>

ወሬ ሲነግሩህ ሃሳብ ጨምርበት [በእውቀቱ ስዩም]

ምኒልክ ጥቁረቱን ክዶ ነበር የሚል ቀደዳ በፌስቡክ ሲዞር ኣየሁ ልበል?

ትልልቅ ቅጥፈቶች ጀርባ ኣንድ ትንሽ መነሻ ይኖራል፡፡

መነሻውን እንመርምር እስቲ፡፡

Minilik and Tayituያድዋ ድል ማግስት የምኒልክ ዝና የጠራቸው የውጭ ኣገር ሰዎች ኢትዮጵያን መጎብኘት ጀምረው ነበር፡፡ ከኒህ እንግዶች ኣንዱ የሄቲው ታጋይ ጋዜጠኛ ቤኒቶ ሲልቪያን ነው፡፡

ሲልቪያንና ምኒልክ ያደረጉትን ጭውውት ስኪነር የተባለ ኣሜሪካዊ ዘግቦታል፡፡

በጭውውታቸው መሀል ምኒልክ ለሄቲው ሰውየi am not a Negro I am a Caucasian ማለቱን ስኪነር ዘግቧል፡፡

ምኒልክ ኔግሮ ኣይደለሁም ብለው ከሆነ ደግ ኣደረጉ ከማለት ውጭ የምለው የለኝም፡፡ ምኒልክ ጥቁር እንጂ ኔግሮ ኣይደለም።ኔግሮ የውርደት ስም ሲሆን ጥቁር የክብር ስም ነው፡፡

ኮኬሽያን የሚለው ቃል ግን ያስተርጓሚ ስተት መሆን ኣለበት፡፡በምኒልክ ዘመን ሰዎች ዘርን ለመግለጽ የሚጠቀሙባቸው ቃላት ከብሉይና ሃዲስ የተቀዱ ናቸው፡፡የሴም ዘር የካም ዘር የያፌት ዘር ወዘተ ይሰኛሉ፡፡ ኮኬሽያን የሚለው ቃል በወዘተ ውስጥ ኣይካተትም፡፡ኮኬሽያን በጊዜው በሊቃውንቱም ሆነ በመኳንንቱ ኣንደበት የሚዘወተር ቃል ኣልነበረም፡፡

ምኒልክ የሚገዛቸው ህዝቦች ጥቁር እንደሆኑ ያምን ነበር፡፡

እንደ ኤውሮፓ ኣቆጣጠር በ1878 ለንጉስ ሊዎፖልድ በጻፈው ደብዳቤ እንዲህ ይላል፡፡

“የኦሮሞ (ቃሉ ተተክቷል) የኣማራ የሱማል መልኩ ኣንድ ነው፡፡ ሁሉም ጥቁር ነው፡፡”
ምንጭ Acta Ethiopia vol 3 Edited by Sven Rubenson page302

ምኒልክ ጥቁረቱን ከመቀበል ኣልፎ ኣፍሪካዊ ጌቶች ጋር ጥቁረትን መሰረት ያደረገ ትብብር ጠይቆ ያውቃል፡፡ለምሳሌ ከሱዳኑ የማህዲስት መሪ ጋራ ሲደራደር የተናገረውን ታሪክ ጸሃፊዎች እንዲህ መዝግበውታል፡፡

Between us there has been no war. Now we have worse enemy who will make slaves of you and me.I am black :and you are black. Unite with me”
ትርጉም፤
”ባንተናኔ መሀል ጠብ ኖሮ ኣያውቅም፡፡ሁለታችንን በባርነት ሊገዛን የተሰናዳ የከፋ ጠላት ኣለብን፡፡ እኔ ጥቁር ነኝ፡፡ ኣንተም ጥቁር ነህ፡፡ እንተባበር“

ልብ በሉ ይህንን የሚለው ምኒልክ ነው፡፡
በካሊፋውና በምኒልክ መካከል የተደረገው ይህ ታሪካዊ ልውውጥ ተመዝግቦ የተገኘው ከጥልያኑ መኮንን ከባራቴሪ ማስታወሻ ውስጥ ሲሆን በእንግሊዝኛ ተርጉማ መጽሃፏ ውስጥ የዶለችውChris Prouty ናት፡፡Empress Taitu and Menilk በተባለው መጽሀፏ ገጽ 119 ላይ ታገኙታላችሁ፡፡

በተረፈ “ወሬ ሲነግሩህ ሀሳብ ጨምርበት” የሚለውን ያባቶቻችንን ምክር በመጋበዝ ልሰናበት፡

Filed in: Amharic