>
5:14 pm - Sunday April 20, 7383

የ1776 ዓ.ም. የአሜሪካ ነጻነትን ያበሰረዉን መግለጫ በማወደስ፣[ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም]

Dec of Indep
 ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

“አንድ  ተደናቂን  ነገር አስመስሎ  መስራት  ከልክ ያለፈ የሙገሳ መግለጫ እውነተኛ ባህሪ ነው“ የሚል የቆየ አባባል አለ፡፡ስለዚህ፣  ይህ ትችትም  እኔ የአሜሪካ የነጻነት መግለጫ  ተመሳሳይ ጥሁፍ  በሙገሳ  መልክ  ይታይልኝ  ፡፡

እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/1776 የእንግሊዝ በአሜሪካ ያሉት የቅኝ ግዛቶች የ ነጻነት መግለጫቸዉን  (በትክክለኛው ቃል ለመግለጽ የትጥቅ ትግል ጥሪ በማቅረብ)  በ ሁለተኛው አህጉራዊ ጉባኤ (ኮንግረስ ) ለዓለም ህዝብ አበሰሩ ፡፡

በእኔ አመለካከት የነፃነት መግለጫ ው  ለ አሜሪካን ብቻ አልነበረም አለምን ሁሉ ይጨምራል ፡፡

ሀምሌ 4 ለእኔ ልዩ ቀን ናት፡፡

እንደዚሁም ሁሉ እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/2016 ለእኔ ልዩ ቀና ናት፡፡

እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/2016 የኢትዮጵያን የሰብአዊ መብት ጥበቃ ትግል ማስፋፋት የጀመርኩበትን 10ኛውን ዓመት አከብራለሁ፡፡

እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/2006 ግልጽ እና ይፋ በሆነ መልኩ የሰብአዊ መብት ጥበቃን በተለይም የኢትዮጵያን የሰብአዊ መብት ጥበቃ አጠናክሮ ለመቀጠል ወደተግባራዊ እንቅስቃሴ ዘው ብየ ገባሁ፡፡ (ጊዜ እንዴት ይበራል እባካችሁ!)

“በትልቁ እንነቃቃ“ በሚል ርዕስ የተዘጋጀው እና 7860 ቃላትን አካትቶ በያዘው መግለጫዬ ወደ ኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ጥበቃ ለምን እንደገባሁ እና ሌሎች ኢትዮጵያውያንንም በተመሳሳይ መልኩ እንደዚህ ያለውን ተግባር እንዲፈጽሙ ጥሪዬን አቅርቤ ነበር፡፡ ያ ያወጣሁት መግለጫ “በአሜሪካ ውስጥ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በሀገር ቤት ለውጥ ማምጣት ይችላሉን?“የሚል ንኡስ ርዕስ ነበረው፡፡

በመግለጫዬ ድልን ለመቀዳጀት በጦር ሜዳ ውስጥ በመሰለፍ በደም እየተነከሩ እና የሬሳ ቁልልን በማስተናገድ ሳይሆን መልካም አስተሳሰብ ባላቸው ወንድ እና ሴት ኢትዮጵያውያን ልብ ውስጥ ሰላምን እና ሰላምን ብቻ መሰረት ያደረገ የሰብአዊ መብት ጥበቃ ትግልን በኢትዮጵያ ስናካሄድ ነው ብዬ አወጅኩ፡፡

ላለፉት አስር ዓመታት የኢትዮጵያውያንን እና በዓለም ላይ የሚገኙ መልካም አስተሳሰብ ያላቸውን ሰዎች አእምሮ እና ልብ በማሸነፍ በሳምንታዊ የሰኞ ትችቶቼ (አሁን በቅርቡ ደግሞ ሐሙስ) መውጣት በጀመሩት ትችቶቼ የተጠናከረ ትግሌን ሳካሂድ ቆይቻለሁ፡፡

በርካታ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖሩ እና የዲያስፖራውን ማህበረሰብ ወገኖቻችንን ልብ እና አእምሮ በማሸነፍ በተለይም ብዛት ያላቸው አንባቢዎቼ የአማርኛውን ትርጉም ትችቶቼን በሚያነቡ ወገኖቼ ዘንድ ስኬትን  አስመዝግበናል ብየ አምናለሁ፡፡

ያለፉት አስር ዓመታት ያለምንም ጥርጥር ለእኔ በህይወቴ የተሻሉ ዓመታት ናቸው ማለት እችላለሁ፡፡ በብዕሬ (በተለይም በኮምፒውተር የፊደል መምቻ ) በመጠቀም የሰብአዊ መብት ጥበቃ፣ የዴሞክራሲ፣ የህግ የበላይነት እንዲጠበቅ እና የኢትዮጵያ ነጻነት እንዲረጋገጥ ሁልጊዜ በየሳምንቱ (አንድም ሳምንት ሳላሳልፍ) በእነዚህ አስር ዓመታት ሙሉ የመታገል ዕድልን ተጎናጽፌ እገኛለሁ፡፡

የሰውን አእምሮ እና ልብ ለመማረክ በሚደረገው ትግል እንግሊዛዊው ደራሲ ኤድዋርድ ቡልዌር በግጥም ስንኞቻቸው እንዲህ በማለት ያስተላለፉት መልዕክት ይህንን ጉዳይ በተሻለ ሁኔታ ይገልጸዋል፡ “እውነት፣ ይህ ነው! ሙሉ በሙሉ ግዙፍ ከሆነው ከሰዎች የባርነት አገዛዝ ቀንበር ውስጥ ነጻ ለመውጣት ብዕር ከጎራዴ የበለጠ ኃይል አለው፡፡ ምድርን ትንፋሽ አሳጥተው የሚኖሩትን የቄሳሮችን አስከፊ አገዛዝ ሽባ ለማድረግ እና ለማመጽ ብዕር ብቸኛው መሳሪያ ነው…“ በማለት ግልጽ አድርገውታል፡፡

ሸክስፒር ሲጥፍ ፣ “በርካቶች ሰንጥቆ የሚጥለውን ጎራዴ የታጠቁ አምባገነኖች አንዲት የላባ ብዕር በሚያዩበት ጊዜ በፍርሀት ይርበደበዳሉ ፣ ድፍረታቸውም እንደ አባይ (ቃሉ ላላ ተድርጎ ይነበብ) ስንቅ እየቀለለ እና እየሳሳ ይሄዳል“ ነበር ያለው፡፡

ሆኖም ግን የቶማስ ጃፈርሰንን ለቶማስ ፔይኔን የሰጡትን ምክር እከተላለሁ፡ “በሌሎች ጊዚያት በጎራዴ ኃይል ሲሰሩ የነበሩትን ነገሮች   አንተ ደግሞ በብዕር  መታገሉን ቀጥለ ”  ነበር ያሉት፡፡

ፔይኔ አምባገነኖችን በጽኑ የሚያወግዙ፣ ነጻነትን ፍቅርን በተላበሰ መልኩ የሚጠብቁ እና ህዝቦች ከህግ አግባብ ውጭ ነጻነታቸውን የሚገፉትን እና የሚጨቁኗቸውን አምባገነኖች ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ማስወገድ ይቻላል በማለት ሲያስተምሩ የነበሩ ታላቅ አሜሪካዊ አርበኛ ነበሩ፡፡

አሁን በህይወት የሌሉት እና የኢትዮጵያዊነት የፍቅር ምሁር የነበሩት ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን ቶማስ ፔንን  (“ስለሰው ልጆች መብት“ የጻፉትን እና የሽግግር ሰብአዊ መብትን አስመልክቶ በየጊዜው ዲስኩር ሲያቀርቡ የነበሩትን)  ታስታዉሰኛለህ ይሉኝ ነበር ፡፡

እ.ኤ.አ ነሀሴ 2014 እንዲህ በማለት በእራሴ ትችቶች ላይ ትችት አቀርቤ ነበር፡ “በየሳምንቱ ጽሁፍ የማወጣ ቢሆንም ቅሉ እራሴን በአምባገነኖች ላይ ሰነድ እና ጽሁፍ አቅራቢ አድርጌ ቆጠርኩ፡፡“ የዘመናዊ ትችት ጽሁፍ ስራዎች ከመውጣታቸው በፊት ባለፉት ዘመናት በወንዶች እና በጥቂት ሴቶች ጠንካራ የሆነ ሀሳብን የሚያራምዱ ሰነዶችን እና ጽሁፎችን በማውጣት በወቅቱ በአካባቢያቸው ይመለከቱት የነበረውን ጉዳይ ለማህበረሰቡ በማቅረብ ለታሪክ ምስክርነት የምያስቀመጡ ዜጎች ነበሩ ፡፡

ስለሆነም ጀፈርሰን ለፔይኔ እንደነገሯቸው ሁሉ እኔም በተመሳሳይ መልኩ ብዕሬን ሌሎቹ በጎራዴዎቻቸው እንደሚያደርጉት ሁሉ  አደርጋለሁ፡፡

ለመናገር የሚዘገንነውን እና በአምባገነኑ መለስ ዜናዊ እና በህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ (ዘ-ህወሀት) እንዲሁም ስሙ በዓለም አቀፍ የሽብርተኞች የመረጃ ቋት ውስጥ ተመዝግቦ በሚገኘው ቅጥር ነብሰ ገዳይ ቡድን በኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጸመውን እልቂት በብዕሬ በማጋለጥ ድምጽ ለሌላቸው የጥቃት ሰላበዎች ድምጽ  በመሆን ድምጼን ከፍ አድርጌ በማሰማት ስታገል ባለፉት አስር አመታት ቆይቻለሁ፡፡

በዘ-ህወሀት እየተሰቃዩ ላሉት በሺዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞች፣ ጋዜጠኞች እና ሰላማዊ አመጸኞች እንዲሁም በዘ-ህወሀት ግዴለሽነት እና ብቃት የለሽነት ምክንያት እ.ኤአ. በ2016 በበርካታ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩትን የረሀብ ሰለባ የሆኑትን ወገኖቻችንን የጥቃት ሰለባ ያደረገውን አውዳሚ ረሀብ ከዓለም አቀፍ የድህነት አቃጣሪ ወትዋቾች ጋር በማበር ከኢትዮጵያውያን እና ከዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዕይታ በመደበቅ ስኬታማ ቢሆኑም ምስከርነቴን በመስጠት በመታገል ላይ እገኛለሁ፡፡

ማሪያን ራይት ኤድልማን የተባሉት ታዋቂ አሜሪካዊ የህጻናት መብት ተሟግች በአንድ ወቅት እንዲህ የሚል ምልከታ አድርገው ነበር፣ “በኢፍትሀዊነት ላይ ቁንጫ መሆን አለባችሁ፡፡ የተጠናከሩ እና በቂ የሆነ ቁንጫዎች ስልታዊ በሆነ መልኩ  ግዙፍ የሆነውን ውሻ  ምቾት በማሳጣት መድረሻ ሊያሳጡት ይችላሉ፡፡ “እንደዚሁም ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ ትልቁን ሀገር ወደተሻለ የኑሮ ሁኔታ ለማሸጋገር ይቻላል“ ነበር ያሉት፡፡

ላለፉት አስር ዓመታት ለዘ-ሀወሀት ቆሻሻ እና እርባና ቢስ ውሻ ቁንጫ ሆኘበት ቆይቻለሁ፡፡ የዘ-ህወሀትን ቆሻሻ ውሻ ስልታዊ በሆነ መልኩ ለመጠዝጠዝ እና ምቾቱን ለማሳጣት በቂ የሆኑ ቁንጫዎችን እንፈልጋለን፡፡

ለአሜሪካ የነጻነት ድንጋጌ ልዩ መግለጫ ምስጋና በማቅረብ በኢትዮጵያ ውስጥ ሳካሂደው የቆየሁትን 10ኛውን ዓመት በዓል ሳከብር ታላቅ ኩራት ይሰማኛል፡፡

ለእኔ ኢትዮጵያዊ አሜሪካዊ ማለት እንዲህ የሚል ሆኖ ይገኛል፡ “እ.ኤ.አ በ1776 በአሜሪካ ውስጥ ቦገግ ብሎ የበራውን ችቦ  እ.ኤ.አ በ2016 በኢትዮጵያ ውስጥ የብርሀን ፍንጣቂ እንዲሰጥ ማድረግ መቻል ነው“ የሚል ነው፡፡ (ይህንን በሚመለከት ወደፊት በስፋት የምገልጸው ይሆናል፡፡)

እ.ኤ.አ ሀምሌ 2007 “በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ጥበቃ መግለጫ“ በሚል ርዕስ በ74 ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች ተፈርሞ ለሕዝብ ይፋ የተደረገው የድረ ገጽ መስመር አቤቱታ ለእኔ ታላቅ ክብር እና ሞገስ ይሰጠኛል፡፡ (በዚያ ወቅት የፈረሙትን ሰዎች ስም ዝርዝር በዚህ ጽሁፍ በስተመጨረሻ ላይ ይመልከቱ፡፡)

ይህ ድንጋጌ እኔ ሁለተኛውን የጸሐይ ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ጥናቶች ጉባኤን በዳላስ ቴክሳስ በመከታተል ላይ እያለሁ ያዘጋጀሁት ረቂቅ ነበር፡፡ ያ ጉባኤ በአዲሱ ሺህ ዘመን ከሁሉም የስራ መስክ የተውጣጡ ኢትዮጵያውያን በአንድ ላይ ሆነው ስለኢትዮጵያ የወደፊት ዕጣ ፈንታ የመከሩበት ጉባኤ በመሆኑ በአንክሮ የሚታወስ እና የሚያነሳሳ ነበር፡፡

ይህ የነጻነት ድንጋጌ ከዩኤስ አሜሪካ የነጻነት ድንጋጌ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ የተደረገ የነጻነት ድንጋጌ ነው፡፡

በነጻነት ድንጋጌው ውስጥ ያሉት እና እንዲህ የሚሉት የማይሞቱ የነጻነት ድንጋጌው ቃላት ሁልጊዜ እንድነሳሳ ያደርጉኛል፡

“ከፈጣሪያቸው የተሰጧቸውን እና ሊነጣጠሉ የማይችሉ መብቶች ማለትም በሕይወት የመኖር፣ በነጻነት እና በደስታ ለመኖር ሁሉም ሰዎች እኩል ሆነው ተፈጥረዋል የሚሉትን እውነታዎች እርግጠኝነት ይዘናል፡፡ እነዚህን መብቶች ለመጎናጸፍ ከሰዎች ተውጣጥተው የሚገዛው (ተገዥው) ህዝብ በሚፈልገው መሰረት ፍትሀዊ በሆነ መልኩ ለማስተዳደር እንዲቻል መንግስታት ተቋቁመዋል፡፡ ለእነዚህ መብቶች አውዳሚ የሆነ ማንኛውም የመንግስት ዓይነት ህዝቡ እርሱን የመለወጥ ወይም ደግሞ የማስወገድ መብት ያለው ሲሆን በእነዚህ መርሆዎች ላይ የተመሰረተ እና የሕዝቦችን ደህንነት እና ደስታቸውን የሚያረጋግጥ አዲስ መንግስት የማቋቋም መብት አላቸው“ ይላል፡፡

ሁሉም ወንዶች እና ሴቶች በፈጣሪያቸው እኩል ሆነው ተፈጥረዋል፣ እንደዚሁም በህይወት የመኖር፣ በነጻነት እና በደስታ ለመኖር ነጻ ሆነው ተፈጥረዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ የመንግስት ብቸኛው ተግባሩ እነዚህን መብቶች መጠበቅ እና መንከባከብ ነው፡፡

በሕዝቦች መፈቃቀድ ላይ በሚመሰረት መንግስት አምናለሁ፡፡ በአንድ ምርጫ ላይ መቶ በመቶ የህዝብ ድምጽ አግኝቼ አሸንፊያለሁ በማለት ማንም የመንግስት አገዛዝ በሕግ የመጠየቅ መብት የለውም፡፡ ሆኖም ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት የዘ-ህወሀት ሀፍረተቢስ ወሮበላ ዘራፊዎች እ.ኤአ. ግንቦት 2015 ተካሄደ የተባለውን የይስሙላ የቅርጫ ምርጫ መቶ በመቶ አሸነፍን በማለት ዓይን ባወጣ መልኩ አውጀዋል፡፡

ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እ.ኤ.አ ሀምሌ 2015 ኢትዮጵያን ጎበኘ፣ እናም መቶ መቶ ምርጫውን አሸንፊያለሁ እያለ የሚጠራውን ዘ-ህወሀትን ዴሞክራሲያዊ መንግስት ነው ብሎ ጠራው፡፡

ኦባማ የእርሱን ወሮበላ ዘራፊዎች እና ሌባ ጓደኞቹን ለመጠበቅ ሲል እስከ ጥርሱ ድረስ ተራ ቅጠፈቱን ከለቀቀ በኋላ የመብት ተሟጋች ጀግና መስሎ በአስመሳይ ምላሱ ሲያታልል ቆይቶ በወሳኙ ወቅት ላይ በሲቪል መብቶች ትግል ላይ የወደቀ ወራዳ ሆኖ አገኘሁት፡፡ የእራሱን ጀግና በውሸት ጥቅጥቅ ጫካ ውስጥ ያጣ ፍሬ ከርስኪ  ሰው እንደሆነ ተሰማኝ፡፡ እናም ከዚያን የለየለት የውርደት ጊዜ ጀምሬ በማክበር እርስዎ እያልኩ መጥራቴን ወደ ጎን አሽቀንጥሬ በመጣል አንተ እያልኩ መጥራቱን ተያያዝኩት፡፡

በቁስል ላይ እንጨት እንዲሉ ኦባማ እ.ኤ.አ ነሀሴ 2014 አስከፊ የሆኑትን የአፍሪካ አምባገነን ወሮበላ ዘራፊ መሪ ተብየዎች በኋይት ሀውስ በመሰብሰብ የቸበርቻቻ የመድረክ ላይ ተውኔቱን ሲያሳይ ነበር፡፡ ቅሬታየን  “የአፍሪካ ተውኔት” በሚል ርዕስ ባዘጋጀሁት ጽሁፍ ገልጨ ነበር፡፡ እነዚህ የሰብአዊ መብት ደፍጣጭ ወንጀለኞች ወደ ማጎሪያ እስር ቤት እንጅ ወደ ኋይት ሀውስ መጋበዝ እንዳልነበረባቸው አምናለሁ፡፡

እ.ኤ.አ በ2009 ኦባማ ወደ አክራ ጋና በመሄድ በአፍሪካ ህዝቦች ላይ እንዲህ የሚል ውሸት ዋሸ፡ “አሁን ምንም ዓይነት  አትጠራጠሩ ፣ ታሪክ ከጀግኖቹ አፍሪካውያን ጎን እንጅ መፈንቅለ መንግስት እያደረጉ ወይም ደግሞ የሕገ መንግስት ለውጥ በማድረግ በስልጣን ተጣብቀው ከሚኖሩት አምባገነኖች ጎን አይደለም፡፡ አፍሪክ ጠንከራ ሰዎችን አትፈልግም፣ ይልቁንም አፍሪካ የምትፈልገው ጠንካራ ተቋማትን ነው“ ነበር ያለው መንታ ምላሰ ረዥሙ ኦባማ፡፡

እ.ኤ.አ በ2016 ኦባማ ለአፍሪካ ጠንካራ ሰዎች የዘላለም ምርጥ ጓደኛ ሆኗል፡፡

የመጀመሪያው አፍሪካ አሜሪካዊ ፕሬዚዳንት እና ጠቅላላ የክንውን ተግባራቱን ወደ አንድ የፖሊሲ አቅጣጫ ላይ አነጣጥሮ ስለሚገኘው ስለኦባማ ባለኝ አመለካከት ጥቂት ሰዎች ትችቴ ጠንከር ያለ ነው የሚሉ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ሆኖም ግን ኦባማ ስሀገር ውስጥ የፖሊሲ ክንውኖች ስላለው ግላዊ ብቃት አደንቃለሁ፡፡ በአፍሪካ ላይ ካለው ጥቂት ፖሊሲ በስተቀር ከኦባማ ጋር ጠብ የለኝም ፡፡

እራሴን የመርህ እና የሀሳብ ሰው አድርጌ እቆጥራለሁ፡፡ ለዚህም ይመስለኛል የኦባማ አስመሳይነት ጭንቅላቴን በከፍተኛ ሁኔታ የመታው፡፡

እ.ኤ.አ በ2010 ያመጣው የመንግስት ዘገባ ንግግር ላይ ኦባማ እንዲህ የሚል መልዕክት አስተላልፏል፣ “በመጨረሻ አሜሪካንን የገነቧት የእኛ ሀሳቦች፣ የእኛ እሴቶች – ከእያንዳንዱ የዓለም ማዕዘን በመጡ ዜጎች እንድትገነባ የፈቀድንባቸው እሴቶች፣ ዜጎቻቻችንን እስከ አሁንም ድረስ ወደፊት እንዲሉ የሚያስችሉ እሴቶች ስላሉን ነው፡፡   

እንደ አጋጣሚ በርካታዎቹ የእኛ ዜጎች በታላላቅ ተቋሞች – በኮርፖርሽኖቻችን፣ በብዙሀን መገናኛዎቻችን እና፣ አዎ፣ በመንግስታችን ላይ እነዚህን እሰቶች አጥተዋል“ በማለት የተናገረው ውኃ የሚቋጥር ነው፡፡

ሆኖም ግን በመጨረሻ የአሜሪካንን ሀሳቦች የገነቧት ምንድን ናቸው?

“ከፈጣሪያቸው የተሰጧቸውን እና ሊነጣጠሉ የማይችሉ መብቶች ማለትም በሕይወት የመኖር፣ በነጻነት እና በደስታ ለመኖር ሁሉም ሰዎች እኩል ሆነው ተፈጥረዋል የሚሉትን እውነታዎች እርግጠኝነት ይዘናል፡፡ እነዚህን መብቶች ለመጎናጸፍ ከሰዎች ተውጣጥተው የሚገዛው (ተገዥው) ህዝብ በሚፈልገው መሰረት ፍትሀዊ በሆነ መልኩ ለማስተዳደር እንዲቻል መንግስታት ተቋቁመዋል፡፡ ለእነዚህ መብቶች አውዳሚ የሆነ ማንኛውም የመንግስት ዓይነት ህዝቡ እርሱን የመለወጥ ወይም ደግሞ የማስወገድ መብት ያለው ሲሆን በእነዚህ መርሆዎች ላይ የተመሰረተ እና የሕዝቦችን ደህንነት እና ደስታቸውን የሚያረጋግጥ አዲስ መንግስት የማቋቋም መብት አላቸው …?“ የሚለውን ከጥርጣሬ ላይ ይጥለዋል፡፡

ኦባማ የለየለትን ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አገዛዝን ዴሞክራሲያዊ ነው ሲል እና ከጨካኞቹ የአፍሪካ  ደም መጣጭ ገዳዮዎች ጋር አብሮ ቸበርቻቻ ሲያደርግ የአሜሪካንን እሴቶች ከድቷል፡፡

በኦባማ አስመሳይነት፣ አታላይነት እና ቀጣፊነት እኔም እራሴ የክዳት ወንጀል እንደተፈጸመብኝ ሆኖ ይሰማኛል፡፡

እንግዲህ እንዲህ በሚሉት የቱፓክ ሻኩር የግጥም ስንኞች እፎይታን አገኘሁ፡ “ጀግናችሁ ከክብር ወድቆ ሲንከባለል ሁሉም ትረካዎች ሁሉ ሚስጠር መሆናቸው ይቀራል፣ ድብቆቹ ይፋ ይሆናሉ፣ ስቃዮችም ይጎላሉ…ጀግናችሁ ከክብር ወድቆ ሲንከባለል ከዋክብትም ይወድቃሉ፣ እንደዚሁም ሁሉ የነገውም አመለካከት አብሮ ይወድቃል፡፡ ከእኔ ጀግና ውጭ ሀዘኔን ለማጽናናት እኔ ብቻ ነው ያለሁት…“ ብለዋል፡፡

ለኦባማ ብቻ ሀዘን ይሰማኛል፡፡

ኦባማ በአፍሪካ ላይ ስላለው ፖሊስ ታሪክ ፍርዱን ይሰጠዋል፡፡ ማን ያውቃል? ምናልባትም አንድ ሰው መጽሐፍ በመጻፍ ኦባማ በአፍሪካ ላይ ስላለው ፖሊሲ ወደ ፍትህ አካል እንዲቀርብ በማድረግ ተጠያቂ የሚያደርግበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡

ያም ሆነ ይህ አምባገነንነትን ሙሉ በሙሉ መቃወም እና አምባገነናዊ የሆነን መንግስት ለመለወጥ ወይም ደግሞ ለማስወገድ የሕዝቡን መበት መደገፍ እና ለሕዝቦች ደህንነት እና ደስታ የሚቆመውን አዲስ መንግስት ለማቋቋም ጥረት ማድረግ እንዳለብን አምናለሁ፡፡

በእርግጥ ያሜሪካ የነጻነት መግለጫ  የመንፈስ ጥንካሬ ከሰጣቸው ሰዎች መካከል እኔ በትንሹ ደረጃ ላይ እገኛለሁ፡፡

በአሜሪካ የእርስ በእርስ ጦርነት አጋማሽ ጊዜ አብርሀም ሊንከን ከነጻነት ድንጋጌው የሞራል እና የመንፈሳዊ ኃይላቸውን በማጠናከር እ.ኤ.አ ሰኔ 1/1863 የጌቲስበርግ መልዕክታቸውን እንዲህ በማለት አስተላልፈው ነበር፣ “ከ87 ዓመታት በፊት የእኛ ቀደምት አባቶቻችን ነጻነት የተረገዘባት እና ሁሉም ሰዎች አኩል ሆነው ተፈጥረዋል ለሚለው መርህ ተገዥ በመሆን በዚህ አህጉር ላይ አዲስ ሀገር እውን አድርገዋል“ ብለዋል፡፡

ከ15 ዓመታት በኋላ እ.ኤ.አ. በ1848 በኒዮርክ በሴኔካ ፎልስ በተካሄደው የሴቶች መብቶች ስምምነት ጉባኤ ላይ በነጻነት ድንጋጌው ቃላት በመገፋፋት ለሴቶች የተለየ ድምጽ መሰጠት እንዲቻል እንዲህ በማለት የእራሳቸውን ሀሳብ የሚያቀርብ ድንጋጌ አቀረቡ፡ “በፈጣሪያቸው የተጎናፈፏቸውን ጥቂት ሊነጣጠሉ የማይችሉ መብቶችን ማለትም በህይወት የመኖር መብት፣ ነጻ የመሆን መብት እና በደስታ የመኖር መብትን በመጎናጸፍ ሁሉም ወንዶች እና ሴቶች እኩል ሆነው ተፈጥረዋል የሚለውን እውነታ ይዘናል… ለእነዚህ መብቶች አውዳሚ የሆነ ማንኛውም የመንግስት ዓይነት ሲከሰት እምቢ አሻፈረኝ አልገዛም የማለት መብት ያለው ህዝቡ ሲሆን በእነዚህ መርሆዎች ላይ በመመስረት የህዝቡ ደህንነት እና ደስታ የተጠበቀ ሆኖ ለመኖር  አዲስ መንግስት ማቋቋም የህዝቡ መብት ነው“ ብለዋል፡፡

ዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ እ.ኤ.አ ነሀሴ 28/1963 “ሕልም አለኝ“ በሚል ርዕስ ባደረጉት ንግግር የሚከተለውን አውጀው ነበር፡ “የእኛ ሬፐብሊክ መሀንዲሶች የሕገ መንግስቱን አስደናቂ ቃላት በሚጽፉበት ጊዜ እና የነጻንነት ድንጋጌን ባወጁበት ወቅት ማንኛውም አሜሪካዊ ከእነዚህ ህጎች ስር እንዲሆን የቃል ኪዳን ሰነድ ተፈራርመው ነበር፡፡ ይህ የቃል ኪዳን ሰነድ ማለትም ሁሉም ህዝቦች፣ አዎ ጥቁር ህዝቦች እንዲሁም ነጭ ህዝቦች የማይነጣጠሉ መብቶችን ማለትም በህይወት የመኖር መብት፣ ነጻ ሆኖ የመኖር መብት እና የደስታ ኑሮ የመኖር መብት እንዳላቸው የሚያረጋግጥ የቃል ኪዳን ሰነድ ነው“ ብለው ነበር፡፡

ማልኮም ኤክስ አሜሪካ እንደዚህ ያለውን የእራስ እውነታ ተግባራዊ ስለማድረጓ በድንጋጌው ላይ በማወጅ ክዷል፡፡ እንዲህ የሚል የክርክር ጭብጥ አቅርቦ ነበር፣ “አፍሪካውያን ወደ አሜሪካ እንዲጋዙ እየተደረጉ ባሮች እንዲሆኑ ተደርገዋል፣ እናም የጌቶቻቸውን ስም እንዲይዙ ተደርገዋል፣ በዚህም መሰረት ከሰብአዊነት እንዲወጡ ሆነዋል፡፡ “አስራሶስቱ ቅኝ ግዛቶች ነጻ ስለመሆናቸው እንዲህ በማለት ጥርጥሬውን አመላክቷል፡ “አስራሶስቱ ቅኝ ግዛቶች ከእንግሊዝ ተለያይተዋል ሆኖም ግን የነጻነት  መለጫ  ብለው ይጠሯቸዋል፣ ይልቁንም የመለያየት ድንጋጌ ብለው አይጠሯቸውም፣ የነጻነት ድንጋጌ እያሉ ይጠሯቸዋል፡፡ ከአንድ ሰው ነጻ ስትሆን ከእነርሱ መለያየት አለብህ፡፡ ከእነርሱ ካልተለያየህ ይህ ማለት ከእነርሱ ነጻ አይደለህም ማለት ነው፡

ማልኮም እስከ አሁን ድረስ በአሜሪካ ውስጥ የሚኖሩ 22 ሚሊዮን ህዝቦች የተሻለ ምግብ፣ የተሻለ ልብስ፣ የተሻለ መጠለያ፣ የተሻለ ትምህርት እና የተሻለ ስራ አሁኑኑ ማግኘት አለባቸው በማለት ለጥቁር ዜጎች ጥሪ በማቅረብ የእራሱን ሙሉ በሙሉ ነጻ የሆነ መግለጫ አወጀ፡፡

የነጻነት ድንጋጌ የአሜሪካ የነጻነት ወይም ደግሞ አምባገነንነትን በመቃወም የተዘጋጀ ሰነድ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ ማግና ካርታ ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ በዓለም ላይ ለሚገኙ ለሰው ልጆች ሁሉ የተዘጋጀ የመጨረሻ የነጻነት ድንጋጌ ነው፡፡

ድንጋጌው በአፍሪካ፣ በእስያ እና በላቲን አሜሪካ ለነጻነት እና የእራስን ዕድል በእራስ ለመወሰን የሚታገሉትን ለቁጥር የሚያዳግቱ በርካታ የሆኑ የጸረ ቅኝ ግዛት ንቅቀናቄዎችን አነሳስቷል፡፡

እ.ኤ.አ የ1930ዎቹ የማህተመ ጋንዲ የህንድ “የነጻነት ድንጋጌ” የተነሳሳው የአሜሪካንን የነጻነት ድንጋጌ መሰረት በማድረግ ነበር፡፡ ጋንዲ እንዲህ በማለት ጽፈዋል፡

“እንደሌሎች እንደማናቸውም ህዝቦች ሁሉ የህንድ ህዝቦች ነጻነት እንዲኖራቸው እና የጥረታቸውን ዋጋ እያገኙ በደስታ የመኖር ፍሬዎቻቸውን ማጣጣም ይኖርባቸዋል፡፡ በዚህም መሰረት ሙሉ ያልተገደበ እድገት ይኖራቸዋል፡፡ እነዚህን መብቶች የሚከልክል እና ህዝብን የሚጨቁን ማናቸውም መንግስት ካለ ህዝቡ መንግስትን የመለወጥ ወይም ደግሞ የማስወገድ መብት እንዳለው እናምናለን፡…በሀገራችን ላይ አራት ጊዜ እጥፍ በሆነ አስከፊ ሁኔታ ለመገዛት አሜን ብሎ መቀበል በሰው ልጆች እና በእግዚአብሄር ዘንድ ወንጅል ነው“ ነበር ያሉት፡፡

እ.ኤ.አ መስከረም 1945 ሆችሚን በሚከተሉት ቃላት የቬትናምን ዴሞክራሲያዊ ሬፐብሊክ ነጻነት እንዲህ በማለት አወጀ፡

“ሁሉም ሰዎች እኩል ሆነው ተፈጥረዋል፡፡ ሊነጣጠሉ የማይችሉ የተወሰኑ መብቶችን ማለትም በህይወት የመኖር መብት፣ በነጻነት የመኖር መብት እና በደስታ የመኖር መበርት በፈጣሪያቸው ተጎናጽፈዋል፡፡ ይህ የማይሞት መግለጫ የተደረገው እ.ኤ.አ በ1776 በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ የነጻነት ድንጋጌ ላይ ነበር፡፡ ሰፋ ባለ መልኩ ሲታይ ይህ ማለት ሁሉም በዚህች ምድር ላይ የሚኖሩ ሰዎች ከውልደታቸው ጀምሮ እኩል ናቸው፣ በህይወት የመኖር መብት እና በደስታ የመኖር መብቶች አሏቸው“ የሚል ነው፡፡

ሆችሚን በወጣትነት ዘመኑ ቦስተን (የአሜሪካ ነጻነት መለጫ ቤት ከሆነው) በመኖር በዩኤስ አሜሪካ ሲደረግ የነበረውን ለጸረ ቅኝ ግዛት እና የእራስን ዕድል በእራስ መወሰን የትግል አርዓያነት ተመልክቷል፡፡ ሆችሚን ከጉዳይ ሳይቆጠሩ የቀሩ ቢሆኑም እርዳታ በመጠየቅ ለፕሬዚዳንት ትሩማን በርካታ ደብዳቤዎችን ጽፏል፡፡ ሆኖም ግን የቬትናም ብሄረተኞች ወደ ኮሙኒዝም ተመለሱ፡፡ ቀሪው እንግዲህ ለታሪክ ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ1948 30 አንቀጾችን በማካተት የተዘጋጀው እንዲህ የሚለው የተባበሩት መንግስታት ዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብቶች ድንጋጌ የተወሰደው ከነጻነት ድንጋጌው ነው፡ “ሁሉም ሰዎች ነጻ እና እኩል ክብር እና መብቶች ያላቸው ሆነው ተፈጥረዋል…“(አንቀጽ 1)፡፡ “ማንኛውም ሰው በህይወት፣ በነጻነት እና በደህንነት የመኖር መብት አለው” (አንቀጽ 3)፡፡ “ማንኛውም ሰው የንብረት የባለቤትነት መብት እና ከሌሎች ሰዎች ጋር የመደራጀት መብት አለው፡፡ ማንም ቢሆን ከህግ አግባብ ውጭ በዘፈቀደ ንብረቱን አያጣም” (አንቀጽ 17)፡፡

ከሰብ ሰሀራ ሀገሮች በቅኝ ግዛትትነት በመያዝ እና ነጻነቷንም በማግኘት የመጀመሪያ የሆነችው የጋና የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት የነበሩት ክዋሜ ንክሩማህ እ.ኤ.አ ግንቦት 24/1963 በአፍሪካ አንድነት ድርጅት የምረቃ ስነስርዓት የመክፈቻ በዓል ላይ በመገኘት የነጻነት ድንጋጌን ከፍ አድርገው በማንሳት ስሜትን በቀላቀለ መልኩ ንግግር አድርገው ነበር፡፡

ንክሩማህ ለአዲሶቹ የድህረ አፍሪካ ቅኝ ግዛት መሪዎች እንዲህ በማለት ነግረዋቸው ነበር፣ “ነጻነት አዲስ እና የበለጠ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ ጉዳዮችን ለመገንባት፣ ባለን ዝንባሌ መሰረት ማህበረሰባችንን ለማሳደግ እና  የኒዮ ኮሎኒያሊስቶችን ቁጥጥር እና ጣልቃገብነት ለመደቆስ እና ለማዋረድ የመጀመሪያው ትግል ብቻ ነው“ ብለው ነበር፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ የሰብአዊ መብቶችን ለመጠበቅ በተዘጋጀው ድንጋጌ እና ድንጋጌውን በፈረሙት 74 ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች ላይ ከፍ ያለ ኩራት ይሰማኛል፡፡

ድንጋጊያችን ለጥቂት ሰዎች ምንም ዓይነት እርባና የሌለው ምንም ዓይነት ለውጥ ሊያመጣ የማይችል አድርገው እንደሚያስቡት እጠረጥራለሁ፡፡

ሆኖም ግን ጋንዲ እንዳሉት ሁሉ “ጥቂት ጠንካራ ጽናት ያላቸው መንፈሶች በማይበገር እምነቶች ለተልዕኮ የሚተኮሱ ከሆነ የታሪክን ጎዳና መቀየር ይችላሉ“ የሚለውን በአጽንኦ ማስታወስ ይገባል፡፡

እውነት ለመናገር የመግለጫችን ዋና ዓላማ የታሪክ ጎዳናን ለመቀየር አይደለም፣ ይልቁንም ለወደፊት ስላሉት ህልሞች ስኬት ትኩረት አድርጎ ይሰራል፡፡ ጃፈርሰን በአንድ ወቅት እንዳሉት “ካለፈው ታሪክ ይልቅ የወደፊት ህልሞችን እመርጣለሁ” ያሉት። እውነትም ትክክለኛ ምርጫ ነው፡፡

አንደዚያው ይሁን !

እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/2007 የተፈረመው የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት መግለጫ፣

በታላላቅ ሀገሮች ታሪክ ህዝቦች በእራሳቸው ጊዜ እራሳቸውን በአንድ ነገር አድርገው ወሳኝ ስራ ለመስራት የሚመርጡበት ጊዜ እንደሚኖር እና በርካታ መስዋዕትነትን በመክፈል በቀደምቶቻቸው ላይ ቅሬታን ከማቅረብ ይልቅ  በጽናት ትግሉን በማጠናከር ለመጭው ትውልድ ትሩፋትን በማውረስ ማለፍ ትልቅ ነገር ነው፡፡

እነዚህ ሰዎች ማቋረጫ በሌለው መንገድ አምባገነኖች በዓለም ባሉ ህዝቦች ላይ ንቀትን በማሳየት የሕግ የበላይነትን፣ የዴሞክራሲ መርሆዎችን እና የሲቪል ነጻነቶችን በመደፍጠጥ እብሪተኞቹ የአምባገነንነት አገዛዛቸውን በሚያራምዱበት ጊዜ የህዝብ ወገኖች እንደዚህ ያለ ምርጫን ለመምረጥ ይገደዳሉ፡፡

በጭቆና አገዛዝ ታሪክ ውስጥ አምባገነኖች የህዝቦቻቸውን የተፈጥሮ ድፍረት በመሸርሸር ቦቅቧቃ ፈሪዎች፣ አጎብዳጆች፣ የጀግንነት ተፈጥሯዊ ባህሪያቸውን እና ስብዕናቸውን በማኮላሸት ባርነትን እንዲቀበሉ በማስፈራራት፣ ለነጻነት የሚያደርጉትን ጥረት በውሸት ተስፋ እና አስመሳይነት እንዲተኩ በማድረግ በውርደት እና በፍርሀት ተሸብበው እንዲኖሩ በማድረግ፣ የታዛዥነት ምግባራቸውን እንዲያዳብሩ፣ የብልግና ጀግንነትን ስራ እንዲለምዱ በማድረግ እና ህሊናቸውን ለውሸት ሲሉ እውነትን እንዲሸጡ ያደርጋሉ፡፡

እ.ኤ.አ በ1776 የአሜሪካ ሕዝቦች የእራሳቸውን አጋጣሚ በመወሰን ምንም ዓይነት ውክልና የሌለው ንጉስ ግብር ክፈሉ በማለት በላያቸው ላይ በጫነው አምባገነናዊ አገዛዝ ላይ በማመጽ ያለፈቃዳቸው በላያቸው ላይ የተጫኑትን ፍትሀዊ ያልሆኑ ህጎች ይሁንታ ባለመስጠት ትግላቸውን ቀጥለዋል፡፡ እኛ በአሁኑ ጊዜ እንዳደረግነው ሁሉ እነርሱም እንደዚሁ እንዲህ በማለት አወጁ፡

“አንድ መንግስት ከተቋቋመበት ህጋዊ ማዕቀፍ አንጻር እና ህዝቡ በደስታ መኖር እንዳይችል እና ሊገመቱ እና ሊነጣጠሉ የማይችሉትን መብቶች ወደ ጎን በመጣል የህዝቦችን የመኖር ህልውና፣ ነጻነት እና ንብረት መጠበቅ ካቆመ ሰይጣናዊ ገዥዎች ለጭቆናዎች ማስፈጻሚያነት በእጃቸው ያለ መሳሪያ ይሆናቸዋል“ ብለው ነበር፡፡

ስለነጻነት፣ ዴሞክራሲ እና የሰብአዊ መብት ጥበቃ በአዲሱ የኢትዮጵያ ሚሊኒየም በሰይጣናዊ ገዥዎች ላይ በአንድነት በመቆም የምንታገልባቸው እነዚህ ናቸው! አሁኑኑ ተግባራዊ ማድረግ አለብን!

በዓለም ላይ ያሉ ኢትዮጵያውያን ሁሉ በአሁኑ ጊዜ እራሳቸውን ከዛሬ፣ ነገ እና ከሚሊኒየሙ የሚወስን ምርጫ መምረጥ አለባቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ የነጻነትን ዘሮች መዝራት አለብን፣ እናም የወደፊቱ ትውልድ ከዚህ አዝመራ ማጨድ ይችላል፡፡

ስለሆነም በኢትዮጵያ ከዚህ በታች በቀረቡት መሰረት ነጻነትን፣ ዴሞክራሲን እና የሰብአዊ መብት ጥበቃን በሚጥሱ ጨቋኞች ላይ አሁኑኑ መነሳት አለብን፡

o    የኢትዮጵን ህዝብ ለመነጣጠል እና ሉዓላዊ ግዛቷን ለመድፈር ከሚጥሩ የውጭ ጠላቶች ጋር ህብረት በመፍጠር ሌት ቀን ደባ መፈጸም፣

o    የሀገሪቱን የፍትሀብሄር እና የወንጀለኛ መቅጫ ሕጎችን አጎብዳጅ እንዲሆኑ እና የህዝቡን መሰረታዊ መብቶች እየሸራረፉ የሕግ የበላይነትን በመንፈግ የፍትህ ስርዓቱን ሽባ ማድረግ፣

o    ህዝቡ በነጻነት ሀሳቡን እንዳይገልጽ፣ በሰላማዊ መንገድ መሰብሰብ እንዳይችል፣ ቅሬታን ለመንግስት ማቅረብ እንዳይችል እና ፕሬሱ በነጻነት መዘገብ እንዳይችል መከልከል፣

o    መሰረታዊ የሆኑ ሰብአዊ መብቶችን መደፍጠጥ እና ዓይን ባወጣ መልኩ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶችን እና ስምምነቶችን መጣስ፡፡ አስቸጋሪ የሆነውን የከፋፍለህ ግዛ ዘዴ መጠቀም እና ታሪካዊ የሆኑ ቅሬታዎችን እየፈለፈሉ ቆፍሮ በማውጣት በህዝቦች መካከል ጥላቻ እና አለመተማመን እንዲነግስ ማድረግ፡፡

o የኃይል እርምጃዎች እንዲፈጸሙ በማድረግ ህዝቦችን ማስፈራራት፣ በህዝቦች መካከል ሽብር መንዛት፣ ሰላማዊ ዜጎችን ከህግ አግባብ ውጭ በዘፈቀደ እየያዙ በቁጥጥር ስር ማዋል እና ማሰር፣ በዜጎች ላይ ሊነገር ከሚችል በላይ የሆነ የእስር ቤት ስቃይ መፈጸም፣ በሀገሪቱ ውስጥ የወታደር ጉንዳን በማዝመት ህዝቦችን ማስፈራራት እና የጎዳና ላይ ፍትህ እንዲኖር ማድረግ፣

o    በዴሞክራሲያዊ ምርጫ በብዙሀኑ ህዝብ ድምጽ እየተሸነፈ እና ውድቅ እየተደረገ ስልጣንን አልለቅም በማለት የሙጥኝ ብሎ ቢሮውን አልለቅም ማለት፣

o    በሕዝብ የተመረጡትን የህዝብ ተወካዮች ሕገወጥ በሆነ መልኩ በቁጥጥር ስር በማዋል ማሰር እና ሰላማዊ የፖለቲካ ተቃዋሚዎችን በሀሰት እና የፈጠራ ክስ እና ወንጀል በመፈብረክ ኢፍትሀዊ በሆነ መልኩ ማሰር፣

o    ፍርዱ በወገንተኝነት ለገዥው ፓርቲ አባላት እንዲሆን የፍትህ ስርዓቱን በማስገደድ በፍትህ ስርዓቱ ላይ መሰናክል ጋሬጣ መፍጠር፣

o    በጎረቤት ሀገሮች ጉዳይ ላይ ጣልቃ መግባት እና በህዝቦቻቸው ላይ ጦርነት በመክፈት ዘላለማዊ የሆነ ጥላቻ ማትረፍ፣

o    ታላላቅ ሀገሮች በኢትዮጵያ ውስጥ የዴሞክራሲያዊ ተቋማት እንዲገነቡ እና ሰብአዊ መብት እንዲስፋፋ እና የህግ የበላይነት እንዲከበር የሚያደርጉትን እርዳታ ለመቀበል ፈቃደኛ ያለመሆን፣ እነዚህ ሕጎች ተግባራዊ እንዳይሆኑ ለማደናቀፍ ለውጭ ባለሙያዎች ከሀገሪቱ ግምጃ ቤት ከፍተኛ የሆነ ወጭ በመመደብ አማካሪዎችን መቅጠር፣ እና

o     በጥንታዊ ዘመን ከነበረው ኋላቀር የአውሬነት አስተዳደር ጋር በሚመሳሰል መልኩ በሰው ልጆች ላይ ወንጀሎችን የመፈጸም ተግባራትን ማከናወን ናቸው፡፡

እነዚህን ጭቆናዎች ለማራመድ በእያንዳንዱ እርምጃ ላይ ህዝቡ ከፍተኛ የሆነ ጨዋነትን በተላበሰ መልኩ ቅሬታዎቹን ያቀርባል፡፡ ዓለም አቀፉ ሕግ ተግራዊ እንዲደረግ እና የዓለም ታላቋ ሀገር ማስፈጸም እንድትችል ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች የተማጽዕኖ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

ህዝቡ ለፍትህ መስፈን በሚያቀርበው አቤቱታ ላይ የመቀለድ፣ በሚቀርቡ ቅሬታዎች ላይ የማሾፍ እና ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለሚሰጠው ምክር የዝሆን ጆሮ ይስጠኝ ማለት እንደ አንድ ዘዴ አድርጎ ቆጥሮታል፡፡

ስለሆነም እኛ ስማችን ከዚህ በታች የተዘረዘረው ሰዎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ከአምላክ በተሰጣቸው ጸጋ በነጻነት፣ በዴሞክራሲ እና ሰብአዊ መብቶቻቸው ተጠብቀው የመኖር መብት እንዳላቸው እና የእራሳቸውን መንግስት በእራሳቸው ፈቃዳ የመመስረት መብት እንዳላቸው እንዲሁም እኛም ለዚህ ዓላማ ስኬታማነት ጠንክረን መስራት አለብን በማለት የሚከተሉት ነገሮች እንዲከናወኑ ተማጽዕኗችንን እናቀርባለን፡

o    የፖለቲካ የህሊና እስረኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በአስቸኳይ እንዲፈቱ፣

o    የህዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብት በአስቸኳይ ለህዝቡ እንዲመለስ፣

o    የዴሞክራሲያዊ ስርዓቱን ማሻሻል እና ተጠያቂነት እንዲኖር ማድረግ፣

o    ፍትሀዊ እና ትክክለኛ የዳኝነት ስራ እንዲሰራ የህግ ተቋማትን አቅም ማጠናከር፣

o    የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖችን እና ድርጅቶችን ማጠናከር እና ለሰብአዊ መብት ማስፋፊያ ፕሮግራም እገዛ ማድረግ፣

o    ሰብአዊ መብቶችን የሚደፈጥጡ ሰዎችን በቁጥጥር ስር በማዋል 193 ሰላማዊ ወንዶችን፣ ሴቶችን እና ህጻናትን የገደሉትን ቅጥር ነብሰ ገዳዮች እና ሌሎችን 763 ሰላማዊ ዜጎችን ቁስለኛ ያደረጉትን ወንጀለኞች ለፍትህ አካል ማቅረብ ፣

o    የፍትህ አካሉን ነጻነት መጨመር፣

o     ቋሚ የሆነ የሰብአዊ መብት ጥበቃ የክትትል እና ዘገባ አቀራረብ ሂደቶችን መመስረት፣

o    የሴቶችን መብቶች ማክበር እና የተረጋጋ ማህበረሰብን ለመመስረት መሰረት የሆኑትን ቤተሰቦች ማጠናከር፣

o    ወጣቶች የወደፊት መሪዎች እንዲሆኑ ማበረታታት፣

o    ሁሉንም የፕሬስ ቅድመ ምርመራ ድርጊቶች ማስወገድ እና የተሟላ የፕሬስ ነጻነት እንዲኖር የግል የመገናኛ ብዙሀንን ማጠናከር፣

o    ከማጭበርበር የጸዳ የምርጫ ሂደት መኖሩን ለማረጋገጥ የምርጫ ሂደቱን ማሻሻል እና የብዙሀን ፓርቲ ፖለቲካ ውድድርን ማጠናከር፣

o    ዓለም አቀፍ ሰላምን ለማረጋገጥ የዩኤስ የጸጥታ ኃይሎችን እገዛ መወሰን እናም ወደ ሲቨሉ ህዝብ ላይ እንዳይደረግ ማድረግ፣ እና

o    በሰው ልጆች ላይ ኢሰብአዊ የሆኑ ወንጀሎችን የፈጸሙት ጥፋተኞች እና ወንጀለኞች ሁሉ ለፍትህ አካል እንዲቀርቡ ያልተቋረጠ ጥረት ማድረግ የሚሉት ናቸው፡፡

ይህንን ድንጋጌ በመደገፍ በአምላክ ኃይል መከታ ጽኑ ተራዳይነት ሁላችንም በአንድ ላይ ሆነን የእያንዳንዱን እና የመላውን የኢትዮጵያን ህዝብ መብት ለመጠበቅ እና ለማስፋፋት ያለምንም ማመንታት ነጻነትን፣ ዴሞክራሲን እና የሰብአዊ መብት ጥበቃን በአዲሱ ሚሊኒየም ተግባራዊ ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

ይህንን ድንጋጌ የደገፉ እና በፊርማቸው ያረጋገጡ ኢትዮጵያውን ስም ዘርዝር ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል፡

1ኛ) ዓለማየሁ ገብረ ማርያም

2ኛ) አብረሀ በላይ

3ኛ) አበበ ገላው

4ኛ) ክፍሌ ሙላት

5ኛ) ክንፉ አሰፋ

6ኛ ስለሺ ጥላሁን

7ኛ) ማሞ ሙጨ

8ኛ) ለምለም ጸጋው

9ኛ) ወንድሙ መኮንን

10ኛ) ሸክስፒር ፈይሳ

11ኛ) አያልነሽ ጫንያለው

12ኛ) አማረ ግዛው

13ኛ) ኤልሳቤጥ ነጋ

14ኛ) ሰብለ ታደሰ

15ኛ) ዶሮዚ አማረ

16ኛ) ሉሊት መስፍን

17ኛ) ዓለማየሁ ዘመድኩን

18ኛ) አዜብ ግርማ

19ኛ) ሜሮን አሀዱ

20ኛ) አስቴር ደመቀ-ሀንሰን

21ኛ) ዙፋን ይመር

22ኛ) አዚዝ መሀመድ

23ኛ) ኤሊያስ ወንድሙ

24ኛ) አበበ ፈቃደ

25ኛ) ዘነበወርቅ ተክሉ

26ኛ)  ገነት ግርማ

27ኛ) ዳንኤል አሰፋ

28ኛ) ጥሩወርቅ ወንድሙ

29ኛ) አበበ ቦጋለ

30ኛ) ማሪያ ሰ.ሉጎ

31ኛ) መዓዛ ገብረ ዋህድ

32ኛ) ጆሴፍ ኤም ሲፉኒ

33ኛ እህተ ገብሬ

34ኛ) ከይፍ ስሺፈር

35ኛ) በቀለች አሰፋ

36ኛ) ንዋይ መንግስቱ

37ኛ) አባይነሽ አሰፋ

38ኛ) ሙሉነህ ዮሀንስ

39ኛ) አንዳርጋቸው ጽጌ

40ኛ) ናታን ይመር

41ኛ) በላይነሽ ኃይማኖት

42ኛ) ብርሀነ መዋ

43ኛ) ሙሉ አየለ

44ኛ) ዝቄ አየለ

45ኛ) ፈቃደ ሸዋቀና

46ኛ) አክሎግ ልመንህ

47ኛ) ፊፊ ደርሶ

48ኛ) የሱፍ ኡመር

49ኛ) መዓዛ እጅጉ

50ኛ) ቴዲዎስ በየነ

51ኛ) አዚዝ መሀመድ

52ኛ) ግደይ አሰፋ

53ኛ) በላይነሽ ሰለሞን

54ኛ) ሐረገወይን ምስማኩ

55ኛ) ኃይሉ አውላቸው

56ኛ) ዘመድ ይተርፍ

57ኛ) ብርሀኑ ድንቁ

58ኛ) ጽጌ ሞገስ

59ኛ) መሰለ አለም

60ኛ) አዳም ዘሪሁን

61ኛ) ግርማ ዳውድ

62ኛ) ይታገሱ ወልደሀና

63ኛ) ሶሎሞን ከበደ

64ኛ እመቤት ሶሎሞን

65ኛ) አብይ አሰፋ

66ኛ) ጁኒየር ይግዛው

67ኛ) ተስፋዬ ስለሺ

68ኛ) ሳሙኤል በልሁ

69ኛ) ሰሙ ዝናቡ

70ኛ) ግርማ ካሳ

71ኛ) መቅደስ ቢ. ካሳ

72ኛ) ታሪኩ ባድማ

73ኛ) ቢንያም ይነሱ

74ኛ) ተስፋዬ ለታ ናቸው፡፡

———–

እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/2007

እ.ኤ.አ ሀምሌ 2/2006 በዩናይትድ ስቴትስ መድረክ በኢትዮጵያ አሜሪካ ምክር ቤት በላክስ ሂልተን በሎስ አንጀለስ ካሊፎርኒያ “በትልቁ እንንቃ” በሚል ርዕስ ንግግር አደረግሁ፡፡ ይህም ንግግር እ.ኤአ. ሀምሌ 4/2006 ታተመ፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 2011 ድንጋጌው በእኔ ድረ ገጽ በሁፊንግተን እንደገና ተጫነ፡፡

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!  

ሰኔ 29 ቀን 2008 ዓ.ም

Filed in: Amharic