኮሌጅ ትምህርቱን የተከታተለው በኡታህ ሆኖ የማሳቹሴትስ አስተዳዳሪ ሆኗል፡፡ ባራክ ኦባማ የተወለደው በሀዋይ ሲሆን የኮሌጅ ትምህርቱን የተከታተለው ደግሞ በካሊፎርኒያ፣ በኒዮርክ እና በማሳቹሴትስ ሆኖ ከኢሊኖይስ የዩኤስ አሜሪካ የምክር ቤት አባል ለመሆን በቅቷል፡፡

የዘ-ህወሀት የጎሳ ፌዴራሊዝም ስርዓት የቅርብ እና ታላቅ የደቡብ አፍሪካ አፓርታይድ አገዛዝ ተቀጽላ መሆኑን መማቆ ደብረጽዮን ማስተባበል የማይቻል ማስረጃ ያቀረበልኝ ስለሆነ አመሰግነዋለሁ፡፡

ኃይል ያለው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ነው፡ የዘ-ህወሀት መገዳደር እርባናቢስ ነገር ነው፣

በዘ-ህወሀት አገዛዝ ላይ መጠነ ሰፊ እየሆነ እና እየተስፋፋ የመጣው ሕዝባዊ እምቢተኝነት እና መገዳደር እልቂትን በመፈጸም፣ የተዛባ የማወናበጃ መረጃ በማቅረብ ወይም ደግሞ በሌላ በማንኛውም መንገድ የሚቆም አይደለም፡፡

በአንዲ ዊሊያም የግጥም ስንኞች ጸሀይ ሰማይን ትለቃለች ብሎ መናገር አይቻልም/ህጻንን እንዳያለቅስ መጠየቅ አይቻልም/የውቅያኖስን ማዕበል ወደ ዳርቻው እየገፋ እንዳይመጣ ለማስቆም አይቻልም/

እንደዚሁም ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ የኢትዮጵያ ሕዝቦች የሰብአዊ መብቶቻቸውን እንዳይቀዳጁ እና የሕግ የበላይነት የተረጋገጠባት፣ የማትከፋፈል፣ ነጻነት እና ለሁሉም ፍትህ የሰፈነባት ዴሞክራሲያዊ የሆነች ሀገርን እንዳይመሰርቱ ማስቆም አይቻልም፡፡

የኢትዮጵያን ሕዝብ ማስቆም በፍጹም አይቻልም!!!

ምክንያቱ ደግሞ ግልጽ እና ቀላል ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ2008 ዓለም አቀፍ ንቃት የተፈጠረ መሆኑን ዥብግኒው ብርዜንስኪ እንደተናገሩት ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ በአሁኑ ጊዜም በኢትዮጵያ ውስጥ የፖለቲካ መነቃቃት ተፈጥሯል፡፡

ብርዜንስኪ እንዲህ የሚል የመከራከሪያ ጭብጥ አቅርበዋል፡

በሰው ልጆች ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሁሉም የሰው ልጆች ሁሉ የፖለቲካ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ናቸው፣ የፖለቲካ ንቃታቸው ከፍ ብሏል እናም የፖለቲካ ተሳትፏቸው እየጨመረ የመጣበት ሁኔታ ተከስቷል…የዓለም አቀፉ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውጤት በዓለም አቀፍ ደረጃ ለበርካታ ዘመናት በቅኝ ግዛት ትዝታ እና በአገዛዝ የበላይነት ተቀፍድዶ የኖረው ሕዝብ በአሁኑ ጊዜ ለግል ክብር መጨመር፣ ለባህል መከበር እና ለኢኮኖሚ ዕድሎች ጥያቄዎችን በማቅረብ ላይ በመገኘቱ ምክንያት ነው…ለክብር የሚጠየቀው ዓለም አቀፍ ጥያቄ ለዓለም አቀፉ የፖለቲካ መነቃቃት ዋና መሰረታዊ ክስተት ነው…ያ መነቃቃት ማህበራዊ መጠኑ ግዙፍ እና ስር ነቀቀል የፖለታካ ጥያቄ ነው… ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ዓለም አቀፍ የሬዲዮ፣ ቴሌቪዥን ስርጭት እና እየጨመረ የመጣው የኢንተርኔት አገልግሎት የፖለቲካ ወይም የኃይማኖት ጉዳዮችን መስመር እያስያዘ ለመብቱ እና ለወደፊቱ ብሩህ ተስፋ ሲል የጋራ ግንዛቤ ያለው ማህበረሰብን በመፍጠር ላይ ይገኛል፡፡ እነዚህ ኃይሎች ዓለም አቀፍ ወሰንን በመሻገር በአሁኑ ጊዜ ባሉት መንግስታት እንደዚሁም ባለው ዓለም አቀፍ ተዋረድ ላይ መገዳደሮችን በመፍጠር ላይ ይገኛል… 

የሶስተኛው ዓለም ወጣቶች በተለይ እረፍትየለሽ እና በቀልተኞች ናቸው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ አሁን ያሉበት የሕዝብ የመጨመር አብዮትም የፖለቲካ የጊዜ ፈንጂ ቦምብ ነው…የወጣቶቹ የወደፊት አብዮተኞች የመሆንም ሁኔታ በርካታ ተማሪዎች የሶስተኛ ደረጃ የከፍተኛ ትምህርት በታዳጊ ሀገሮች ተከታታይ እና በምሁራን ካምፕ ውስጥም የሚገኙ በመሆናቸው የሁኔታው መከሰት ጎልቶ በመውጣት ላይ ይገኛል… 

የዓለም ዋና ዋና ኃይሎች፣ አዲሶቹ እና የቀድሞዎቹ አስደናቂ ከሆነ እውነታ ጋር ተጋፍጠዋል፡ የጦር ኃይላቸው አደገኛነት ከምንጊዜውም በላይ የበለጠ ሆኖ የሚገኝ ቢሆንም የፖለቲካ መነቃቃት በተፈጠረበት ማህበረሰብ ላይ በመግባት ሁኔታውን ለመቆጣጠር መሞከር በጣም ዝቅተኛ የሆነ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡ አቅምን የሚገድብ ስለሆነ ማለት ነው፡፡ ጉዳዩን በግልጽ ለማስቀመጥ በዱሮ ጊዜ አንድ ሚሊዮን ሕዝብ በአካል ከመግደል ይልቅ አንድ ሚሊዮን ሕዝብን መቆጣጠር ይቀል ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን አንድ ሚሊዮን ሕዝብን ከመቆጣጠር ይልቅ አንድ ሚሊዮን ሕዝብን መግደል መቁጠር ከሚያስችል በላይ ቀላል ነገር ነው፡፡   

ለዘ-ህወሀት የተገኙት ትምህርቶች ቀላል እና እንዲህ የሚሉ ናቸው፡

70 በመቶ ያህሉን የሕዝብ ብዛት የሚይዙት የኢትዮጵያ ወጣቶች ሕዝባዊ የእምቢተኝነት አመጹን እና አብዮቱን የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ መሪዎች እና ሌሎች ቀሪዎች ሳይሆኑ ወጣቶቹ በመምራት ላይ ይገኛሉ፡፡

የኢትዮጵያ ወጣት ሕዝቦች የሰብአዊ ክብር እና ሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ በመጠየቅ ላይ ናቸው፡፡ ይኸ ነገር ምንም ዓይነት ድርድር ሊቀርብበት የሚችል ጉዳይ አይደለም፡፡

የኢትዮጵያ ወጣት ሕዝቦች እረፍትየለሾች እና በቀልተኞች ናቸው፡፡ ምንም ዓይነት ትዕግስት የላቸውም፡፡ እንደ እቃ ሊገዙ ወይም ሊሸጡ አይችሉም፡፡

የኢትዮጵያ ወጣት ሕዝቦች በዘ-ህወሀት የጭቆና አገዛዝ የሁለተኛ ዜግነት ባርነት ተጭኖባቸው የሚገኙ ስለሆነ በዚህ መቅነቢስ ዘረኛ ስርዓት ታመዋል፣ ደክመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ወጣት ሕዝቦች የዘ-ህወሀት መሪዎች ባልሰለጠነው አውሪያዊ ምዕናባቸው ከሚስሉት በእጅጉ የበለጠ ስረነቀል ለውጥን ናፋቂ እና ለተግባራዊነቱም ሌት ከቀን የሚታገሉ የህብረተሰብ ክፍሎች ናቸው፡፡

ዘ-ህወሀት አንድ ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ከመቆጣጠር ይልቅ አንድ ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን መግደል በእጅጉ ይቀለዋል፡፡

የዘ-ህወሀት ወታደራዊ ኃይል አደጋ ጣይነት ከምንጊዜውም በላይ ከፍተኛ ነው፣ ሆኖም ግን ከኢትዮጵያ ወጣቶች ኃይል ጋር ስናነጻጽረው በአውሎ ነፋስ ዉስጥ አንዳለ የላባ ያህል ነው፡፡

እንግዲህ የዘ-ህወሀት ዕድል እንደዚህ ነው፡፡

ዘ-ህወሀት ባዶ ይሆናል እናም ወደታሪክ ቆሻሻ መጣያ ቅርጫት ይጣላል፡፡

ዘ-ህወሀት ማወቅ ያለበት አንድ የማይሞት እና የማይበገር ሕግ አለ፡፡

ያንን ሕግ ያቀናበሩት ማህተመ ጋንዲ ሲሆኑ ሕጉ እንዲህ የሚል ነው፡

“ጨቋኞች እና ገዳዮች ለጊዜው የማይበገሩ መስለው ይታያሉ፣ ሆኖም ግን በመጨረሻ ሁልጊዜም ቢሆን ይወድቃሉ፣ አስቡት ሁልጊዜ፡፡“

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!  

መስከረም 17 ቀን 2009 ዓ.ም

Filed in: Amharic