>

የመለስ ግድብ ሕዳሴ ከንቱ ዉዳሴ? [ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም]

ትርጉም – በነጻነት ለሀገሬ

ግድቡን መገንባት ወይም ደግሞ እርግፍ አድርጎ መተው የሚለው የመለስ ጥያቄ ነበር፡፡

Ethiopia- The Meles Jinx, the GERD Nixed-by Aelmayehu G.Mariamከዛሬ አራት ዓመታት በፊት እ.ኤ.አ ሚያዝያ 2/2011 አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ በምዕራብ ኢትዮጵያ በሚገኘው ቤንሻንጉል ጉሙዝ እየተባለ በሚጠራው “ክልል” ልዩ ስሙ ጉባ በሚባለው ቦታ በመገኘት በዚያን ወቅት የሚሊኒየሙ ግድብ/Millennium Dam እያለ ይጠራው የነበረውን እና እንደገና በኋላ ደግሞ በደቀ መዛሙርቶቹ አማካይነት ታላቁ የኢትዮጵያ የሕዳሴ ግድብ (ታኢሕግ)/Grand Ethiopian Renaissance Dam (GERD) እየተባለ እስከ አሁንም ድረስ በዚሁ ስያሜ የሚጠራውን ግድብ የመሰረት ድንጋይ በመጣል የቅዠት ህልሙን እና ራዕይውን አስቀምጦ ነበር፡፡ በዚያን ዕለት የመሰረት ድንጋዩን ካስቀመጠ በኋላ አስቀድሞ በሚታወቅ ነብያዊ ትንበያ በሚመስል መልኩ አቅርቦት የነበረው እንዲህ የሚለው ንግግሩ በአሁኑ ጊዜ በስልጣን ማማ ላይ ከህዝብ ፈቃድ ውጭ ተፈናጥጠው የሚገኙትን እና እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ (ህወሀት) እያለ በሚጠራው ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አምባገነን ደቀመዛሙርቶች መንፈስ ላይ እንዲህ የሚለው የመለስ ሙት መንፈስ በጠራራ ጸሐይ እየተመላለሰ እረፍት ነስቷቸው እና አስጨንቋቸው ይገኛል፡

“የግድቡ ጠቅላላ የግንባታ ወጭ ግምት 3.3 ቢሊዮን ዩሮ ወይም ደግሞ 78 ቢሊዮን ብር ይሆናል፡፡ በዕቅዳችን ይዘን ገንዘብ አፈላልገን እና መድበንላቸው እየተገበርናቸው እንዳሉት ሌሎች ፕሮጀክቶቸ ሁሉ የዚህ የግድብ ፕሮጀክት ወጭም ተጨማሪ በመሆን ከፍተኛ የሆነ ጫና ፈጥሮብናል፡፡ ይህንን የገንዘብእጦት ጫና ለማቃለል ያደረግናቸው ሁሉም ጥረቶች ሁሉ ዉጤታማ ሳይሆኑ በመቅረታቸውአሁን ለማድረግየምንችላቸው ሁለት አማራጮች ብቻናቸው፡፡ እነርሱም ፕሮጀክቱን እርግፍ አድርጎ በመተው እጅን አጣጥፎ መቀመጥ ወይም ደግሞ ለግንባታው ስራ አስፈላጊ የሆነውን ገንዘብ ለማግኘት በእራሳችን አቅም ገንዘብ ማሰባሰብ አለብን፡፡ ከእነዚህ ከቀረቡት አስቸጋሪ ምርጫዎች መካከል የኢትዮጵያ ህዝብ የትኛውን አማራጭ እንደሚመርጥ ያለጥርጥር አውቀዋለሁ፡፡ የፈለገውን ያህል ድሆች ብንሆንም ችግርን የመፍታት ልምዳችንን ከግንዛቤ በማስገባት የኢትዮጵያ ህዝብ ማንኛውንም ዓይነት መስዋዕትነት ይከፍላል፡፡ ግድቡን እንገነባዋለን የሚል አንድ ድምጽ እንደሚያሰሙ ምንም ዓይነት ጥርጣሬ የለኝም፡፡“ (አጽንኦ ተጨምሮበታል፡፡)

በአሁኑ ጊዜ የግድቡን የግንባታ ስራ እርግፍ አድርጎ የመተው ጊዜ ደርሷልን?

ምንም ይሁን ምን መለስ ለመጨረሻ ጊዜ ባደረገው ትንታኔው በአፍሪካ ታላቅ እና ግዙፍ የሆነ የስሚንቶ ግንብ ገንብቶ ስሙን ለእድሜ ልክ ለመዘከር እንዲቻል ከተፈለገ አስተማማኝ እና ግዙፍ የሆነ ገንዘብ ማግኘት እንደሚያስፈልግ ተገንዝቦት ነበር፡፡ መለስ በዚህ ፕሮጀክት ሰበብ ብትታለብ ብትታለብ የማትነጥፍ ጥገት ላም ለማግኘት ሲል ዕርባናየለሽ ዕቅዱን አዘጋጅቶ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴው ለመግባት ሙከራ በማድረግ ላይ ነበር፡፡

በአጭሩ መለስ በዚያ ጉባ በተባለው የግድብ ፕሮጀክቱ ቦታ ላይ በመገኘት ያን የመሰለ በስሜት የተሞላ እና እርባናየለሽ ንግግር ካደረገ በኋላ በቀጣይነት ሁሉም በሀገር ውስጥ እየተንቀሳቀሱ ያሉ ባንኮች ለሚያበድሩት ለእያንዳንዱ ብድር 27 በመቶ በሚሆነው ገንዘብ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ያዘጋጀውን ቦንድ እንዲገዙ እና መንግስት በቀጣዮቹ 16 ወራት ጊዜ ውስጥ ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት የሚያገለግሉትን የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ለመተግበር የሚያስችል 12.6 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ እንዲቻል ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡

በትውልድ ኢትዮጵያዊ የሆኑት የሳውዲ ቢሊየነር መሀመድ አል አሙዲ እ.ኤ.አ መስከረም 2011 ለታኢሕግ/GERD ግንባታ በሚል 1.5 ቢሊዮን ዶላር (88 ሚሊዮን ዶላር አካባቢ) መዋጮ አደረጉ፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ ባለፈው ወር ይፋ የሆነ አንድ ዘገባ እንዲህ የሚል ጽሁፍ አስነብቧል፣ “በኢትዮጵያ በነዳጅ ዘይት ግብይት የመሪነት ቦታውን የያዘው የግል ኩባንያ በ5 ቢሊዮን ዶላር ወጭ በሚቀጥሉት 10 ዓመታት ውስጥ የነዳጅ ዘይት ማጣሪ ፋብሪካ ለመገንበታ ዕቅድ አወጣ… ከዚህ ኩባንያ ባለአክሲዮኖች ውስጥም በግንባታ፣ በወርቅ ማዕድን ቁፋሮ፣ በሆቴሎች እና በኃይል ዘርፎች ተሰማርተው የሚገኙት እና ከ10 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሀብት እንዳላቸው የሚነገርላቸው የሳውዲ ቢሊየነር የሆኑት መሀመድ ሁሴን አል አሙዲ ይገኙበታል…“እነዚህ የብሄራዊ ነዳጅ ዘይት ማጣሪያ ፋብሪካ በቀጣዮቹ 10 ዓመታት ውስጥ እንገነባለን የሚሉት ባለአክሲዮኖች ቢያንስ ጥቂት ቢሊዮንዶላሮችን እንኳለታኢሕግ/GERD ግንባታእንዲውል ማድረግ አልነበረባቸውምን? (ምን መናገር እንዳለብኝ የምታውቁትን ነውእተናገርኩያለሁት፡፡)

እ.ኤ.አ ግንቦት 2012 እንደ መንግስታዊ የዜና ወኪሎች ዘገባ ከሆነ አምባሳደር ግርማ ብሩ እንዲህ የሚል ዘገባ አውጥተዋል፣ “በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ የ3.3 ሚሊዮን ዶላር የቦንድ ሽያጭ ተከናውኖ ከዚህ ውስጥ ከ123 ሺ ዶላር በላይ ተቀብለናል፡፡“ ያ ዘገባ እንዲህ የሚል ያልተረጋገጠ መረጃ ይፋ አድርጓል፣ “ከ1.5 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተሰበሰበው በዋሽንግተን ዲ.ሲ ከሚኖረው የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ነው፡፡“

እ.ኤ.አ ሀምሌ 2012 ህይወቱ ያለፈውን የመለስን ሞት በመደበቅ እ.ኤ.አ መስከረም 2012 በመገናኛ ብዙሀን እና በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ በማለት መለስ ለህዝብ ስራ ሌት ከቀን ተወጥረው ስለሚውሉ የስራ ጫና በጣም ይበዛባቸው ስለነበር እና ኃይለኛ የድካም ስሜት ስለሚታይባቸው ከድካማቸው ለማገገም እንዲችሉ እረፍት ላይ ናቸው በማለት በዚያን ወቅት የኮሙኒኬሽን ሚኒስትር እና የታኢሕግ/GERD የገንዘብ ማሰባሰብ የብሄራዊ ኮሚቴ የጋራ ሊቀመንበር የነበረው እና የሀሰት እና የቅጥፍና ዘገባ በማሰራጨት የሚታወቀው በረከት ስምኦን እስከዚያ ጊዜ ድረስ ለፕሮጀክቱ ግንባታ 5.5 ወይም ደግሞ 6 በመቶ ወለድ ለመክፈል የሚታሰብ ቦንድ በመሸጥ ከህዝቡ 5 ቢሊዮን ብር እንደተሰባሰበ ይፋ አድርጎ ነበር፡፡ (በረከት ስምኦን አሜሪካ በኢራቅ ላይ ከፍታው በነበረው ጦርነት ወቅት የጦርነቱን ሂደት እየተከታተለ ይዘግብ የነበረውን እና እንደ አክርማ የሚሰነጠቅ ቀጣፊ እና አስመሳይ የነበረውን የሳዳም ሁሴን የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር የነበረውን እና እንዲህ ይል የነበረውን ኬሚካል ዓሊ የተባለውን ቀጣፊ ኮሚክ አስታወሰኝ፣ “አሜሪካኖች እየተማረኩ ለኢራቅ ጦር ኃይል እጃቸውን ይሰጣሉ ወይም ደግሞ በታንኮቻቸው ላይ እንዳሉ ዶግ አመድ ሆነው እዚያው ይቀበራሉ፡፡“ እጹብ ድንቅ ነው፣ የኢራቅን የጦር ኃይል አባላት እየማረኩ እና እያሳደዱ የነበሩት የአሜሪካ የጦር ኃይል አባላት እንጅ ኢራቃዊያን አልነበሩም፡፡ በእርግጥ ቀጣፊው ኬሚካል ዓሊ የአሜሪካኖችን ዕጣፈንታ በእንደዚያ ያለ የውሸት ዘገባ ጥላሸት እየቀባ በነበረበት በዚያ ጊዜ አሜሪካኖች ጦርነቱን በድል አድራጊነት ከፍጻሜ አድርሰው እና አጠናቅቀው ታንኮቻቸውን እና ሌሎች የጦር ተሽከርካሪዎቻቸውን ከኢንፎርሜሽን ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ውጭ ፊትለፊት መስመራቸውን እያስያዙ በተረጋጋ ሁኔታ አቁመዋቸው ይታዩ ነበር፡፡ እንደዚሁም ሁሉ በረከት ስምኦን በተመሳሳይ መልኩ እንደ ኬሚካል ዓሊ ሙጥጥ ያለ ቅጥፈትን በተላበሰ መልኩ ዓይኑን በጨው ታጥቦ መለስ ቀደም ሲል ሞቶ እያለ እና ከታመኑ የዜና ምንጮች ውስጥ ለውስጥ በመዘግቦ ላይ እያለ ይህንን ሀቅ ሙልጭ አድርጎ በመካድ በውሸት በነተበው አንደበቱ በስራ ውጥረት ምክንያት ጫና ስለነበረባቸው ከድካማቸው ለማገገም በማሰብ በእረፍት እና በሽርሽር ላይ ናቸው በማለት በዓለም ህዝብ ላይ ዓይን ያወጣ ታላቅ የውርደት ውሸት ዋሸ፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 2013 የግድቡ ጠቅላላ ግምታዊ የግንባታ ወጭ 4.7 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡

እ.ኤ.አ መስከረም 2012 የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት/International Monetary Fund የኢትዮጵያ ኃላፊ የሆኑት ጃንሚከልሰን የመለስን አገዛዝ እንደ ሰካራም የመርከብ ነጅ ግዙፍ የሆነ ወጭ ማውጣቱን እንዲያቆም እንዲህ የሚል ተማጽዕኖ አቅርበው ነበር፣ “አንዳንድ ፕሮጀክቶች ሁሉንም በሀገሪቱ ውስጥ ያለውን ገንዘብ እንዲይዙት በማድረጉ ሂደት ላይ ቆም ብሎ ማሰብን ይጠይቃል… ሁሉንም በሀገሪቱ ውስጥ የሚዘዋወረውን ገንዘብ በጥቂት ፕሮጀክቶች ላይ ብቻ እንዲውል ማድረግ ሁሉም ገንዘብ ለዚያ ፕሮጀክት ብቻ አገልግሎት ታሳቢ በማድረግ ሌሎችን የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴዎች ይገድባል፡፡ እናም በተለመደው መልኩ ቀን በቀን ሁልጊዜ ለሚከናወነው ንግድ እና ቢዝነስ የሚውል ገንዘብ አይኖርም፡፡“

እ.ኤ.አ ሰኔ 2013 እንደዚሁ ከባንኮች ጋር በተያያዘ መልኩ ሚከልሰን መለስ እ.ኤ.አ ሚያዝያ 2011 በግድቡ ቦታ ላይ በመገኘት ያደረገውን ንግግር ተከትሎ በግል ባንኮች ላይ የተጣለው 27 በመቶ የቦንድ ግዥ ግዴታ በኢትዮጵያ ባሉ ባንኮች ላይ ታላቅ ጫናን ፈጥሯል፡፡ ይህ ሁኔታ በመፈጠሩም የተጠናከረ የባንክ አገልግሎት መስጠት አይችሉም…ባንኮች ከዚህ ግብይት ጋር በተያያዘ መልኩ የሚያደርጉትን ግብይትም እንዲያጡ ያደርጋቸዋል፣ ይህም በመሆኑ በጣም አስቸጋሪ ሁኔታን ፈጥሮባቸዋል“ ብለው ነበር፡፡

በአሁኑ ጊዜ ተራው ህዝብ ለህዳሴው ግድብ እየተባለ ካለችው ለኑሮ ከማትበቃ ጥቂት ገቢው ውስጥ ከገንዘብ መክፈያ ሰነድ ላይ በመቀነስ የግዴታ ክፍያ ወይም ደግሞ በግድ መዋጮ እንዲያደርጉ እየተደረጉ ነው፡፡ ከፍተኛ ቁጣን ቀስቅሶ የነበረው የቦንድ ሽያጭ በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ያልተመዘገቡ ሰነዶችን በውጭ ሀገር መንግስት ወይም ደግሞ በተወካዮቹ አማካይነት መሸጥ በአሜሪካ የፌዴራል እና የአካባቢ ግዛቶች ህገወጥ ድርጊት ነው በማለት ለህወሀት ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ “ምክር” ከሰጠሁ በኋላ በአሁኑ ጊዜ ቢያንስ በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ፍጹም በሆነ መልኩ የቆመ ይመስላል፡፡

በግድቡ ዙሪያ እስከ አሁን ድርስ በተጨባጭ የተሰበሰበው የገንዘብ መጠን ምን ያሀል እንደሆነ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡

ቁንጮ ከሆኑት ከማይታወቁ እና ስምየለሽ ከሆኑት የህወሀት አመራሮች በስተቀር ማንም ቢሆን እስከ አሁን ድረስ ምን ያሀል ገንዘብ እንደተሰበሰበ እና የተሰበሰበውም ገንዘብ ለግድቡ በምን ዓይነት መንገድ በስራ ላይ እየዋለ እንዳለ የሚያውቅ የለም፡፡ የታኢሕግ/GERDን በሚመለከት ስለተሰበሰበው ግንዘብ ሁኔታ በጣም ጥቂት የሆነ መረጃ ብቻ ነው ያለው፡፡ አጠቃላይ እና ፍጹም የሆነ ሚስጥራዊነት የወያኔ የኃይማኖት መጽሐፍ ነው፣ እናም ወያኔዎች ከፍሪማንሰንስ ወይም ደግሞ ከኢሉሚናቲ (እራሳቸውን ብርሀን አምጭዎች ብለው ከሚጠሩት ስውር አጧዦች) የበለጠ ድብቆች ናቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በ10 ሚሊዮኖች በሚቆጠሩት በእርሱ ደጋፊዎች እና ወዳጆች ዘንድ ተፈቃሪ እና ተወዳጅ የሆነው የመለስ ዜናዊ ሞት መንስዔ ምን እንደሆነ የማይታወቅ የዘራፊ ወሮበላ መንግስታዊ ሚስጥር ነው፡፡ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩት ደጋፊዎቹ እና አፍቃሪዎቹ እንኳ ስለመለስ ሞት መንስዔ ምንም ዓይነት የሚያውቁት ፍንጭ የላቸውም፡፡ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ መሬት ለሱዳን አሳልፎ የመስጠቱ ዓለም አቀፋዊ የሸፍጥ ስምምነት እና ሌሎች ግብይቶችም ምክንያታቸው ምን እንደሆነ የማይታወቅ ድብቅ ሚስጥሮች ናቸው፡፡ መሰረቱን በህንድ ሀገር ካደረገው የግብርና ቢዝነስ ከሆነው ከካሩቱሪ ጋር ያላቸው ግብይት መለስ ተናግሮት እንደነበረው እ.ኤ.አ በ2015 ኢትዮጵያ በምግብ እህል እራሷን ለመቻል የሚያበቃት እየተባለ ሲደሰኮርለት የነበረውም ምን እንደሆነ የማይታወቅ ሚስጥር ነው፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት በካሩቱሪ ላይ የደረሰው ኪሳራ ግን በምንም ዓይነት መልኩ ሚስጥራዊ ሊሆን አልቻለም፡፡ ለካሩቱሪያውያን የእፎይታ ግልግል ነው፡፡ ገንዘብ የሚፈስስባቸው ሁሉም የመንግስት ፕሮጀክቶች የሂሳብ ሰነዶች ሁሉ በከፍተኛ ደረጃ ሚስጥራዊ ናቸው፡፡

የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ስላከናወኛቸው ተግባራት እና ስለስኬቶቹ ሁሉ የሚያቀርባቸው ዘገባዎች በከፍተኛ ደረጃ መረጃን ያዛቡ እና በቅጥፈት የተሞሉ እንዲሁም ለህዝብ ግንኙነት ፍጆታ ሲባል የማታለያ ስራውን እውነተኛ እና ታማዕኒነት ያለው ለማስመሰል በሌላ ሶስተኛ ወገን የውሸት ምስክርነት እንዲሰጠው ያደርጋል፡፡ ወያኔ ገና ከጫካ ከነበረበት ጊዜ ጀምሮ እንደዚህ ያለ የህዝብ ግንኙነት ስራ ይሰራ እንደነበረ አምናለሁ፡፡ ይህንንም የጫካ ተሞክሯቸውን መንግስታዊ ስልጣንን በኃይል ከተቆጣጠሩ በኋላ የበለጠ ከፍ ወዳለ እና ወደላቀ ደረጃ በማሸጋገር በቀላሉ ሊሞኙ የሚችሉትን፣ ሰነፎችን እና ህሊና የሌላቸውን የምዕራባውያንን መገናኛ ብዙሀን ለእራሳቸው መጠቀሚያ በማድረግ ይገለገሉባቸዋል፡፡ የወያኔን የህዝብ ግንኙነነት ታዛዥ ሎሌዎች አደንቃቸዋለሁ፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ የእውቀት ደረጃ ከንቀት ላይ ሊጥል በማይችል መልኩ ነው መግለጫዎችን የሚሰጡት፡፡

ላለፉት በርካታ ዓመታት የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ መረጃ የማዛባት እና የማጥፋት አባዜ እንዲህ የሚል ሆኖ ይገኛል፣ “ባለፉት አስርት ዓመታት ኢትዮጵያ 11.7 በመቶ የሆነ ባለሁለት አሀዝ የምጣኔ ሀብት ዕድገት በማስመዝገብ ላይ ትገኛለች፡፡“በእርግጠኝነት ሸፍጥን የተላበሰ ተራቅጥፈትነበር! ከምንም ጥርጣሬ በላይ በሆነ መልኩ ይህንን ተራ ቅጥፈት እና ነጭ ውሸት በተጨባጭ መረጃ ላይ በመመርኮዝ፣ “የኢትዮጵያ የባለሁለት አሀዝ የምጣኔ ሀብት ዕድገት ተራ የሆነ ቅጥፈት፣ ነጭ ውሸት እና የቁጥር ጨዋታ ነው” (ወያኔዎች በጥርሳቸው ይዘው የሚቀጥፉበትን፣ የሚዋሹበትን እና የሚያጭበረብሩበትን ለመግለጽ የተጠቀምኩበትን ቃል በማያያዝ በስራ ላይ የዋለ) በማለት ማጋለጥ በመቻሌ ታላቅ ኩራት ይሰማኛል፡፡

ባለፈው ወር የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በታዛዥ የህዝብ ግንኙነት ሎሌው አማካይነት በሚቀጥሉት 10 ዓመታት ውስጥ በ5 ቢሊዮን ዶላር የነዳጅ ዘይት ማጣሪያ ፋብሪካ እገነባለሁ የሚል የቅጥፈት ዘገባ ይፋ አድርጓል፡፡ ወቼ ጉድ! አስቲ ወገኖቼ በአንክሮ እናስበው! የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በ4 ቢሊዮን ዳለር ወጭ የግድብ ግንባታ ስራውን መተግባር ሳይችል በመቅረቱ እንደ ጅብራ ተገትሮ ሲቀር በአደባባይ እየታዬ ባለበት ሁኔታ ጭራሽ አሁን ደግሞ ካፈርኩ አይመልሰኝ በሚል የአምባገነኖች እና የሞኞች ብሂል እንዲያውም ገንዘቡን ከፍ በማድረግ በ5 ቢሊዮን ዶላር የነዳጅ ዘይት ማጣሪያ ፋብሪካ ገንዘብ ከሰማይ እንደ መና ካልወረደ በስተቀር በምን ዓይነት ሁኔታ ሊገነባ ይችላል ተብሎ ይታሰባል? እብደት እና ድድብና ከማለት በስተቀር ሌላ ምን ይባል ይችላል!

ባለፈው ሳምንት የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ግዙፍ የሆነ የአውሮፕላን ማረፊያ ለመገንባት ዕቅድ ይዣለሁ በማለት እንዲህ የሚል ሌላ የቅዠት አዋጅ አስደምጧል፣ “ወደፊት ለመገንባት በዕቅድ የያዝነው የአውሮፕላን ማረፊያ ግዙፍ ነው፡፡ እጅግ በጣም ግዙፍ፡፡ ይህ የአውሮፕላን ማረፊያ በዓለም ላይ ከሚገኙት ታላላቅ የአውሮፕላን ማረፊያዎች መካከል አንዱ ነው፡፡ ለወደፊቱ እንደዚህ ያለ ግንባታ ለማከናወን የሚችሉ ሌሎች ሀገሮች ለመኖራቸው የሚታወቅ ነገር የለም፣ ሆኖም ግን በአፍሪካ ይህንን የመሰለ አቅም የፈጠረ ሀገር አይገኝም፡፡“ በዓለም ላይ “እጅግ በጣም ግዙፍ“፣ ትልቅ የአውሮፕላን ማረፊያ? ህም! ህም! ህም!

የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራሮች የእነርሱ የድንቁርና ደረጃ አዕምሯቸውን የሸፈናቸው ስለሆነ ምንም የማናስብ ደንቆሮዎች እንደሆንን አድርገው ያስባሉ፡፡ የአሜሪካ የሳቅ ተውኔት ባለሞያ የነበረው ኮናን ብሬን እንዲህ ሲል መናገሩ እውነትም ትክክል ነበር፣ “ሁሉም ውድቀት ሲደርስባቸው ሁልጊዜ በቅዠት ዓለም ውስጥ መኖር ይጀምራሉ፡፡“ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ፍጹም በሆነ መልኩ አሳፋሪ የሆነ ውድቀትን ተከናንበዋል፣ እናም በአሁኑ ጊዜ በመንገዳገድ ላይ የሚገኙት በቅዠት ከተሞሉት እርባናየለሽ የቅጥፈት ምናባዊ አስተሳሰቦቻቸው ጋር ነው! (እውነት ለመነጋገር እባካችሁ እንዲህ የሚለውን ጥያቄ ሊነግረኝ የሚችል ሰው ሊኖር ይችላልን፡ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ እንደሚመስለው እና እንደሚያስበው በእውነት እኛ እንደዚህ የማናስብ እና ምንም ነገር የማናውቅ ደደቦች ነን እንዴ?)

በግድብ ግንባታ ሰበብ የስነ ልቦና መዛባት፣

በአሁኑ ጊዜ ታኢሕግ/GERD እየተባለ በሚጠራው እና የሀሳቡ አፍላቂ እና ዋና መሀንዲስ በነበረው እና አሁን በህይወት በሌለው በመለስ ዜናዊ ሀሳቦች እና ህልሞች (ቅዠት አላልኩም) ላይ ጊዚያቸውን ወስደው በመመርመር እና በመፈተሸ ቁጣ በተቀላቀለበት መልኩ ክርከራቸውን የሚያጧጡፋ ወገኖችን ስመለከት እና ሳስብ በጣም ይገርመኛል፡፡ የመለስ ዋና ታማኞች እና ጽኑ ደቀመዝሙሮች በአሁኑ ጊዜ የመለስ አዳኝ ሙት መንፈስ የሆነው የስነ ልቦና መዛባት እየጮኸባቸው የሚይዙት የሚጨብጡትን አጥተው ግራ ተጋብተው ተቀምጠዋል፡፡

በመለስ እጀ ብድግ ተደርጎ በዙፋን ላይ እንዲቀመጥ የተደረገው በአደናጋሪ ንግግሩ የሚታወቀው እና አሻንጉሊቱ የይስሙላ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እ.ኤ.አ መስከረም በ2012 በተደረገው የጌታው የቀብር ስነስርዓት ላይ በመገኘት ሰውን ያህል ደካማ ፍጡር ያውም እንደመለስ ያለውን እጁ በወገኖቻችን ደም የተጨማለቀውን ተራ የአሸባሪ ቡድን እና ስብስብ ቁንጮ እንደ አምላክ አድርጎ በማሰብ እንዲህ የሚል ንግግር አሰምቶ ነበር፣ “ዘላለማዊ ክብር እና ሞገስ ለታላቁ መሪያችን!“ (ዘላለማዊ ክብር እና ሞገስ የሚለውን ሀረግ ለዚህች ዓለም ፈጣሪ ለሆነው ለአምላክ ብቻ የተተወ መሆኑን ነው የማምነው፡፡ ለፕሮቴስታንት እምነት ተከታዩ የይስሙላ ጠቅላይ ሚኒስትር ይኸ አምላካዊ የመጸሐፍ ቅዱስ ቃል ስልጣን እና ኃይል ሲበዛለት ጊዜ ተግልብጦ ታየው እንዴ!?) የይስሙላው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዲህ የሚል ሰውን ከመልዓክ አስበልጦ የሚያቀርበውን እና ከእውነት በእጅጉ የራቀውን ባዶ ጉራ አሰምቶ ነበር፣ ”አሁን በህይወት የሌሉት ብልሁ እና አርቆ አሳቢው መሪያችን“፣ እንደዚሁም ዲስኩሩን በመቀጠል “የትልቅ ስብዕና ባለቤት የሆኑት እና ህይወታቸውን ለህዝብ ጥቅም ሲሉ መስዋዕት ያደረጉ ልዩ ጀግና“፣ ይህ ብቻ በቂ አልነበረም እንዲያውም ሌላም በመጨመር “ዓላማ እና ራዕይ የነበረው ታላቁ እና ታዋቂው መሪያችን“… ወዘተ፣ ውሻ በበላበት ይጮሀል እንዲሉ ይህ የድንክ አስተሳሰብ ባለቤት የሆነው የይስሙላ ጠቅላይ ሚኒስትር ምን ያላለው ነገር አለ!?

ኃይለማርያም የባለዓላማ እና ራዕይ ባለቤት የነበረውን የእርሱን ታላቁ እና ታዋቂ መሪ ራዕይ ስኬታማ በሆነ መልኩ እውን እንደሚያደርግ ቃል ገባ፡፡ ኃይለማርያም እንዲህ በማለት አወጀ፣ “ከሁሉም በላይ ዋናው እና ትኩረት የሚሰጠው ነገር በእርግጥ የህዳሴው ግድብ ግንባታ ጉዳይ ነው፡፡ ታላቁ መሪያችን በከፍተኛ ደረጃ ቅድሚያ ሰጥተውት የነበረው የዚህን የግንባታ ፕሮጀክት እውን ከማድረግ ላይ ነው…ግድቡን ለማጠናቀቅ በእኛ ቁጥጥር ስር ያለውን ማንኛውንም ዓይነት ኃይል እንጠቀማለን፣ ይህንንም በማድረግ እንዲያውም ፕሮጀክቱን እንዲጠናቀቅ ከተቀመጠለት የጊዜ ሰሌዳ በፊት ለማጠናቀቅ ጥረት እናደርጋለን፡፡“ ድንቄም ከተቀመጠለት የጊዜ ሰሌዳ በፊት! ከዋሹ እና ከቀጠፉ አይቀር እንዲህ እያደረጉ እንደ አክርማ መሰንጠቅ ነው እንጅ!

ሁልጊዜ በመገናኛ ብዙሀን ባየሁት እና ንግግሩንም በሰማሁ ጊዜ የኢራቁ መሪ የነበረው የአምባገነኑ ሳዳም ሁሴን የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር የነበረው ኬሚካል ዓሊ ትዝ የሚለኝ በረከት ስምኦን የተባለው የሸፍጥ ጌታ የታኢሕግ/GERDን ጉዳይ በማስመልከት እንዲህ በማለት ገልጾት ነበር፣ “አሁን በህይወት የሌለው የጠቅላይ ሚኒስትራችን የአዕምሮ ልጅ የሆነውን ራዕይ ለማሳካት ተነሳሽነታችንን ማሳየት ይኖርብናል፡፡“

የመለስ ደቀመዝሙሮች ዘላለማዊ ክብር እና ሞገስ ለሰጡት ጌታቸው ወንጌል አፈጻጸም ተገዥነታውን አረጋግጠዋልን?

መለስ የእርሱ ደቀመዝሙሮች የእርሱን ትሩፋት ለማስቀጠል ወይም ደግሞ ለማቆየት እንደማይችሉ እራሱም በህይወት እያለ የሚያውቀው እና የእርሱን ታላላቅ እና ግዙፍ የቅዠት ምናባዊ ሀሳቦች እውን ማድረግ እንደማይችሉ ሊያሳዩ የሚችሉ በርካታ በቂ እና አሳማኝ የሆኑ ማስረጃዎች አሉ፡፡

መለስ የእርሱ ተቃዋሚ የሆኑትን የፖለቲካ ፓርቲ ድርጅቶች በሳምንቱ ባሉት ማናቸውም ቀናት ውስጥ መብለጥ እንደሚችል፣ በሀሳብ የበለጠ እንደሚልቅ፣ የበለጠ ብልህነትን የተላበሰ እንደሆነ፣ ማንንም ማሳመን እንደሚችል፣ በማንንም ሀሳብ ማሸነፍ እንደሚችል፣ በጥበብ እና በዘዴ መጓዝ እንደሚችል እና በእነዚህ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ላይ ከፍተኛ የሆነ ንቀት የማሳየት እምነት እንደነበረው ግልጽ የሆነ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡

በስፋት ያልታወቀው እውነታ ቢኖር መለስ በዙሪያው ከበውት ይኖሩ የነበሩትን ሳይጠሩ አቤት ወዴት ምን ልታዘዝ ይሉ ለነበሩት እና ለታማኝ እና ታዛዥ ሎሌዎቹ ያለው ንቀት (ምናልባትም ከተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች የበለጠ) ነው፡፡ በአጠገቡ የተኮለኮሉትን አብዛኞቹን በጥላቻ የተሞሉ፣ ተላላኪ ታማኝ አገልጋዮች፣ ለከርስ ጥቅም ሲባል ጌታቸውን የመልዓክን ኃያል አድርገው የሚያቀርቡ፣ አስመሳዮች፣ ጫማ ላሾች፣ እና የጌቶቻቸው አፈቀላጢዎች በእርሱ መልካም ፈቃድ ብቻ የሚኖሩና እና በሙስና መረቡ እንዳይያዙ እራሳቸውን በእርሱ ጥላ ስር ወሽቀው ከበከተው የሙስና ድርጊታቸው ለማምለጥ እየፈሩ እና እየተርበደበዱ የሚኖሩ ህሊናየለሽ ዘራፊ ሌቦች እና እምነተቢሶች ናቸው፡፡

በእርሱ ዙሪያ አካባቢ በአዲስ አበባ ለውኃ ወረፋ ሲባል ተደርድረው የሚገኙትን ብጫማ የውኃ መያዣ ጀሪካኖች በሚመስል መልኩ ተኮልኩለው የሚገኙትን አብዛኞቹን ታዛዥ ሎሌዎቹን በውል ማሰብ የማይችሉ ደደቦች፣ የአዕምሮ አስተሳሰብ ድሁሮች፣ ከእርሱ ማራኪ እና አስደናቂ ምሁራዊ ክህሎት በእጅጉ ያነሱ እና ምንም ነገር የማያወቁ ማይሞች አድርጎ ይቆጥራቸው ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ የፕሬዚዳንት ኦባማ የብሄራዊ ደህንነት አማካሪ የሆኑት ሱሳን ራይስ እ.ኤ.አ መስከረም 2012 በመለስ የቀብር ስነስርዓት ላይ በመገኘት እንዲህ የሚል ንግግር አሰምተው ነበር፣ “ጠንካራ፣ መንፈሰ ጽኑ እና የማይበገሩ“ በማለት ለአሜሪካ ፖለቲዊ እና ምጣኔ ሀብታዊ ጥቅሞቻቸው ሲሉ ስለኢትዮጵያ ሕዝብ መከራ እና ስቃይ ኬረዳሽ በማለት የሌለውን ስብዕና በመስጠት አሞካሽተውታል፡፡ በእርግጥ ለሞኞች እና ለደደቦች እራሱ እንደሚገልጸው ሁሉ በጣም አናሳ የሆነ ታጋሽነት ነበር ያለው፡፡ መለስ የሚስቅባቸው እና የሚሳለቅባቸው አብዛኞቹ ሞኞች እና ደደቦች የነበሩት በተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች አመራሮች ሳይሆን በወያኔ ወሮበላ የዘራፊዎች ቡድን ስብስብ ውስጥ ነበር፡፡ ያ በምንም ዓይነት መልኩ ሊደበቅ የማይችል እውነታ ነው! ለዚያም ነበር መለስ እርሱ ከሌለ የእርሱን ትሩፋት በመያዝ ወደፊት ሊያስቀጥል የሚችል አንድም ሰው፣ ምንም ነገር ሊኖር የሚችል እንደሌለ አሳምሮ ያውቅ የነበረው፡፡ የእርሱ ትሩፋት እርሱን የመሰለ ማንንም ሳይተካ አብሮት ሊቀበር እንደሚችል ያውቅ ነበር!

ጠቃሚ የሆነ ነጥብ ለማንሳት የሚከተሉትን እውነታዎች እና ጉዳዮችን እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡ ጥቂት የዜና ተንታኞች ወይም ደግሞ የመለስ ደቀመዝሙሮች እና አጎብዳጆች መለስ ስለታኢሕግ/GERD ግድብ ፕሮጀከት የተናገራቸውን ተጽዕኖ ፈጣሪ ንግግሮች በመግለጽ እንዲሁም ስለእነዚያ ንግግሮች ጠቃሚነት አጉልቶ በማሳየት በአሁኑ ጊዜ ቁጣን እና ስሜታዊነትን በተላበሰ መልኩ ውይይት ያደርጋሉ፡፡ ያ ንግግር ሲታሰብ እና ሲመረመር የመለስ የአዕምሮ ባህሪያዊ ሁኔታ ምን ያህል የአዳኝነት እና የማንአህሎኝነት በሽታ ተጠናውቶት እንደነበር ጉልህ ማስረጃ ነው፡፡ መለስ ደግ ነገርን እንደሚያደርጉት አማልዕክት (እንደ ግሪክ የባህር እና የወንዞች አማልዕክት) የዓባይን ወንዝ ስለመገደብ ራዕይው ይናገር ነበር፡፡ እራሱን ፍጹም ለሆነ ታላቅ እራስ አገዝ እና ለሌሎች ህዝቦች ወሰን የሌለው ደግ ነገርን እንደሚሰራ አድርጎ ይቆጥር ነበር፡፡ ለእርሱ የግድቡ መሰራት በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህዝቦች ከድህነት አረንቋ እና ከተፈጥሮ አደጋ ይገላገላሉ ብሎ ያስብ ነበር፡፡ የግድቡ መሰራት በወንዙ ግራ እና ቀኝ ዳርቻ እና በአካባቢው ያሉ ማህበረሰቦች እና በሱዳን የሚገኙ ህዝቦች ደህንነታቸው ዘለቄታዊ በሆነ መልኩ ከጎርፍ አደጋ ይጠበቃል የሚል እምነትን ያራምድ ነበር፡፡ ግድቡ የሚገነባው የኤሌክትሪክ ኃይልን በሀገር ውስጥ በማምረት ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅማችንን ከፍ ለማድረግ እና የኃይል ፍላጎታችንን ለማርካት ብቻ አይደለም፣ ሆኖም ግን ኃይልን ወደ ጎረቤት ሀገሮች እንዲወጣ በማድረግ እነርሱንም ከድህነት እና ከመከራ ለማላቀቅ ጭምር በማሰብ ነው በማለት ይደሰኩር ነበር፡፡ በተከታታይነት እና ማቋረጫ በሌለው መልኩ ግድቡ ሁሉንም የጎረቤት ሀገሮች በተለይም የታችኛው የዓባይ ተፋሰስ የሆኑትን የሱዳንን እና የግብጽን ሀገሮች ተጠቃሚ ያደርጋል በሚለው ንግግሩ ላይ ያሰምርበት ነበር፡፡

በግድቡ ምክንያት ምንም ዓይነት የአካባቢ ስነምህዳር ችግር እንደሌለ እና አስተማማኝ የሆነ ጥናት ተደርጎበት ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴው እንደተገባ እና ከዘመኑ ጋር የተገናኘ የቴክኖሎጂ ስራዎች እንደሚካተቱ በሰላ አንደበት በተደጋጋሚ ይናገር ነበር፡፡ የሱዳንን እና የግብጽን ግድቦች በተደጋጋሚ ጊዜ እንደሚያጠቃው ደለል እና ዝቃጭ ዓይነት ችግር በሚሊኒየሙ ግድብ እንደማይኖር እና ልዩ በሆነ ጥንቃቄ እንደሚገነባ ይናገር ነበር፡፡ እንደዚሁም ደግሞ ግድቡ በአፍሪካ የቴክኖሎጂ ውስብስብነት እና ምጥቀት የሚታይበት ይሆናል ይል ነበር፡፡ ግድቡ በውኃ ትነት የሚባክነውን የውኃ መጠን በመቀነስ ያለውን የውኃ ሀብት አቅርቦት እንዲጨምር እና በዓባይ ወንዝ ላይ ዓመቱን ሙሉ የተስተካከለ እና የተመጣጠነ የውኃ ፍሰት እንዲኖር ያደርጋል ይል ነበር፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ግድቡ በኢትዮጵያ፣ በሱዳን እና በግብጽ መካከል በዓባይ ወንዝ ላይ ፍትሀዊ የሆነ የውኃ አጠቃቀም እንዲኖራቸው ያስችላል ይል ነበር፡፡

ሆኖም ግን ሲያደርጋቸው በነበሩት ንግግሮቹ ላይ ድብቅ ሆኖ የቆየው እና በጥቂት የዜና ትንታኔ አቅራቢዎች እና በደቀመዝሙሮቹ ብቻ የሚታወቀው የሚሊኒየሙ ግድብ በገንዘብ ፍሰት እጥረት ምክንያት ሳይገደብ ተገትሮ ሊቀር እንደሚችል የነበረው የራዕዩ ግልጽነት ያለመታወቁ ጉዳይ ላይ ነው፡፡ የመለስ እርኩስ መንፈስ ከበሮ ሲደለቅለት የነበረው ግድብ ከፍተኛ በሆነ የገንዘብ ፍሰት ካልታገዘ ሊቆም እንደሚችል ካለመገንዘቡ ላይ ነው፡፡

ግድቡ በአግባቡ ከተያዘ እና ሱዳን እና ግብጽም በገንዘብ መዋጮው በኩል እንዲሳተፉ እና ተቃሚ እንዲሆኑ ተደርጎ የግንባታ ስራው ቢጀመር ግንባታው ሊጠናቀቅ እንደሚችል መለስ አሳምሮ ያውቀው ነበር፡፡ ቀጥታ በሆነ መልኩ የገንዘብ መዋጮ እና ድርሻ ሳይኖራቸው የግንባታ ስራው ቢካሄድ የሰጠው ውሳኔ በመጨረሻው ሰዓት አንድም የግድቡን ፕሮጀክት እርግፍ አድርጎ መተው ወይም ደግሞመዋጣት ያለበትን ገንዘብ ማሰባሰብየግድ እንደሆነ መለስከጥርጣሬ በላይ በሚገባ ያውቀው ነበር፡፡

በአሁኑ ጊዜ የመለስ ደቀመዝሙሮች ለግድቡ ግንባታ አስፈላጊ የሆነውን ገንዘብ ለማሰባሰብ ጥረት በማድረግ ላይ ሲሆኑ የታኢሕግ/GERD መጠነ ሰፊ የሆነ የገንዘብ ችግር ምናልባትም ወደ 3 ቢሊዮን አካባቢ ዶላር የሚያስፈልገው ለመሆኑ ጥያቄ የሚያስነሳ ጉዳይ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን ባለራዕዩ መሪ እየተባለ የሚጠራው መለስ ይኸ ሁሉ ችግር ሊመጣ እንደሚችል አስቀድሞ አውቆት ነበር፡፡ አስቀድሞ የኢትዮጵያን ጥገት ላሞች ማለትም ባንኮችን፣ የቢዝነስ ሰዎችን እና በአጠቃላይ ተራውን ህዝብ ጥሩ አድርጎ አንጠፍጥፎ ካለበ በኋላ ሌላ አዲስ የምትታለብ ላም ያገኝ እንደነበር ያውቃል፡፡ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጉባ በተባለው ቦታ ላይ ባደረገው ንግግር አዲሶቹ የሚታለቡት ላሞች እንዴት ሊገኙ እንደሚችሉ እንዲህ በማለት ግልጽ አድርጎ ነበር፡

“የሚሊኒየሙ ግድብ ጥቅም የሚሰጠው ለኢትዮጵያ ብቻ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን ለሱዳን እና ለግብጽም ተጨማሪ የጋራ የተጠቃሚነት ዕድሎችን ይሰጣል፡፡ በእርግጥ ማንም ሰው እንደሚያስበው እነዚህ ሀገሮች ከግድቡ ግንባታ ጋር በተያያዘ መልኩ ሊከሰት የሚችለውን ወጭ እያንዳንዱ ሀገር እንደሚያገኘው ጥቅም እንደየመጠኑ መካፈል እንዲችሉ ዝግጅት ማድረግ አለባቸው እንደሚል ይጠበቃል፡፡ በዚህ ስሌት መሰረት ሱዳን 30 በመቶ እና ግብጽ ደግሞ 20 በመቶ የሚሆነውን ጠቅላላ የፕሮክቱን የግንባታ ወጭ መሸፈን አለባቸው፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ፍትሀዊ እና ገንቢ የሆነ ግላዊ የሆነ ፍላጎትን መሰረት ባደረገ መልኩ ዝግጅትን ያካተተ አስፈላጊ የሆነው የተሳትፎው ከባቢ አየር በአሁኑ ጊዜ የለም፡፡ በእርግጥ በአሁኑ ጊዜ ያለው አጠቃላይ ሁኔታ ኢትዮጵያ ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ የሚሆነውን ገንዘብ ለማግኘት የምታደርጋቸውን ጥረቶች ሁሉ እየተከታተሉ ማምከን ነው፡፡ በእርግጥ ጠቅላላ የፕሮጀክቱን ወጭ ለመሸፈን ከእራሳችን የሀገር ውስጥ የቁጠባ መዋዕለ ንዋይ ላይ ብቻ መሰረት እንድናደርግ ተገደናል፡፡”

የትብብር ጊዜው በእጅ ላይ ነውን?

ባለፈው ሳምንት የዓባይ/ናይል ተፋሰስ ሀገሮች የውኃ አጠቃቀም ስምምነት በሚል ጋዜጣዊ መግለጫ ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ የመርሆዎች ድንጋጌን (ዴክላሬሽን) የተፈራረሙ መሆናቸው ይፋ ተደርጓል፡፡

መርሆዎቹ ዓላማ አድርገው የተነሱት በተደራዳሪ ሀገሮች መካከል የጋራ መግባባት እንዲኖር፣ መተማመን እና ልማት እንዲዳብር፣ አስከፊ የሆነው የአካባቢ ስነምህዳር ጉዳት እንዲወገድ፣ ፍትሀዊ እና ተገቢ የሆነ የውኃ አጠቃቀም ስርዓት እንዲዘረጋ፣ እርስ በእርስ መተማመን እንዲዳብር እና የጋራ መረጃ የመለዋወጥ ስርዓት እንዲጠናከር፣ የግድቡ ደህንነት እንዲጠበቅ፣ ሉዓላዊነት በጽኑ መሰረት ላይ እንዲጣል፣ ትብብር እና የግዛት አንድነት እንዲጠናከር እንዲሁም የሚከሰቱ ውዝግቦች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ለማስቻል በሚሉ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ያደረጉ ናቸው፡፡

ባለፈው ሳምንት ባቀረብኩት ትችቴ ላይ ስለስምምነት ድንጋጌው በርካታ የሆኑ የመግቢያ ጥያቄዎችን ለማንሳት ሞክሪያለሁ፡፡

በዚህ በአሁኑ ትችቴ ላይ ደግሞ የእርሱን መርህ በመከተል እየተጓዙ ላሉት ለመለስ ደቀመዝሙሮቹ በድንጋጌው ጉዳይ ላይ ትኩረት በማድረግ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ላቀርብላቸው እወዳለሁ፡

1ኛ) እ.ኤ.አ ሚያዝያ 2/2011 መለስ ግድቡ በሚገኝበት ጉባ ተብሎ በሚጠራው ቦታ ላይ በመገኘት ያደረገውን ዲስኩር አንብበው እና ምን እንደሚል በውል አጢነውታልን?

2ኛ) ዲስኩሩን አንብበውት እና አጢነውት ከሆነ የእርሱን የፖሊሲ ስልታዊ ይዘት/policy strategic content በውል ተገንዝበውታልን?

3ኛ) በዚያን ጊዜ ያደረገውን ንግግር አንብበውት እና ተገንዝበውት ከሆነ በቀንና ሌሊት ስለግድቡ ከመዘመር እና ባዶ ዲስኩር ከማቅረብ ባለፈ በዚያ ንግግር ላይ የተቀመጡትን ትዕዛዞች በትዕዛዙ መሰረት ለመፈጸም የማይንቀሳቀሱት እና ሲተጉ የማይታዩት ለምንድን ነው?

4ኛ) ያንን ንግግር ያላነበቡት እና በውል ያላጤኑት ከሆነ ያለማንበባቸው እና በውል ለማጤን ሙከራ ያለማድረጋቸው ምክንያቱ ምንድን ነው?

5) የመለስ ደቀመዝሙሮች በዚያ ንግግሩ ላይ የተቀመጡትን ትዕዛዞቹን ተግባራዊ የማያደርጓቸውስ ለምንድን ነው?

በጉባ ላይ በተደረገው ንግግር መለስ አስፈላጊ የሆነው የተሳትፎ ከባቢ አየር ሲሟላ ሱዳን 30 በመቶ እና ግብጽ ደግሞ 20 በመቶ የሚሆነውን የጠቅላላውን የፕሮጀክት ግድቡን የግንባታ ወጭ ይሸፍናሉ ብሎ ነበር፡፡ ይኸ ድንጋጌ በባለራዕዩ መሪ ቀደም ሲልየተነገረውን የተሳትፎ ከባቢአየርመሟላቱን እና መድረሱን ያመላክታልን?

ድንጋጌው በሚፈረምበት ጊዜ የግብጹ ፕሬዚዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ለልማት እና አንዳችን በአንዳችን ላይ የመተማመን ስሜት እንዲኖር በማሰብ ትብብርን መርጠናል…ለዘመናት በውዝግብ እና በጥርጣሬ ዓይን በመተያየት እስከ አሁን ድረስ ኖረናል፣ አሁን ግን በመተባበር እና በመተማመን መኖር መጀመር አለብን፡፡“ (እውነት ለመናገር ስለዓባይ ውኃ አጠቃቀም ጉዳይ የግብጽ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሕግ አማካሪ የሆኑት አይማን ሰላማ ስለግብጽ ድንጋጌ ያላቸው ህጋዊ ራዕይ ከዚህ ለየት ያለ ነው፡፡ በአጭሩ ሀሳባቸው እንዲህ በሚሉ ዓረፍተ ነገሮች ተከሽኖ ይገኛል፣ “ለቀጣዩ የግድቡ ምዕራፍ አስፈላጊ የሆኑትን ዝርዝር ጉዳዮች አጥንቶ ለማጸደቅ የሚደረጉት ስምምነቶች እጅግ በጣም አስቸጋሪ የሆኑ እና የግብጽ ተደራዳሪ ወገን በተቻለ መጠን ግብጽ አትራፊ እና ተጠቃሚ የምትሆንበትን መንገድ ለዘለቄታው ሊያሳካ የሚችል መሆን አለበትማለትም የግብጽን በዓባይ ወንዝ ላይየመጠቀም ታሪካዊመብቶችን የሚያስጠብቅ መሆን አለበት፡፡“) (አጽንኦ ተጨምሮበታል፡፡) ኃይለማርያም ስለመለስ አህጉራዊ ጠበቃነት እና ደግ አድራጊነት ራዕይ የፕሬስ መግለጫ ሰጥቶ ነበር፡፡ ሆኖም ግን የመለስን ዋናውን እና እንዲህ የሚለውን አስፈላጊ የሆነውን መልዕክት ዘሎታል፡ “ሱዳን እና ግብጽ 30/20 የሚለውን ጠቅላላ የግንባታ ፕሮጀክቱን ወጭ መሸፈን አለባቸው፡፡“

ኃይለማርያም የእርሱን “ዘላለማዊ ኃያል መሪ” እያለ የሚጠራውን ለግድቡ የግንባታ ሂደት ስኬታማነት ወሳኝ የሆነውን የመለስን ትዕዛዝ የዘለለው ለምንድን ነው?

በባለራዕዩ መሪ ቀደም ሲል የተነገረው አስፈላጊ የሆነው የተሳትፎ ከባቢ አየር ኃይለማርያም ድንጋጌውን በሚፈርምበት ጊዜ ያልደረሰ እና ያልተሟላ ከሆነ ለመሆኑ ያ ዕለት የሚመጣው እና ተግባራዊ የሚደረገው መቼ ነው? አጠቃላይ የግድቡን የግንባታ ፕሮጀክት ወጭ 30/20 የሚሆነውን ሱዳን እና ግብጽ እንዲሸፍኑ ሳይደረግ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴው መገባቱ አጠቃላይ በሆነ መልኩ የታኢሕግ/GERD አፈጻጸም የተሟላ፣ ቀጣይነት እና ዘላቂነት ያለው እንዲሁም ህይወት ያለው እና ትርፋማ ይሆናል ብሎ ማሰብ እና መተንበይ ይቻላልን?

በአስቸጋሪው በረከት ስምኦን ስር ሆኖ ሲያገለግል የነበረው እና በአሁኑ ጊዜ በስደት ላይ የሚገኘው የቀድሞው የኮሙኒኬሽን ሚኒስትር ዴዔታ ኤርሚያስ ለገሰ እንዳቀረቡት ዘገባ ከሆነ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከዚህ ድንጋጌ መፈረም ጋር በተያያዘ መልኩ በተደራዳሪ ሀገሮች መካከል መተማመን እንዲኖር፣ ልማት እንዲፋጠን፣ በሁሉም ዘንድ ትብብር እንዲኖር፣ ወዘተ የሚለው ፋይዳ በጣም አናሳ እንደሆነ ግልጽ አድርገዋል፡፡ ሆኖም ግን ይህ ስምምነት በዋናነት እንዲያገለግል የተፈለገው ከሕዝቦች ፍላጎት ውጭ በአሁኑ ጊዜ በስልጣን ላይ ተፈናጥጦ የሚገኘው አምባገነን የዘራፊ አገዛዝ የሞት ሽረት ትግል በማድረግ የስልጣን እድሜውን ለማራዘም ነው፡፡ የድንጋጌው ዓላማ በተቻለ መጠን የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብን የስልጣን እድሜ በተወሰነች ጊዜም ቢሆን ለማራዘም እንዲቻል ታስቦ ነው፡፡ የዚህ ስምምነት ዋናው ዓላማም የእራሳቸውን የቢዝነስ ግዛት በመፍጠር እስከ አሁን ድረስ ምንም ዓይነት ኦዲተር የማያውቀውን እና የኢትዮጵያን አብዛኛውን የምጣኔ ሀብት ተቆጣጥሮ የሚገኘውን የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራሮች የግል የቢዝነስ ተቋም የሆነውን እና ማህበረ ረድዔት ትግራይ (ማረት)/Endowment Fund for Rehabilitation of Tigray (EFFORT) እየተባለ የሚጠራውን ዘራፊ ተቋም ለማበልጸግ ነው፡፡ እውነት ነው ለወያኔ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራሮች ማረት ማለት ረድዔት (ትሩፋት፣ በረከት፣ ጸጋን ማግኘት፣ በሀብት መንበሽበሽ) ነው ለብዙሀኑ ለኢትዮጵያውያን/ት ግን ክስረት እና መቀመቅ እየወረደ ያለ ህይወት ተምሳሌት ነው፡፡

የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የስምምነት ድንጋጌውን የፈረመበት ዋናው ምክንያት ግብጽ በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ተፈናጥጦ የሚገኘውን አገዛዝ በትጥቅ ትግል ለማንበርከክ እና ለማስወገድ ለሚፋለሙ ኃይሎች ድጋፍ እንዳትሰጥ ለማድረግ፣ ግብጽ ለኤርትራ የገንዘብ ድጋፍ እንዳትሰጥ ለማባበል፣ ከግድብ ግንባታው ጋር በተያያዘ መልኩ ከዓለም አቀፍ ለጋሽ እና አበዳሪ ድርጅቶች የሚደረገውን ጫና ለማለሳለስ እና ለማስቆም እንደዚህም ደግሞ ስምምነቱን የልመና አኩፋዳ በማድረግ በርካታ የሆነ እርዳታ እና ብድር ለማግኘት ሲባል ነው በማለት ኤርሚያስ የክርክር ጭብጣቸውን አቅርበዋል፡፡ ኤርሚያስ በአሁኑ ጊዜ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከታኢሕግ/GERD በተያያዘ መልኩ ከፍተኛ በሆነ የገንዘብ ችግር ተጠፍንገው እንደሚገኙ እና እንዲያውም በግምት ከ3 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማግኘት እንደሚያስፈልጋቸው ሀሳባቸውን ገልጸዋል፡፡ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በእውቀት እና በመረጃ ላይ በመመስረት ሳይሆን በስሜታዊነት እና በተራ የካድሬ አስተሳሰብ ያለምንም በቂ ጥናት የጀመሯቸውን በርካታ ፕሮጀክቶች ለማስፈጸም የሚያስችል የገንዘብ አቅም የላቸውም፡፡ ከዚህም በላይ የበለጠ አስደንጋጩ እና አሳሳቢው ጉዳይ ደግሞ በአሁኑ ጊዜ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ እጅግ በጣም ትንሽ የሆነ የውጭ ምንዛሬ ክምችት ብቻ ያለው የመሆኑ ጉዳይ ነው፡፡ (እንደ የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት/International Monetory Fund እ.ኤ.አ ሰኔ 2014 ላይ እንዳወጣው ዘገባ ከሆነ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ ለሚገቡ እቃዎች እና አገልግሎቶች የሚሆን ጠቅላላ የውጭ ምንዛሬ ክምችቱ ከ3 ወራት በላይ የማያቆይ መሆኑን ይፋ አድርጓል፡፡)

ኤርሚያስ ታኢሕግ/GERD እየተባለ ሌት ቀን የሚደሰኮርለት ፕሮጀክት የተቋቋመበት ዋናው ምክንያት የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የግል ሀብት የሆነውን እና አስከ አሁን ድረስ ምንም ዓይነት ኦዲተር ጎብኝቶት የማያውቀውን ማረትን/EFFORTን እና ደጋፊዎቻቸውን ለማበልጸግ ነው በማለት አሳማኝ የሆነ የክርክር ጭብጣቸውን ያቀርባሉ፡፡ እርግጥ ነው ታኢሕግ/GERD ገና ከአጀማመሩ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብን እና ማረት/EFFORT እተባለ የሚጠራውን ኦዲተር የማያውወቀውን የእራሱን የቢዝነስ ድርጅት ለማበልጸግ ሲባል የተገኘ ንፋስ አመጣሽ እና እንደ መና ከሰማይ የወረደ ሆኖም ግን በፖለቲካዊ ቀመር የተሰራ ሸፍጥ ለመሆኑ ጥያቄ የሚያስነሳ ጉዳይ አይደለም፡፡ ለግድቡ የግንባታ ስራ የሚያገለግሉት ግብዓቶች ማለትም ስሚንቶ፣ ብረት፣ ጣውላ – እንደ ትራንስፖርት እና የሎጅስቲክ አገልግሎቶች ሁሉ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ከማረት/EFFORT ጋር የተቆራኙ ሆነው ይገኛሉ፡፡ ታኢሕግ/GERD በታለመው እና በታሰበው መንገድ የሚሄድ ቢሆን ኖሮ ለማረት/EFFORT ከፍተኛ የሆነ የገንዘብ መዝረፊያ መድረክ ይሆን ነበር፡፡ ሆኖም ግን ታኢሕግ/GERD በአሁኑ ጊዜ ከፍተኛ በሆነ የገንዝብ እጦት ቀውስ ውስጥ ወድቆ በመንፈራገጥ ላይ ይገኛል፡፡ ማረት/EFFORT እንደ ካሩቱሪ ገንዘቡን አውጥቶ ብር ብሎ መጥፋት የተሻለ ምርጫው ነው!

የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከገንዘብ፣ ከውሸት፣ ከጊዜ እና ከዕድል ውጭ ግድቡን ገድቡት፣ የመለስን ትዕዛዝ ለመተግበርሞክሩ፣

ስለታኢሕግ/GERD የመለስን ሰይጣናዊ ትንበያ በማንጸባረቅ ሀሳቤን እደመድማለሁ፡፡ በሱዳን እና በግብጽ የ30/20 አጠቃላይ የግድብ ፕሮጀክት ወጭ መጋራት ስሌት እና ትግበራ ውጭ ምንም ዓይነት ታኢሕግ/GERD የሚባል ነገር አይኖርም፡፡ አሉ ከተባለ አሁን በህይወት ከሌለው ከመለስ ጋር ጥቂት የምስማማባቸው ነገሮች አሉ፡፡ እ.ኤ.አ በ2005 የተደረገውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ ተከስቶ በነበረው ውዝግብ በቁጥር 193 የሆኑ መሳሪያ ያልታጠቁ ሰላማዊ ወገኖቻችንን በጥይት እያስደበደበ ካስከጨረሰበት እና ወደ 800 በሚሆኑት ላይ ደግሞ አስከፊ የሆነ የአካል ጉዳት ካስደረሰበት እኩይ ምግባር ጋር በአጠቃላይ እና ፍጹም በሆነ መልኩ ከመለስ ጋር አልስማማም፡፡ በጣም ከፍተኛ ስፋት ያለውን የሀገራችንን ሉዓላዊ ግዛት የሆነውን መሬታችንን በማን አለብኝነት እና በእብሪት በመነሳት ቆርሶ ለሱዳን መንግስት በሚስጥር ከሰጠው የከሃዲነት ባህሪ ጋር በፍጹም አልስማማም፡፡ ብርቱካን ሚደቅሳን፣ ታላቁን ጓደኛዬን እስክንድር ነጋን፣ ከማንም ጋር ለውድድር የማትቀርበውን ጀግናይቱን ርዕዮት ዓለሙን እና መንፈሰ ጠንካራውን እና ደፋሩን ዉብሸት ታዬን እንዲሁም ሌሎችን በርካታዎቹን ወጣት የኢትዮጵያ አርበኛ ጋዜጠኞችን እና ጦማሪያንን ካሰረበት ሰይጣናዊ ባህሪው ጋር በፍጹም አልስማማም፡፡ በአጠቃላይ መልኩ ከመለስ ጋር በፍጹም አልስማምም፡፡

የረዥም ጊዜ አንባቢ ደንበኞቼን ሊያስደንቅ በሚችል መልኩ እንደጣና ሐይቅ ዓሳ በ360 ዲግሪ ተገለባብጨ ሱዳን እና ግብጽ በአጠቃላይ ለግድብ ፕሮጀክቱ የተመደበውን ወጭን ሱዳንና ግብፅ 30/20 በመሸፈን ኢትዮጵያ 50 በመቶዉን ብያዋጡና በጋራ ግደቡን ለመስራት ቢተባበሩ ግድቡን ግብ ሊያደርሱት ይችላሉ የሚለው የመለስ አባባል ትክክለኛ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡

የብዙሀን ሀገሮች ተባብረው የግድብ ግንባታዎች ተገንብተው ያለምንም ችግር አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ አርጀንቲና፣ ፓራጓይ እና ኡራጓይ ታላቁን የሳልቶን ግድብ በጋራ ገንብተው ሀገራዊ ጥቅምን ከሚሰጡ ድርጅቶች የጋራ የሆነ ጥቅም በማግኘት በፍቅር እና በመተባበር ላይ የተመሰረተ ዲፕሎማሲን በማራመድ በሰላም ይኖራሉ፡፡ በዓመታዊ የኤሌክትሪክ ማመንጨት አቅሙ ከዓለም በ2ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው የኢታይፑ ግድብ የተገነባው በፓራጓይ እና በብራዚል ሀገሮች የጋራ ትብብር ነው፡፡ ሌሎችም ምሳሌዎቸን ማቅረብ ይቻላል፡፡ ሊሰራ ይችላል፡፡ እነዚህ እርባና የሌላቸው የመለስ ደቀመዝሙሮች ይህንን ድርጊት ይፈጽማሉ ለማለት ጥርጣሬው አለኝ፡፡ መለስ ቢኖር ኖሮ ይፈጽመዋል የሚል ግምት አለኝ ምክንያቱም ቢያንስ አምባገነንነቱ እና ዘራፊነቱ እንዳለ ሆኖ ለሚያደርገው ነገር እምነቱ እና ድፍረቱ ነበረው፡፡ አሁንማ ማንስ ሊያዝዝ ማንስ ፈጻሚ ሊሆን!? በመለስ ላይ አስከፊ የሆነ ግድፈት ነበር፡፡ ያንን የመሰለ አጋጣሚ ለመጠቀም ያንን የመሰለ አጋጣሚ ማጣት አልነበረበትም! እኔ በታኢሐግ/GERD ግንባታ ላይ ተቃውሞ እንዳለኝ የምታምኑ ወገኖቼ ሁሉ በቀጣይ ጊዜ በአዲስ መልክ ሁሉንም ተዋንያን ሀገሮች ባሳተፈ መልኩ ታኢሕግ/GERDን እንደ አገባቡ (ሱዳን፣ ግብጽ እና ኢትዮጵያ) በ30/20/50 ወጭ እና ጥቅም እያወጡ እና እያገኙ እንዲገድቡት እና በጋራ በሰላም እንዲጠቀሙ የሚል ሀሳብን አቀርባለሁ!

ለእኔ ዓባይ ለኢትዮጵያ፣ ለሱዳን እና ለግብጽ የህይወት ምንጭ ነው፡፡ የሶስቱ ሀገሮች ዕጣፈንታ በዓባይ ወንዝ ዘላለማዊ በሆነ መልኩ ተሳስሮ እና ተገምዶ ይገኛል፡፡

በአፍሪካ ህብረት ላይ አምናለሁ፡፡ በአህጉራዊ አንድነት ላይ አምናለሁ፡፡ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ አምናለሁ፡፡ ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ በአባይ ወንዝ አካባቢ የሚያከማቹትን ወታደራዊ ኃይል እና መሳሪያ እንዲሁም በየጊዜው የሚያንዣብበውን ጥላሸት የመቀባባት ፕሮፓጋንዳ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ በማስወገድ አፍሪካን የዳቦ ቅርጫት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በጨለማው አህጉር የብርሀን መስጫ መቅረዝ ሆነው መገኘት ይኖርባቸዋል፡፡ ሶስቱ ሀገሮች በዓባይ ምክንያት ከሚፈጠረው መንፈስ አንጻር አንድ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡

መለስ በበርካታ ነገሮች ላይ ስህተት የሚሰራ ሰው እንደነበር አምናለሁ፣ ለእኔ ቆጥሮ ለመጨረስ የሚያዳግቱ እጅግ ብዙ፡፡ ሆኖም ግን መለስ በታኢሕግ/GERD ላይ ትክክል ነበር፡፡ መለስ እንዲህ በማለት ሁለት አማራጮች ብቻ አሉ ብሎ ነበር፣ “ግድቡን መገንባት ወይም ደግሞ እርገፍ አድርጎ መተው“፡፡ እንዲህ ብሎ ነበር፣ “30/20 ጠቅላላ የግድቡ የፕሮጀክት ወጭ በሱዳን እና በግብጽ የሚሸፈን ከሆነ“ ብቻ እና ብቻ ግድቡን መገንባት ይቻላል፡፡ መለስ ትክክል ነበር!

በአሁኑ ጊዜ እ.ኤ.አ 2015 ውስጥ ነን፡፡ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ገንዘብ የማሰባሰብ የሸፍጥ ተግባራት ሁሉም ፍጹም በሆነ መልኩ መክነዋል፡፡ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከገንዘብ፣ ከውሸት፣ ከጊዜ እና ከመልካም ዕድል ውጭ ሆነዋል፡፡

ስለሆነም ለኃይለማርያም እና ለወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከፋይ አለቆቹ ስለ 4 ቢሊዮን ዶላር የማቀርበውን ጥያቄ እነሆ፡አንዱንግልጽየሆነውን እናየኃያሉ ዘላለማዊ መሪያችሁ ትዕዛዝ የነበረውን 30/20 የአጠቃላይ የግድቡን ወጭ ሱዳን እና ግብጽእንዲሸፍኑት ሆኖየሚገነባውንግድብ ትታችሁ ለምን የሚገድብ ግድብን ለመገንባት እና የዘላለም ንትርክ እና ጦርነት ድግስንየሚደግስ ግድብ ለመፍጠርትውተረተራላችሁ?

ስለ 30/20 የሚደረገው ስምምነት መቼ ነው አስፈላጊ የሆነው ከባቢ አየር የሚመጣው?

በምንም ዓይነት ሁኔታ በማንኛውም ነገር ላይ ከመለስ ጋር የምስማማበት ሁኔታ ይኖራል የሚል ሀሳብ ወይም ደግሞ ከእርሱ ጋር ስምምነት ሊኖረኝ ቢችል እንኳ በሕዝብ ፊት በአደባባይ አምኘ እቀርባለሁ የሚል እምነት አልነበረኝም!

ሁሉንም ነገር እንዳየሁት ለመጥራት የምሞክር ሰው ነኝ፡፡ ሁልጊዜ ነገሮችን ከምንም በላይ በጸዳ ፍትሀዊ በሆነ መልኩ ለማየት እና ትክክል ሲሆንም ትክክል እንደዚሁም ደግሞ ስህተት ሲሆንም ስህተት ነው የሚል እምነትን የማራምድ ሰው ነኝ፡፡ እውነታው ግን መለስ20/30/50በማለትስለታኢሕግ/GERD አስቀምጦት ያለፈው ትዕዛዝ በእኔ እምነት ትክክል ነው! የዚያን ያህል ቀላል ነገር ነው!

የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራሮችን የመለስን የታኢሕግ/GERD ትዕዛዝ ተከተሉ እላቸዋለሁ!

ሕዝብን ማደናገርያ ግድብ? አቦስለምርጫው ብን ነጋገርስ?

የዚህ የግድብ ነገር ላለፉት ጥቂት ሳምንታት የሕዝብን ቀልብ የማስቀየሻ ስልት በመሆን እርባናቢስ ደንቃራ ሆኖ ቆይቷል፡፡ በዚህ በግድቡ ዙሪያ ላይ ከፍተኛ የሆነ የምሁራን ክርክር እና ውይይት ሲካሄድ ቆይቷል፡፡ ይበቃል!

ልንነጋገርባቸው እና ልንወያይባቸው የሚገቡ በርካታ ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ያህልም ስለ”ምርጫው”፡፡ የምን ምርጫ!? ታውቁታላችሁ፡፡ እ.ኤ.አ ግንቦት 24/2015 የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በ99.9 በመቶ ያሸነፈውን ምርጫ ነዋ!! ታድያ ምናለ አሸናፊዎቹን “አንክዋን ደስ አላችሁ ብንላቸው!

እያንዳንዱ ሀገር ሊያገኝ ከሚችለው ጥቅም አንጻር የዋጋ ምጣኔ ስሌት እየተሰራ እነዚህ ሀገሮች ወጭውን በጋራ መሸፈንእንዳለባቸው ማንምሊገምትይችላል፡፡ በዚህ ስሌት መሰረት ሱዳን 30 በመቶ እና ግብጽ ደግሞ 20 በመቶ የጠቅላላ የግድቡንየፕሮጀክት ወጭ ይሸፍናሉ፡፡ እንዳጋጣሚሆኖ በአሁኑጊዜ ፍትሀዊ እና ገንቢ በሆነ መልኩ የእያንዳንዱን ሀገር ጥቅም ሊያስከብርከሚችለው አስፈላጊ ከሆነው የተሳትፎ ከባቢ አየር ላይአልተደረሰም፡፡

መለስ ዜናዊ ሚያዚያ 2/2011

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

መጋቢት 29 ቀን 2007 .

Filed in: Amharic