>
5:13 pm - Monday April 20, 1316

የማለዳ ወግ...ረሃብ አጠቃን ! ረሃብን ሽሽት ሞት ተደፍሯል ![ነብዩ ሲራክ]

* የረሃቡ መረጃ ከወራት በፊት ..
* ረሃቡን ሸሽተው ሳውዲ ከገቡት እማኞች ጋር …
* ቀናኢው የሳውዲ ነዋሪ ለተጎዳው ወገኑ …
*የረሃብ ፖለቲካውን እንተወው … ለወገኖቻችን እንድረስላቸው

የረሃቡ መረጃ ከወራት በፊት …
በወርሃ ነሀሴ 2007 የመጀመሪያ ሳምንት በአፋር ረሀብ ስለመግባቱ በጀርመን ራዲዮ ከመስማታችን አስቀድሞ ኢትዮጵያን ከሚያስተዳድራት የአህአዴግ መንግስት ለምን ድርቅን ይሸፋፍናል ? ስንል ጠየቅን … የአፋር አርብቶ አደር ብቸኛ አንጡረ ሀብት የሆኑት ከብቶቹ አደጋ ላይ በድርቁ ክፉኛ ስለመመታታቸው በተጨባጭ ተንቀሳቃሽ የምስል ቀርቦ የወዳደቁትን ከብቶች አይተን አዝነናል … የአካባቢው ነዋሪ “ድርቅ መታን ” ሲሉ ” ለድርቁ የአፋር መስተዳደር ባለሥልጣናት ተገቢና ፈጣን ምላሽ አልሰጡም !” በማለት ወቀሳቸውን ለጀርመን ራዲዮ መግለጻቸውን ወዳጀና የሙያ አጋሬ ጋዜጠኛ ማንተጋፍቶት ስለሽ እጥር ምጥን ባለው የጀርመን ራዲዮ ዘገባው አስደምጦናል ፣ የዛሬ ሶስት ወር ነሀሴ … ! በዘገባው የቀረቡት ነዋሪዎች “ተወካዮች በአፋጣኝ መድረስ መርዳቱ ቀርቶ ድርቁን ለመደባበቅ ይሞክራሉ !” ሲሉ አማረዋል ያለው የጀርመን ድምጽ ራዲዮ የወቅቱ ዘገባ የመንግስት የፌዴራልና የክልል መንግሥት ግን ችግሩን ለመቋቋም በመስራት ላይ እንደሚገኙ መግለጻቸውን በጋዜጠኛ ማንተጋፍቶት ዘገባ ተጠቅሶም ነበር …

Nebiyu Sirak 13112015የሆነው አሞን አሳስቦን ሀገርና ህዝብን የሚያስተዳድረው የኢህአዴግ መንግስት አስከፊ አደጋ ሲደርስ የሚያጠግብ መልስ ነፈገን …. ረሀብን ለፖለቲካ ሲጠቀምበት ጃንሆይን ” ረሀብን ደብቆ ኬክ ቆረሰ !” ብሎ ያወገዘ ፣ ደርግን በተመሳሳይ መንገድ ” ረሃብን ደበቀ ” ሲል ሌላ የፖለቲካ መጠቀሚያ አድርጎ ተቃውሞውን ያፋፋመው የኢህአዴግ ፖርቲ መንግስት ሆኖ ሀገር መምራት ሲጀምር ድርቁን አቃለለው ፣ ደባበቀው ! ረሀብ ቸነፈሩ ከቁጥጥር ሳይወጣ በይፋ እርዳታ መጠየቅ ማስተባበር ሲገባ የፖለቲካ ድርጅቶች አመታዊ የልደትና የድል በአላትን ሲከበር በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ የማባከኑን ፍትሃዊነት ጠይቀን አሁንም ሆድ የሚያሞላ የማያጠግብ የእውነት መልስ ታጥቶ ለወራት ስንንከላዎስ ይህው ከከፋው አደጋ ደርሰናል !

የአደጋውን አሳሳቢነት ከተራቡት መረጃ ደርሶን አልሰማ ብለን ብንከርምም የውጭ መገናኛ ብዙሃን ረሃቡ ከጋማ ከብቶች አልፎ ክቡሩን ሰው መቅጠፍ መጀመሩን ተጎጅዎችን እያቀረቡ እየነገሩን ነው ። ችግሩን አምኖ እርዳታውን ለማሳለጥ ከመትጋት ይልቅ ገና ተቃዋሚዎች ረሃቡን እነሱ በዘመነ ደርግ እንዳደረጉት የረሃብ ፖለቲካ እንዳያወግዟቸው ፣ እንደያሳጧቸው ፣ የስልጣን ወንበሩ በተቃውሞ መነቃነቅ እንዳይፈጠር የእኛው ቀርቶ የውጭ መገናኛ ብዙሃንን መረጃ ዘገባ “ውሸት ነው !” እያሉ ማጣጣል መያዛቸው ያላመመው ያለ አይመስለኝም ! አሁን አሁንማ ” አል ኒኖ ” የተባለው አለም አቀፍ የአየር ጸባይ ችግሩን ማስከተሉን የካደ ያለ ይመስል ” አል ኒኖ ” ተብየው መጋኛው ምክንያት ሆኖ አስር ጊዜ እየተደረደረ ” እርዳታው ጅቡቲ ገብቷል ፣ ለተረጅዎች እርዳታ እያከፋፈልን ነው! ” የሚለው አደንቋሪ ፕሮፖጋንዳ ቀጥሏል የምለው ከድርቁ ሸሽተው ሳውዲ በአሳር በመከራ የገቡ እማኞቸን አግኝቸ ያንዣበበውን አስከፊ አደጋ ” እህ ” ብየ ሰምቻለሁና ነው !

አንድ አፍታ ረሃቡን ሸሽተው ሳውዲ ከገቡት እማኞች ጋር …
ረሃቡን ሸሽተው ሳውዲ የገቡት የረሃቡ እማኞች አግኝቻቸው ሲናገሩ ሀምሌ አልፎ ነሃሴ 2007 ሲጠባ በራያ ቆቦ አደጋው ታይቶ ሰው መፈናቀል መሰደድ ጀምሮ ነበር ። አረ ምን ይህ ብቻ ልማት መር የአርሶ አደሩን ኑሮ ክፋት ፣ ጉዳት በቅጥ በቅጡ ያስቀምጡታል … ያንን አስደንጋጭ ወግ ለዛሬ ትቸ ወደ ረሃቡ ስንመጣ ከሶስት ወር በፊት የክልሉ ተጠሪዎች አደጋውን ከአፍንጫቸው ስር እያዩ ” አደረግን !” ለማለት ብቻ እርዳታ ቢጤ ለአንዳንድ የገበሬ ቀበሌ ማህበር ጀምረው እንደ ነበር እማኞቹ አልካዱም ። ያም ሆኖ እርዳታው ለአንድ ቤተሰብ አምስት ኪሎ እህል መስፈር ሲጀምሩ እህሉ እንኳንስ በረሃብ የተጎዳ ጎንን ሊጠግን ዘመድ ለዘመድ መለያየቱን ሲናገሩት ያማል … እንዲህ እንዲህ እያለ ነሀሴ ተሸኘና መስከረም ጠባ ፣ የተዘራው ፍሬ በድርቁና በቀበኛው ወፍ ተበላባቸው ፣ የተረፈው አዝመራ እንኳንስ መተዳደሪያ ለእለት ጉርስ የሚሆን የሚላስ የሚቀመስ መጥፋቱን አጫውተውኛል። በዚህ መንገድ እያስገመገመ የመጣው ድርቅ ማሳያ በርካታ ምልክቶች ሲታዩ ወንድም እህቶቸ ረሃቡን ሸሽተው ሞትን ደፍረው ወደ አረባዊቷ ሳውዲ በሶማሊያና በየመን አድርገው መግባት ጀመሩ …

ብዙዎቹ ባህሩን ተርፈው በጦርነት አለንጋ ወደ ምትበጠበው የመንና በሳውዲ በርሃ ሲያቋርጡ በጥይት አሩር ፈጃቸው ፣ የበርሃ ውሃ ጥምና በደላሎች ግፍ በርሃው የተበሉት ተበልተው የተረፉት ተረፉ … እነሆ አማኞቸ በመንገድ ሲያልፉ ያጋጠማቸውን ሬሳ ሲያገኙ የቻሉትን እየቀበሩ ያልቻሉትን ልባቸው እየተሰበረ ለአሞራና አውሬ ቀለብ ጥለዋቸው ሳውዲ መግባታቸውን እያለቀሱ ግን በብስጭትና ምሬት አጫውተውኛል !

የረሃቡ ክፋት በገፈት ቀማሾች እንዲህ ሲገለጽ የኢህሃዴግ መንግስት ስለተራቡትና ስለ እርዳታው ስርጭት የመረጃ ግልጽነት ጎድሎት ማየት ያማል ። ዛሬ አለም በመረጃ ልውውጥ ለመጥበቧ ከዚህ በላይ ምስክርነት የሰጡኝ ሞት አይፈሪዎች የረሃቡ ስደተኞች ናቸውና የሰጡኝ መሬት ላይ ያለ እውነቱን ጠቋሚ ከሆነ መልካም ነው ። ታዲያ ኢህአዴግ በዚህ ከብርሃን ፍጥነት ባለይ በሚወረዎረው የመረጃ ዘመን ከአፍንጫ ስር ያለን ረሃብ መደባበቁና ግልጽ አለመሆን ምን ይባላል ? ይህስ እድገት ምጥቀትን ነው ወይስ ውድቀት ዝቅጠትን ያሳያል ? መልሱን ለእናንተ ልተወው …

ቀናኢው የሳውዲ ነዋሪ ለተጎዳው ወገኑ …
በሳውዲ የሚገኙ በርካታ ኢትዮጵያውያን የረሃቡ መረጃ መናኘት ከጀመረ ወዲህ እርዳታ በማሰብ ወገኖቻችን ለመርዳት ከፍ ያለ ፍላጎት እንዳላቸው እየገለጹ ይገኛሉ ። በሳውዲ አረቢያ ያለው ወገን እንኳን ለሀገሩ ለተራው የተጎዳ ወገኑ አይጨክንም ። ዳሩ ግን ከፖለቲካው ጀምሮ በስደት መከራ ለሚንገላታው የመብት ጥበቃ ጉድለት መንግሰትን እየሸሸ ቢገኝም የወገኑ ህመም ህመሙ ነውና ጨክኖ አያውቅም ! ምንም እንኳን መንግስት ለሚያደርገው የተለያየ ድጋፍ ጥሪ በአሳር በመከራ ተቀስቅሶ የረባ እርዳታ ሲለግስ አለመታየቱ ባይደንቅም ተራው ዜጋ ተቸገረ ብየ እኔ በአቅሜ ስጠይቅ ያገኘሁት ተደጋጋሚ ምላሽ ምስክሬ ነው ። ይህንን አስረግጨ አንድናገር ከጅማው አርሶ አደር ከጀማል ፣ እስከ ቁንፊዳው መሀመድ ሁሴንና አሁን እርዳታ በመሰብሰብ ላይ ያለሁት በሀኪሞች ስህተት 9 አመት አልጋ ላይ ለዋለው ለብላቴናው መሀመድ አብድልአዚዝ እናት ሃሊማ የማሰባስበው እርዳታ ለነዋሪው ቀናኢነት ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል ! በቅርቡም በዋና ከተማዋ ሪያድ ኢትዮጵያውያን በሀጅ አደጋ ለተጎዱ አንዳንድ ወገኖች እያደረጉ ያሉት እርዳታ ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል ። በተለይም በአፍሪካ ቲቪ ቀርበው ሀይማኖታዊ ትምህርት ይሰጡ የነበሩትና በሐጅ የሚና ጀማራት አደጋ የደረሰባቸው ኡስታዝ አህመድ ሙስጦፋ የተባሉ የእስልማና ሀይማኖት ልሂቅ ለመርዳት በሪያድ በተጠራው የድጋፍ ማሰባሰቢያ ጥሪ በአንድ ምሽት በማህበራዊ ድህረ ገጾች በተደረገ ጥሩ ብቻ 609,000 ስድስት መቶ ዘጠኝ የሳውዲ ሪያል ወይም በብር ወደ 3.5 ሚሊዮን የሚገመት ብር መሰብሰቡን በማሰባሰቡን ላይ የተሰማሩ አንድ ወንድም ሲያጫውቱኝ ይህ ገንዘብ ገና በዋትሳፕ what’s up “ሶሻል ሚዲያ ” Social Media በመሰብሰብ ላይ ያለውን እንደማይጨምር ከነተጨባጭ መረጃው አሳይተውኛል ! ይህን ማለቴ የሚሰበስብ የሚያዳምጠው ያጣው ስደተኛ እንኳንስ‪#‎ክፉ_ቀን‬ ለመጣበት ለሀገር ለወገኑ ለተራው ነዋሪ የእርዳታ ድጋፍ ለማድረግ ቀናኤ መሆኑን ለማሳየት ከረዳችሁ ደስ ይለኛል !

የረሃብ ፖለቲካውን እንተወው … ለወገኖቻችን እንድረስላቸው !
” ረሃብ ጊዜ አይሰጥም ” ይባላል እውነት ነው ! ለመገናኛ ብዙሃን ቅርብ ያልሆኑት የኢህሃዴግ መንግስት በረሃብ ለተጎዱት እርዳታውን ከማከፋፍልና ተጎጅዎችን ወደ ተሻለ ቦታ ከማስፈር ጀምሮ ስለተከሰተው ድርቅ አደንቋሪ ፕሮፖጋንዳን አቁመው ግልጽ መረጃ ሊሰጡን ይገባል ! ከምንም በላይ በዚህ ጊዜ የተጎዳውን ወገን አንድ ሆነን ቀን ከማይሰጠው የረሃብ አለንጋ ወገናችን ለማትረፍ ልዩነትን አስዎግደን በጋራ ልንቆም ይገባል ! ተቃዋሚዎችም ሆኑ ኢህአዴግ እርዳታውን ለዘባተሎው ፖለቲካ መጠቀሚያ ከማድረግ ተቆጥበው በህብረት ለተጎዱት ወገኖቻችን እርዳታ እንዲደርስላቸው የየበኩላቸውን ሊያደርጉ ይገባል ! ” ስለ ኢትዮጵያ ያገባናል !” የምንል ሁሉ ዜጎች በረሃቡ ፖለቲካ ከመባዘን ተቆጥበን ማትረፍ ስላለብን ወገናችን ልናስብ ይገባል ! ካለፈው እንማር ፣ የረሃብ ፖለቲካውን እንተወው … ለወገኖቻችን እንድረስላቸው መልዕክቴ ነው !

#ክፉ_ቀን ‪#‎Ethiopianfamine‬

ከምንም በላይ ፈጣሪ ይታደገን ፣ ቸር ያሰማን !

ነቢዩ ሲራክ
ህዳር 3 ቀን 2008 ዓም

Filed in: Amharic