>

መላቀቅ የለም [ከአንተነህ መርዕድ]

Dont ever give up Anteneh Meridበዚች ቅፅበት፣ አንድ ቃል ተናግራቸሁ በማትጨርሱባት ደቂቃ፤ በወያኔ አልሞ ተኳሾች፤ በመላዋ ኦሮምያ፣ ጎንደርና ኦጋዴን ንፁሃን እየተገደሉ ነው። በዚችው ደቂቃ አፄ ዮሃንስና አባቶቻችን የወደቁባት መሬት በወያኔ ለሱዳን ተሰጥታ፤ አገራችንን አናስነካም ያሉ ጀግኖች ከወያኔና ከሱዳን በሚተኮስ ጣምራ ጥይት እየወደቁ ነው። በዚችው ደቂቃ ከአስራ አምስት ሚሊዮን የበለጡ ኢትዮጵያውያን አስፈሪውን ርሃብ ያለማንም እርዳታ ተጋፍጠውት ሮጠው ያልጠገቡ ልጆቻቸው እቅፋቸው ላይ ለዘለዓለሙ እያሸለቡ ነው። ከማምረቻ ፋብሪካዎች በላይ በበዙ ግልፅና ድብቅ እስርቤት ሺዎች እየማቀቁ ነው። ይህንን ሁሉ ግፍ የሚሠራው ዘረኛ ወያኔ እንደድሮው አፍኖ የሚገዛበት አቅም አጥቶ የመጨረሻ ኃይሉን እየተጠቀመ ሲሆን ህዝቡም ግፉ ሞልቶ በመፍሰሱ ከአሁን በኋላ እንደድሮው ላለመገዛት ቆርጦ መውጣቱን ከአሁኑ ድርጊቱ የበለጠ ማረጋገጫ አያስፈልግም።
ይህንን ህዝባዊ ትግል ወደ ዘላቂ ድል ለመቀየር አስተውሎ መራመድን ይጠይቃል። ተደጋጋሚ ድሎቹ የተነጠቁበት ህዝብ ተስፋ ባለመቁረጥ እንደገና ሲነሳ ዳር ቆሞ የሚታዘብና የሚያሽሟጥጥ አቅም ያለው ኢትዮጵያዊ የተረገመ ነው። በተለይም በሌለ አቅሙ ያስተማረህ/ሽ ምን ዓይነት እንቅልፍ አሁን ይወስድሃል/ሻል?? ትግሉ ብዙ ፍልስፍናና ምርምር የሚጠይቅ አይደለም። ዋና ዋና መሰረታዊ ጥያቄዎች እንዲፈቱ ማለም ብቻ ነው። የተነሳው ህዝባዊ አመፅ መልኩን እንዲይዝ አጀንዳውን ማስፋትና አገራዊ ማድረግ ወደ ዘላቂው መፍትሄ ያደርሳል። በመላ ኦሮምያና በጎንደር የተነሳው አመፅና በግፍ የሚፈሰው ደም ለተወሰነ ቦታ ሳይሆን ለአገር ነውና መስዋዕታቸውን ከፍተኛ ዋጋ ልንሰጠው ይገባል። የነሱን ትግል መላ ኢትዮጵያዊ እንዲቀላቀል የትግሉ ዓላማዎች አገራዊነትና ጥልቅ መሆን ስለሚገባቸው በነዚህ ዓላማዎች ዙርያ እንታገል። ህዝቡም እነዚህን ዓላማዎች እንዲያሳካ አቅጣጫ ይውጣለት።
• የዜጎች ግድያና እስራት በአስቸኳይ ይቁም፤ ፈፃሚዎችም ለፍርድ ይቅረቡ!
• ሁሉም የፖለቲካና የህሊና እስረኞች ይፈቱ!
• የኢትዮጵያ ሉዐላዊነትና ድንበሯ ይጠበቅ!
• መሬት የዜጎች እንጂ የአምባገነኖች የግል ንብረት አይደለም! መሬት ላራሹ ! የከተማ መሬት ባለቤትነት ይከበር!
• የመፃፍ፣ የመደራጀት፣ የመሰለፍና ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ያለገደብ ይከበር!
• የመከላከያ፣ የደህንነትና የኤኮኖሚ ተቋማት ከጠባቡ ህወሃት እጅ ይውጡ!
• ሁሉንም ያካተተ የሽግግር መንግስት ይቋቋም!
• አገሪቱ ላይ እስካሁን የተፈጠሩትን ችግሮች መርምሮ የወደፊቷን፣ የሁሉም የሆነች ኢትዮጵያን ለመግንባት የሚያስችል ብሄራዊ እርቅ ይጀመር!
• በርሃብ የተጠቁ ወገኖቻችንን በአስቸኳይ ለመርዳት የሚያግዝ ገለልተኛ አካል ይፈጠርና አፋጣኝ ህይወት አድን ሥራ ይቀናበር!
• አገር ውስጥ ያሉ ሆኑ ውጭ የሚገኙ ሁሉም የፖለቲካ ድርጅቶችና ንቅናቄዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በህዝባቸው ጉዳይ ላይ በአስቸኳይ ተገናኝተው ለመፍትሄው በጋራ መሥራት ይጀምሩ!
እነዚህ ከላይ የተቀመጡ ዓላማዎች ሁሉን የሚያጋሩ ይመስለኛል። የሚጨመሩም ካሉ ጨምሮ ህዝቡ በትልልቅ አላማዎች ዙርያ እንዲታገል የመምራትና የማስጨበጥ ሃላፊነት ያለባችሁ ወገኖች በዚህ ዙርያ ድከሙ። በየቦታው የተጀመሩ ትግሎችና ድሎች በሁሉም ይዳረሱ።
ኢትዮጵያን እግዜብሄር ይታደጋት!
ለልጆቿም ጥንካሬና አንድነትን ይስጥ!

Filed in: Amharic