>

ገራፊዬን አየኹት [አቤል ዋቤላ]

ቀልድ ያለፈበት ጨዋታ ሆኗል፡፡ አሁን ዘውጉ ተቀይሯል፡፡ ፍጥጥ ግጥጥ ያለ ዕውናዊ ድርሰትን መመልከት ይዘናል፡፡አይን አያየው የለም፡፡ አሁን ደግሞ ገራፊዬን አሳየኝ፡፡ በኮምፒዩተር የኤሌክትሪክ ገመድ ጀርባዬ እስኪቀደድ የገረፈኝን፣ በመጥረጊያ እንጨት ውስጥ እግሬን ያነደደኝን፣ እጄ በካቴና ታስሮ ወለል ላይ ያንከባለለኝን፣ ጨለማ ቤት ውስጥ አስገብቶ ከየት እንደመጣ በማላውቀው ጅራፍ አሳሬን ያበላኝን፣ እናቴን ከመቃብር ጠርቼ “አንቺ እናቴ ለምን ጥሩ ሁን ብለሽ አሳደግሽኝ? ብዙ ክፉ ሰዎች እንዳሉ ለምን አልመከርሽኝም?” ብዬ እንድወቅሳት ያደረገኝን፣ ወንድ፣ የወንዶች ቁና በካቴና የታሰረን ሰው በዕኩለ ሌሊት ጠርቶ አፉ ውስጥ ጨርቅ ወትፎ የሚደበድብ በአይኔ በብረቱ አየኹት፡፡

ዮናታን ተስፋዬ ለጊዜያዊ ቀነ ቀጠሮ አራዳ ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ሰምቼ ነው ወደዚያ የሄድኩት፡፡ ይህችን የተለመደች ሰርከስ ሁሉም የፖለቲካ እስረኛ ይወዛወዛታል፡፡በማዕከላዊ ይጀመራል ከዚያ አራዳ ፍርድ ቤት ይቀጥላል፡፡ የማዕከላዊ ደብዳቢዎች በጨለማ የሚያሰቃዩትን እስረኛ በቀን ሰው መስለው (ወገኞች ናቸው አንዳንዴማ ዩኒፎርምም ያጠልቃሉ) ፍርድ ቤት ያቀርቡታል፡፡ ውሸት ውሸቱን ይቀባጥራሉ፡፡ “ግበረ አበሮቹን በኢንተርፖል እያሳደድን ነው፣ ክቡር ዳኛ በዋስ ከተለለቀቁ ልማታችንን ያደናቅፋሉ፡፡ ወህኒ ሰብረው እስረኛ ያስፈታሉ” የመሳሰሉትን በጠራራ ጸሐይ ይቀባጥራሉ፡፡ እየቀለድኩኝ አይደልም የምሬን ነው እንዲህ አይነት በሬ ወለደ ምክንያት በጆሮዬ ሰምቻለው፡፡ ዳኛውም አብሮ ይተውናል፡፡ የፈለጉትን ቀን ያህል ያራዝማል፡፡

ገራፊዬንም ያየሁት እኔንና ጓደኞቼን እንደነዳው እንዲሁ ተረኛውን ገፈት ቀማሽ ሲያመጣ ነው፡፡ ላንዳፍታ አይኖቻችን ተጋጩ፡፡ አስተውሎኝ ይሁን አይሁን አላውቅም በፍርድ ቤቱ ቢሮዎች መሐል ገብቶ ተሰወረ፡፡ እኔ ግን በእርግጠኝነት ለይቸዋለው፡፡ ውስጤ ዳግም ተቆጣ፡፡ እስር ቤት ብቻዬን ደጋግሜ ባሰብኩት ቁጥር እንደአዲስ የልቤ ቁስል ያመረቅዝ ነበር፡፡ ቂም ስቋጥር እና ስፈታ ከአመት በላይ ቆይቻለው፡፡ ቂም ይዣለው በውድም ሆነ በግድ ኢትዮጵያዊ በሆነ ሁሉ ላይ ቂም ይዣለው፡፡ እንዴት ሰው በሀገሩ ይህንን ጉድ ተሸክሞ ይኖራል? እንዴት እንደዚህ አይነት ተቋም በመዲናይቱ እምብርት ላይ አስቀምጦ ዝም ይላል? ይህን ባርቤሪዝም ጌጡ ካደረገ ማኀበረሰብ ጋር በቀላሉ የማይበርድ ግጭት ውስጥ ነኝ፡፡ ስለዚህ በመንገድ ስታገኙኝ ፊቴ ጥቁር ብሎ ብታገኙኝ “ምን ሆነህ ነው?” አትበሉኝ፡፡ ቂም ይዤ ነው፡፡ ተራ ማኩረፍ አድርጋችኹ አትውሰዱት ስር የሰደደ ከነፍስ የሚቀዳ ጸብ ነው፡፡

torturedevices. 2በግርፋት የተሰነጠቀውን ጀርባዬ በቅባት ላሹኝ ዕድሜ ለእነ ኤባ ቁስሉ እዛው ማዕከላዊ ነው የዳነው፡፡ የልቤ ስንጥቅ ግን አልዳነም ፡፡ ያ ዘላለም ክብረት “ምድር ብዙ ክፋት የሚፈጸምባት ቦታ ናት በእኛ ላይ የደረሰውም አዲስ ነገር አይደለም” እያለ ብዙ እንዳላዝን ቢመክረኝም ያቄመው ልቤን ሊያሸንፈው አልቻለም ነበር፡፡ የተገኘሁበት፣ ያሳደገኝ ማኀበረሰብ ላይ እንዳቄምኩኝ ከእስር ወጣኹኝ፡፡ ባለፉት አራት ወራት በአንጻራዊ ነጻነት ማሳለፌ ግን ትንሽ እንዳዘናጋኝ የገባኝ ግን በቀደም ገራፊዬን ያየኹት ቀን ነው፡፡ወይ ጊዜ ስንቱን ያስረሳል አልኩኝ፡፡ አሁን ከእስር መፈታት ብርቅ የሆነበት ጊዜ አልፏል፡፡ ቁስሌ ዳግም አመርቅዟል፡፡ ገራፊዬን እና አለቆቹን የያዘው ህንጻ ካልፈረሰ አልያም ሙዚየም ካልሆነ ዕርቅ የማይታሰብ ነው፡፡ ድሮ እስር ቤት ሳለኹኝ በእስረኛ ማጓጓዣ መኪና ወደ ፍርድ ቤት ስንመላለስ በመስኮት ስመለከተው የዕለት ጉርሱን ለማብሰል የሚራኮተው አዳሜ አሁንም ውስጡ ሁኜ ስመለከተው ከሆዱ በቀር የኔ ቁስል ግድ የሰጠው አይመስልም፡፡ ስለዚህ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ ብዬ ይቅር እላለው? ውስጤ የበለጠ ስለሻከረ እምቢኝ ብያለው፡፡ ይህ የአንዲት ነጠላ ነፍስ መብት ነው፡፡ በገዛ ነፍሴ ጥላቻን ማርገዝ መብቴ ነው፡፡ ከፈለጋችኹ ለዐቃቤ ሕግ ንገሩትና በፊት ‘የማኀበረሰቡን ጤና እና ደህንነት ለአደጋ በማጋለጥ’ እንደ ከሰሰኝ አሁን ደግም ‘በማኀበረሰቡ ላይ ስር የሰደደ ጥላቻና ቂም በመቋጠር’ ይክሰሰኝ፡፡

እነ ኤቢሳ አካላዊ ቁስሌን እንደሳምራዊው ሰው በቅባት እንዳሹልኝ አሁን ደግሞ ዘመዶቻቸው የተሰበረ መንፈሴን የቆሰለ እኔነቴን ሊጥገኑ ተነስተዋል፡፡ የእነኤቢሳ፣ የእነቶፊቅ እና የእነ ቶላ ዘመዶች እኔን ከህመሜ ሊያድኑኝ ደማቸውን እየከፈሉ መሆናቸውን ድፍን ፌስቡክ እየተመለከተው ነው፡፡ አዲስ አበቤ “አገር ሊያፈርሱ ነው ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አትኖርም” ቅብርጥሴ ቅብርጥሴ ቢልም እኔ ግን ከሚፈርሰው አገር ከፒያሳ ከፍ ብሎ ያለው ማዕከላዊ ጎልቶ ይታየኛል፡፡ ስለዚህ በመሬት ላይ ዋጋ እየከፈሉ ያሉትን ወገኖቼን ይቅር ብያለው፡፡ ከነዚህ በቀር ሌላው ማኀበረሰብ “እርሱ” አይደለም “እኔ” ራሱ ይቅርታን አያገኛትም፡፡ አራዳ ፍርድ ቤት መሄዴ አይቀርም፡፡ በማዕከላዊ በርም አልፋለው፡፡ በየጊዜው እየሄደኩኝ ከገራፊዎቼ አንዱን እያየው ጥላቻዬን እያደስኩኝ እመጣለው፡፡ ቁስሉ ይበልጥ እንዲቆጠቁጠኝ ወደገራፊዬ ተጠግቼ አይኖቹን በአይኖቼ አድናለው፡፡ አይገርምም ግን ………….…ገራፊዬ እስካሁን እዚያው ነው፡፡

Filed in: Amharic