>

እስር፣ ወከባ እንደገና! [ኣቶ ኣስራት ኣብርሃ ]

Asrat Abrhaየእውነተኛው አንድነት አመራሮች በትናንትናው ዕለት ግንቦት 7/2007 ዓ.ም. በደህንነት ኃይሎች እስር እና ከፍተኛ ወከባ ተፈፅሞባቸዋል። የማህበራዊ ጉዳይ ሀላፊ የነበረው አቶ አለነ ማህፀንቱ በትናንትና ዕለት ያለፍርድ ቤት ማዘዣ በደህንነት ኃይሎች ታፍኖ የተወሰደ ሲሆን፤ በኃይልና በድብደባ የኢሜል አድራሻውንና ፓስዎርድን ከወሰዱ በኋላ ጉለሌ ፖሊስ ጣቢያ አምጥተው እንዲታሰር አድርጓል። ከዚህም በተጨማሪ የአንድነት ሊቀመንበር የነበሩት አቶ በላይ ፍቃዱ እና ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበሩ አቶ ተክሌ በቀለ በተመሳሳይ ዕለት በደህንነት ኃይሎች ሲዋከቡ የዋሉ ሲሆን ማስፈራሪያና ማስጠንቀቂያ ተስጥቷቸወዋል።

እንግዲህ አንድነትን አፍርሰው፤ በህገወጥ መንገድ ለተላላኪዎቻቸው ካስረከቡ በኋላ፤ እንዲህ በሀገራችን እንኳ በሰላም መኖር እንዳንችል በወከባና በክትትል፤ በእስርና በማስፈራሪያ መከራችን የሚያሳዩን ምን ፍጠሩ እንደሚሉን ግልፅ አይደለም፤ ሰርተን መኖር አልቻልም፤ ወይ ይሰሩን ወይም በግልፅ ሀገሩን ልቀቁልን ይበሉንና ሀገር አልባ ሆነን እግራችን ወደ አመራው እንሂድላቸው፤ ቀድሞውስ መቼ ሀገር ነበረን፤ ሀገር ቢኖረንማ እንዲህ ሁሉም ነገር ባዕድ ሆኖብን ባልኖርን ነበር።

እኔ በሀገሬ ተስፋ ቆርቼ አላውቅም፤ እነዚህ ሰዎች ምን አድርጉ እንደሚሉን ግን አይገባኝም፤ በሆነ ባልሆነ ነገር በባነነ ቁጥጥር እኛን ማሰርና ማስፈራራት መፍትሄ ያደረጉት ነው የሚመስለው፤ ሰው እንዴት በሀገሩ በሰላም መኖር ይከለከላል፤ አሁን እኛ ምን እንዳናደርግ ነው የሚፈልጉት፤ በቃ በኃይል ፓርቲያችንን ሰርፈውን የለ ከዚህ በላይ ምን ይፈልጋሉ፤ የግል ንብረታችንን እንኳ ማውጣት እኮ አልቻልም፤ ለምሳሌ የእኔ አንድ አዲስ ኮት እዚያ ቀርቷል፤ ቢሮዬ ውስጥ ለምሳ እንደወጣሁ ነበር ፖሊሶች መጥተው ጽ/ቤቱን የወረሩት፤ እኔም ምናልባት ያመጧቸው ሰዎች ኮት የሌላቸው ሊሆኑ ይችላሉ ብዬ ዝም አልኩ፤ መቼስ የእኔ ኮት ከአንድነት አይበልጥ!
በትግርኛ አንድ ተረት አለ፤ “ወይ እንዳሉህ ሁን ወይም ሀገራቸውን ልቀቅላቸው” የሚል፤ ጎበዞቹ ይህን ተረት በተግባር እያዋሉት ይመስላሉ፤ ልዩነቱ ሀገሩ የእኛም መሆኑ ላይ ነው! ሀገራችን ለቀን ወዴት እንሂድ እኔማ በእንዲህ ዓይነት ስርዓት ስር መኖር እንዴት እንደመረረኝ… መግለፅ ከምችለው በላይ ነው! ሀገር እንዲህ ያስጠላል፤ እንዲህ ተስፋ አስቆራጭ ይሆናል!

Filed in: Amharic