>

ተራራም ይሰረቃል? የራስ ዳሽኑ ፖለቲካ [ክንፉ አሰፋ]

Ras Dashen ራስ ዳሸን  ተራራ ከትግራይ “ክልል” ካርታ የመውጣቱ አሲዮ ቤሌማ  በብሄራዊ  ቴሌቪዥን ሲነገር፤  “ደፍረውናል! ንቀውናል! ብታምኑም ባታምኑም በቁም ሞተናል!” የሚለው የኮሎኔል መንግስቱ ንግግር በጆሮዬ ላይ አቃጨለ። ድፍረቱ እና ንቀቱ እንዳለ ሆኖ፣ በቁም የሞቱት ግን እኛ ሳንሆን እነሱ መሆናቸውን የሚያበስር የዜና እወጃ ነበር።

ነገሩ እንጂ ሁሉም የተለመደ ነገር ነው። ውሃ ይጠፋል፣ መብራት ይጠፋል፣ ስልክ ይጠፋል፣ ገንዘብ ይጠፋል፣ ኮንዶሚንየም ህንጻም ይጠፋል። ይህ በህወሃት ፖለቲካ ጥርሳቸውን ላልነቀሉትም አዲስ ነገር አይደለም።  ዘረፋም ለነሱ አዲስ አይደለም። መንግስት ሆነው ከተቀመጡ በኋላ እንኳን 10 ቶን ቡና ሰርቀዋል፣ የመብራት ጀነሬተሮች  ሰርቀዋል፣ ከብሄራዊ ባንክ ወርቅ ሰርቀዋል… የህዝብን ድምጽም በተደጋጋሚ ሰርቀዋል። ተራራ ተሰርቆ ሲመለስ ግን የመጀመርያው ነው።

ከኢትዮጵያ አንደኛ፣ ከአፍሪካ ደግሞ በከፍታ 4ኛው ተራራ ነው ራስ ዳሸን። ከሰሜንጎንደር ከየዳ ወረዳ ተሰርቆ ለ25 አመታት ሙሉ ትግራይ ክልል ገብቶ ነበር። ወንጀሉ ወደ ትግራይ “ክልል” መግባቱ ብቻ አይደለም። አንድ ትውልድ  እና በስነ-ምድር ሳይንስ በውሸት ታሪክ እንዲታነጽ መደረጉ እንጂ!

በነገራችን ላይ በመላው ሃገሪቱ መስከረም 2 ላይ  መጀመር የነበረበት ትምህርት እስካሁን አልተጀመረም። ምክንያቱም ግልጽ ነው። ተማሪዎች እየተካሀደ ያለውን  አመጽ መጨረሻው ደረጃ ያደርሱታል በሚል ስጋት ነው። በሁለተኛው አለም ጦርነት ግዜ እንኳን ትምህርት አልተቋረጠም ነበር።  ሂትለር ትምህርት እንዳይቋረጥ አዝዞ ነበር። ጦርነት እየተካሄደም፣  ትውልድ እንዳይጠፋ ውስጥ ለውስጥ ትምህርት ይሰጥ ነበር።   የኛዎቹ  ጉዶች ግን ለአራት ወይንም አምስት ሰዎች ስልጣን ጥማት ሲባል “ትምህርት ገደል ይግባ” ያሉ ይመስላል።

ለመሆኑ ማን ነው ወንጀለኛው? መምህሩ፣ ህዝቡ ወይንስ ስርዓቱ?  በመማርያ ካሪኩለም ውስጥ ራስ ዳሽንን ትግራይ ካርታ ውስጥ አስገብተው፣ መጽሃፍም አሳትመው ሲያበቁ ፣ የንግድ ድርጅቶቻቸውን ዳሽን ባንክ፣ ዳሽን ቢራ… እያሉ የሰየሙት የ”አማራው” ተወካዮች ከዶሮ ያልታሻለ ጭንቅላት ይዘው፣ ስብእናቸውን እና ማንነታቸውን ጥለው ፓርላማ የተባለው ጉረኖ ውስጥ ተሰግስገዋል።

አንድ ትውልድን በዘረኝነት መርዝ ብቻ ሳይሆን በዚህ አይነት ውሸት ክመረዙ በኋላ ይቅርታ መጠየቁ ምን ይበጃል? በፈተና ግዜ ራስ ዳሽን ተራራ የሚገኘው በሰመን ጎንደር  ነው ብለው የወደቁትስ የአእምሮ ካሳ ሊከፈላቸው ነው?  የህወሃት ሰዎች አፍ እንጂ ጆሮ ስለሌላቸው ጥያቄዎችወች እንጂ አንድም መልስ አናገኝም።

ለመጀመርያ ግዜ ከህወሃት አንደበት ይቅርታ የሚል ነገር ሰማን ልበል? አንድ የፖለቲካ ተንታኝ በአንድ ወቅት ሲናገር የበታችነት ስለሚሰማቸው ይቅርታን ከሌላው ይሿታል እንጂ ፈጽሞ አይሏትም እንዳለ ትዝ ይለኛል። ይህ አንደኛው መጨረሻውን ጠቋሚ መሆኑ ነው።  በመጨረሻም እንዲህ ይሆናል። የፖለቲካ እስረኞች ይፈታሉ። ይቅርታ ማለት ይጀምራሉ። አጠር ያለች ረጅም የአብዮት ትንታኔ!

ይህ ይቅርታ ከመባሉ ሳምንታት በፊት፣ ሰላሳ ሚሊዮን አማራን ማጥፋት የሚችል ሃይል እንዳላቸው ደብረጽዮን በፌስ ቡክ ገጻቸው ጽፈውልናል። “አባ በጠጡ አቃቢቱን…”  እንዲሉ ይህንን የደብረጽዮን ጽሁፍ ሃይለማርያም ተቀብለው ሲያበቁ በመገናኛ ብዙሃን ቀርበው አንቦርቅቀውታል። “አብዮታዊ ሰራዊቱ ሕዝቡን እንዲገድል ትእዛዝ ሰጥቻለሁ!” ያሉ መሰለኝ። ለማመን እስኪከብድ ሂትለራዊ ቀረርቶ እና ፉከራም ሳይቀር አሰምተውናል።   እነ አቦይ ስብሃት ታዲያ ጥጋቸውን ይዘው፣ በጨበጡት ብርጭቆ ሰንጥቀው እየመነጠሩዋቸው “ደፋር!” ሳይሏቸው አልቀረም።   “ስልብ፣  በጌታው ብልት ይፎክራል!”  ይላሉ አበው።

ሕዝብን ለመጨረስ ትዕዛዝ  አስተላልፈናል ያሉበት አንደበታቸው ገና ሳይዘጋ ከጎንደር የሰረቅነውን ተራራ መልሰናል። ይህንን ተራራ ትግራይ ላይ አኑረነው ስለነበር ይቅርታ! ብለው መናገራቸው  ጨዋታ የመቀየር ስልት መሆኑ ነው።   ሕዝብ ቀድሟቸው ባይሄድ ኖሮ ሊሸውዱት ይሞክሩ ነበር። የተለመደ ነጠላ ዜማ፣ በተመሳሳይ ግጥም –  በተመሳሳይ ዜማ ይዘው መከሰታቸው ግን ከእንሰሳ እንኳን ያልተሻሉ መሆናቸውን  የሚያሳይ ነው።   ህዝቡን የሚያዩበት መነጽር አሁንም አልቀየሩትም።

ራስ ዳሽንን ከይቅርታ ጋር ለባለበቱ መልሰናል ብለዋል። ከዚህ ቀደምም የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ተገቢ ነው ብለውናል። የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ተገቢ መሆኑን የባነኑት የአማራ ሕዝብ ሲነሳ መሆኑ ግን የፖለቲካ ጨዋታውን ቀልድ አስመስሎታል። በዚህ አላበቁም ለፈሰሰው የወገናችን ደም ካሳ እንደሚከፍሉም ተናግረዋል።  የሰው ልጅን ህይወት እንደ እቃ ቆጥረው ሲያበቁ  በገዛ ራሱ  ገንዘብ ሊክሱት ቃል መግባታቸው የባሰ ያሳምማል።   የህይወት ካሳ አለ እንዴ?  ለመሆኑ የአንድ ሰው ነብስ ስንት ያወጣል?

የራስ ዳሽን መመለስ ኢትዮጵያ አሁን የገባችበትን ችግር አይፈታውም። የሕወሃትን ማንነትን ግን የበለጠ ይፋ አድርጎታል።

Filed in: Amharic