>

የ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ››ትግል የሁላችንም ነውና በጋራ እንነሳ![ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ መግለጫ]

ነገረ ኢትዮጵከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ መግለጫ

ትብብራችን ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› በሚል መርህ የሠላማዊ ትግል ፕሮግራም ካደረገው እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ የተከሰቱትን ወቅታዊ ሁኔታዎች በመገምገም ሁለተኛ ዙር ፕሮግራሙን ነድፎ ለምርጫ ዕጩዎችን የማስመዝገብ ተግባር ጎን ለጎን ለተግባራዊነቱ በዝግጅት ላይ እንገኛለን፡፡ የዚህ የሁለተኛ ዙር ፕሮግራም ማጠቃለያም የካቲት 15 /2007 በተመረጡ 15 የአገራችን ከተሞች በተመሳሳይ ጊዜ የሚደረጉ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፎች መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከዚህ በመነሳት የዛሬው መግለጫ ለየካቲት 15 የታቀደውን በ15 ከተሞች የሚደረግ ሰላማዊ ሰልፍ ፕሮግራም በአንድ ሳምንት ተራዝሞ ወደ የካቲት 22/07 መተላለፉን ለማሳወቅና ትብብራችን እስከ ዛሬ ያደረገውን ሰላማዊ ትግል አስፈላጊነት፣ወቅታዊነትና ትክክለኝነት በተጨባጭ በማረጋገጥ፣የተያያዝነውን ሰላማዊና ህዝባዊ ትግል እንዴት ማስቀጠልና ውጤታማ ማድረግ ስለሚቻልበት የገዢዎቻችንን ከግምት ያለፈ የፍርኃትና ስጋት ደረጃን ያገናዘበ ስልት መቀየሳችንን ፣ የቆምንበትን ህገመንግስታዊነትና ህጋዊነት እንዲሁም የትግሉን ትኩረት የሚመለከቱ መሰረታዊ ጉዳዮች ላይ የደረስንበትን ጭብጥ ለህዝባችን በዝርዝርና በስፋት በማቅረብ ለቀጣዩ ትግል ጥሪያችንን ለማቅረብ ነው፡፡

በዚሁ መሰረት የተደረሰባቸው ጭብጦች፡-
1.ገዢው ፓርቲ/መንግስት የቱንም ያህል አሰቃቂና አረመኔያዊ የአፈና እርምጃዎች ቢወስድ የህዝብ ጥያቄዎች እስካልተመለሱ ድረስ ህዝባዊ ትግሉን ማዳፈን እንጂ ማስቆም እንደማይችል ይልቁንም ተጠናክሮ በረቀቀ ስልት እንደሚቀጥል የሙስሊም ማኅበረሰቡ ታህሳስ 10/07 ዓ.ም በኑር መስጂድ፣ የካቲት 06/07 በአንዋር ካሰማውና የትግሉን ቀጣይነት ካረጋገጠበት ፍጹም ሠላማዊ በሆነና አንድም ጉዳት ባልደረሰበት የተሳካ የተቃውሞ ድምጽና ክንዋኔ ተረድተናል፤

2. በታህሳስ 10/2007 ዓ.ም ተመሳሳይ ዕለት የባህር ዳር ከተማ ህዝብ ሃይማኖት፣ ዘርና ሌሎች ልዩነቶችን ወደጎን አድርጎ ፣ገዢው ፓርቲ በዘረጋው የአንድ ለአምስት የደህንነት መዋቅር ሳይጠለፍና ሳይገታ፣ በአንድነት ያሳየው ህዝባዊ እምቢተኝነትም አፈና የቱንም የህዝብ ጥያቄ የማፈን አቅም የሌለው መሆኑን ይልቁንም ትግሉን ወደ ግብታዊነት ሊመራ እንደሚችል ተገንዝበናል፤

3. ገዢው ፓርቲ/መንግስት በመንግስት መዋቅሮችም ሆነ በህዝቡ ማኅበራዊ ግንኙነት እያደረሰ ያለው ጭቆና/የመብት ረገጣው፣ሙስና፣ የመልካም አስተዳደር እጦት…/ እና ከህዝብ የመሸከም አቅም በላይ የሆነው የኑሮ ውድነት፣የመከፋፈልና የጥላቻ ፖለቲካ … የህዝቡን የለውጥ ፍላጎትና የትግል ተነሳሽነት እያሳደገው መምጣቱን ፣የተባበረና የተቀናጀ አመራር ካገኘ ህዝቡ ለለውጥ ያለውን ጥማትና ዝግጁነት አስገንዝቦናል፤

እነዚህ ሲጠቃለሉም-ገዢው ፓርቲ/መንግስት ስለመድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ከቃላት ያለፈ እምነትም ሆነ ቁርጠኝነት የሌለው በመሆኑ ለዚህ የተቋቋመውን የዲሞክራሲ ተቋም -የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በቁጥጥሩ ሥር በማዋል በጠንካራ ፓርቲዎች የውስጥ ጉዳይ በማስገባት ከመጪው ምርጫ ለማግለል ቆርጦ መነሳቱን ፣ ለዚህም አንድነትና መኢአድ ፓርቲዎችን በሚመለከት በቦርዱ የተላለፈው ፖለቲካዊ ውሳኔና ፍጻሜው ፍንትው አድርጎ ያሳያል፡፡ በተጨማሪም ለቀጣዩ ምርጫ ዕጩዎችን ለማስመዝገብ በተንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ላይ በተለይ በኦሮሚያ፣በአማራና በደቡብ ኢትዮጵያ እየተፈጸሙ ያሉት ተመሳሳይ ህገወጥ ተግባራት ነገ ወደ ትብብራችን አባላትና ሌሎች ፓርቲዎች ውስጥ በግልጽና በቀጥታ የማሸጋገር አቅጣጫ መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከሰሞኑ ኢቢሲ ያቀረበው በህገመንግስታዊው የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካዊ ሥርዓት የተቀመጠውን የተቃዋሚ ፓርቲዎችን የመኖር ትርጉም ዋጋ የሚያሳጣው ‹‹መንግስትንና የመንግስት አስፈጻሚዎችን ከተቻችሁ፣ካላከበራችሁ ወይም ጸጥ ለጥ ብላችሁ የምርጫ አጃቢ ካልሆናችሁ እስከ 15 ዓመት ትታሰራላችሁ›› የሚል አንድምታ ያለው በ ‹‹ባለሙያዎች ትንታኔ ›› ሥም የተላከው የማስፈራሪያ መልዕክትና የሌሉ የፈጠራ ክሶችን ለመፈብረክ በአባል ፓርቲዎቻችን ላይ ‹‹የሞተ ጉዳዩን ከመቃብር በመቀስቀስ›› እና በአዲስ መልክ የተጀመረው የሚዲያ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻም በግልጽ ያስተላለፈው ይህንኑ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ የትብብራችን አባል ፓርቲዎች አመራሮችና አባላት ወደ ምርጫው በአንድ ምልክት ለመወዳደር በዕጩነት በቀረቡበትና በሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎች ምዝገባ ላይ በምርጫ ክልል ክስና ቅሬታ ባልቀረበበት ከምርጫ ጋር ከተያያዙ ህጎች፣መመሪያዎችና ደንቦች ውጪ በብሄራዊ ምርጫ ቦርድ የተፈጠረው ችግር፣እስከ ትናንት ማታ ድረስ ከዕጩዎች ምዝገባ ጋር በተያያዘ የትብብራችንን አባል የሰማያዊ ፓርቲን ሥም ለመጥራት የፈሩበትና እስከዛሬ ትብብራችን የሚጠቀምበትን የሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ለማስለቀቅ የተጀመረው የተቀነባበረ ሴራም የሚያረጋግጠው ይህንኑ ነው፡፡

በሌላ በኩል ገዢው ፓርቲ/መንግስት በመንግስት እና በ ‹‹ግልና ነጻ ሚዲያ ሥም ›› በተደራጁ መገናኛ ብዙሃን እያስተላለፈ ካለው ‹‹ማስፈራሪያ›› በተጨማሪ አምስቱን ዓመታት እየሰራ ያለውን የምርጫ ፕሮፖጋንዳ በማጠናከር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከህወኃት ምስረታ 40ኛ ዓመት ጋር አያይዞ ደደቢትን በ‹‹ልማታዊያን›› እያስጎበኘ፣በኢህአዴግ ውስጥ የህወኃትን የበላይነት ጠቅላይ ሚኒስትሩንና አፈ ጉባኤውን ጨምሮ በባለሥልጣናቱ እያስመሰከረ፣እንዲሁም የመሰረተ ልማት ግንባታ የመሰረት ድንጋይ እያስቀመጠ የምርጫ ቅስቀሳ አጠናክሮ በስፋት በቀጠለበትና በጠንካራ ፓርቲዎች ላይ ፖለቲካዊ ውሳኔ በተላለፈበትም ገዢው ፓርቲ ከጠበቀው ውጤት በተቃራኒ የትብብሩን ትግል ለማጠናከር አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ በተለይ የአንድነት አባላትን ከሰላማዊ ትግሉ ያላሸሻቸው ይልቁንም ወደ ትግሉ በተጠናከረ ሞራልና በላቀ ቁርጠኝነት ከትብብራችን አባል ሰማያዊ ፓርቲ መቀላቀላቸው የነጻነት ሰላማዊ ትግሉ በአጠቃላይ፣ የ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› ፕሮግራማችን በተለይ፣ በተለያየ ፓርቲ የነበሩትን በአጋርነት በማሰባሰብና ለውጡ የምመጣለትን ምልዐተ- ህዝብ ወደ ትብብራችን የበለጠ በመሳብ ለቀጣዩ የጋራ ትግል ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡ የዚህ በስፋት የመቀጠል ዕድል ከፍተኛ በመሆኑ ገዢው ፓርቲ/መንግስት /ለውጡ የሚመጣባቸው አምባገነኖች/ ላይ ድንገተኛ ከፍተኛ ፍርኃትና ሥጋት በማሳደሩ ህገመንግሥቱን በመጨፍለቅ በግልጽና በአደባባይ ህገወጥ ውሳኔዎችንና እርምጃዎችን ለመውሰድ መገደዳቸው፣ ይህም የህዝቡን የለውጥ ፍላጎትና የትግል ተነሳሽነት በማሳደግ ህዝባዊውን ትግል ወደ ላቀ/ከፍተኛ ደረጃ ማሸጋገሩ የበለጠ ግልጽ ሆኗል፡፡

ስለዚህ ከላይ በተገለጸው አገራዊ ተጨባጭ እውነታ ውስጥ የሚደረግ ሠላማዊና ህጋዊ ትግል በብልሃት/ጥበብና ዲስፕሊን የሚመራ፤ ቆራጥነትን የተላበሰ፣ የተቀናጀና ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል የሚያሳትፍ፣በጠራ ኃሳብ ላይ የቆመ መሆን እንደሚገባው፣ አመራሩም የትግሉን ህጋዊነትና ትኩረት ለይቶ ለህዝብ ግልጽ ማድረግ እንዳለበት ተረድተናል፡፡ ስለሆነም ቀጣዩ ትግላችን ፡-
በመጀመሪያ – ትብብራችን የተከተለው የጋራ ትግል ትናንት፣ዛሬም ሆነ እስከ መጨረሻው ፍጹም ህገ መንግስታዊ፣ ህጋዊና ሰላማዊ፣በአገራችንም ከረጅም ጊዜ ጀምሮ የተለመደ ነው፡፡ በተለይም ለየካቲት 15 ቀን ስናቅድ ለምርጫ 2007 በወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ዕውቅና የማይጠየቅበት የፓርቲዎች የቅስቀሳ ወቅት ስለሆነ እንደነበር፣ አሁን በከለስነው ዕቅድም የከተማ አስተዳደሮች ዕውቅና ወይም እነርሱ እንደሚሉት ‹‹ፍቃድ›› የማይጠየቁበት ለገዢው ፓርቲ የማስፈራሪያ ፕሮፖጋንዳ የማይውልና ምልዐተ-ህዝቡ ሰልፉ ተፈቅዷል/አልተፈቀደም ከሚል ጥያቄ ነጻ መሆኑ፣፤
በመቀጠልም – የትግል ጥያቄኣችን ትኩረት ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ነጻነትና ክብር መሆኑ ነው፤ ተጠቃሚዎቹ ኢትዮጵያዊያን ሁላችን ፣ በትግላችን ስኬታማነት የሚጎዱ ቢኖሩ ከግል ጥቅማቸው የሚነቀሉ፣ በአገርና ህዝብ ላይ በሰሩት ወንጀል ተጠያቂ የሚሆኑ ጥቂት አምባገነኖችና ህገወጥ የጥቅም ተጋሪዎቻቸው ብቻና ብቻ ናቸው፡፡ ገዢዎቹ እንደሚሉትና እንደሚያስፈራሩበት እንኳን ከእኛ የተለየ የፖለቲካ እምነት ያለው ዜጋ፣ ተራው የህወኃት/ኢህአዴግ አባልና ካድሬ፣ የመንግስት ሠራተኛ፣የፖሊስና መከላከያ አባልም ሆነ የደህንነት ሠራተኛ በምንም መልኩ በሚጠበቀው ለውጥ ተጎጂ እንደማይሆን፤ ለጉዳዩ ቀዳሚና ዋነኛ ባለቤት ለመራጩ ህዝብ ግልጽ ሊሆን ይገባል፡፡
በአጠቃላይ ባለንበት ተጨባጭ ሁኔታ የእኛ-የአገራችንና ዜጓቿ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ በሁለት አማራጮች ላይ የተንጠለጠለ ነው፡፡ እነዚህም በአጭር አገላለጽ፡- አንድም –ያለውን አምባገነናዊ ሥርዓት ተቀብለን፣የአገራችን ሉዓላዊነት በጥያቄ ውስጥ ባለበት፣ የጭቆና ቀንበር ተሸክመን በከፋ ውርደት ሥር ሰጥ- ለጥ ብሎ መገዛት፤ ያሊያም– አምባገነንነትና ጭቆናን ‹‹በቃ›› በማለት በሕዝባዊ የተቀናጀ ሰላማዊ ትግል ለአገራችን ሉዓላዊነትና የዜግነት ክብራችንን ለማስመለስ በህገ መንግስታዊ መብታችን ተጠቅመን ትግላችንን እስከማይቀረው ለውጥ/ ድል ደጃፍ ድረስ በቆራጥነት መቀጠል፣ ናቸው፡፡
ለእኛ ሁለተኛው ሁሉንአቀፍ የነጻነትና ክብርን የማስመለስ ሰላማዊ ትግል ብቸኛ አማራጭ ነው፡፡ግባችንም በህገመንግስታዊው የመድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት በሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ለአገራችን ሉኣላዊነት፣ዘላቂ ሠላምና ልማት፣ ለነጻነት፣ የዜግነት ክብር፣ እኩልነትና እኩል ተጠቃሚነት መረጋገጥ ነው፡፡ የመጀመሪያው በኃይል ጭቆናን በማክበድ አምባገነንነትን ለማስቀጠል የሚደረገው ሁሉ ለውጡን ያዘገየው፣መስዋዕትነቱንም ያከብደው እንደሆነ እንጂ እንደማያስቀረው ግልጽ በመሆኑ ፣ በውጤቱም ማንም ተጠቃሚ ስለማይሆን ፤በተለይም የገዢው ፓርቲ ‹‹ልዩ ተጠቃሚዎች /አምባገነኖችና ጥቂት ጭፍሮቻቸው/ ›› ተጠያቂነታቸውን የሚያጠናክር፣ህዝባዊ ትግሉም ከማናችንም/ከእነሱም ከእኛም/ ቁጥጥር ውጪ ሆኖ ሠላምና መረጋጋት ከጥያቄ የሚያስገባ አላስፈላጊ ሁኔታ እንዳይከሰት የመከላከል ሚና ያለው ነው፡፡ማለትም ትግላችን ህገመንግስታዊ መብታችንን በመጠቀም በህግና በሥርዓት የሚመራ ነው፡፡ በመሆኑም፡-
1ኛ/ ምልዐተ ህዝቡ፡- የተባበረን ህዝባዊ ትግል አሸንፎ በሥልጣኑ የዘለቀ አምባገነናዊ ሥርዓት ያለመኖሩን፣ ነጻነት ነጻ ያለመሆኑን፣ የፖለቲካ ትግል በተጨባጩ ዓለም የሚቻለውን ማድረግ ነውና የሰላማዊ ትግሉና የመድብለ ፓርቲ ሥርዓቱ በር ሙሉ በሙሉ እስኪዘጋ ባለው የንፋስ መግቢያ ቀዳዳ በመጠቀም የነጻነት ትግሉን እስከምንችለው ጫፍ ድረስ በጽናትና ቆራጥነት ለመምራት ዝግጁ መሆናችንን ተረድታችሁ፣ በገዢው ፓርቲ የ‹‹ከፋፍለህ ግዛ›› ፖሊሲ ሳትጠለፉ፣በማስፈራሪያ ፕሮፖጋንዳዎች ሳትሸማቀቁ ፣
2ኛ/ ‹‹ኢህአዴግነት ከዜግነት በላይ ›› ሆኖ የሥራ ዋስትናችሁ፣ዕድገትም ሆነ ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች በሙያችሁ፣ በልምዳችሁ፣ ክህሎታችሁ፣ በጥቅሉም በሥራ ብቃታችሁ ሳይሆን በፓርቲ አባልነት በሚመዝን ሥርዓት የሚደርስባችሁ ሁሉ እንዲገታ፣ የተነጠቃችሁትን በራስ መተማመን መንፈስ ለማስመለስ የምትተጉ፤ ሲቪል የመንግስት ሠራተኞች፣
3ኛ/ የቴለቪዥንና ሬዲዮው ‹‹ሚሊዬነርነት›› ከፕሮፖጋንዳ ያለፈ የህይወት ለውጥ ያላመጣላችሁ ‹ላም አለኝ በሰማይ ወተቷን የማላይ›› የሆነባችሁ፣ የግብርና ግብአቶች ማግኘት የዜግነት መብታችሁ ሆኖ ሳለ ‹‹የፖለቲካ ጉቦ›› የምትጠየቁ በየምክንያቱ ለመፈናቀልና ስደት የተዳረጋችሁና የተጋለጣችሁ አርሶ አደርና አርብቶ አደር ወገኖች፣
4ኛ/ በአገራችሁ በነጻነት ሰርቶ የማደር መብታችሁን ተነጥቃችሁ ለአድሎኣዊ ውድድርና ለሙሰኞች የተጋለጣችሁ፣ በየትኛውም ጊዜ ከየትም አቅጣጫ ሊመጣ በሚችል ጥቃት በስጋት እየተሰቃያችሁ ያላችሁ የንግዱ ማኅበረሰብ አባላት፣
5ኛ/ የህወኃት/ኢህአዴግ ተራ አባላትና ካድሬዎች፤ የፖለቲካ ልዩነት የተለያየ አመለካከትና ኃሳብ ማራመድ ጤናማ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ መገለጫ እንጂ እንደሚነገራችሁ ‹‹ጠላትነት›› ባለመሆኑ፣ትግላችንም ለሠላማዊና ህጋዊ የሥልጣን ሽግግር እንጂ እንደሚነገራችሁ በናንተ ‹‹መቃብር ›› ላይ አዲሱን ሥርዓት የማቆም፣ የነበረውን አጥፍቶ ከዜሮ የመጀመርና እናንተን የማጥፋት ዓላማ እንደሌለው ተረድታችሁ፣ ተቃዋሚዎች እንደናንተው ኢትዮጵያዊያንና ለኢትዮጵያና ህዝቧ የሚጨነቁ መሆናቸውን በመረዳት ተቃዋሚዎችን እንደ‹‹ ጠላት›› ከመመልከት አስተሳሰብ ራሳችሁን ነጻ አውጥታችሁ፣
6ኛ/ የፖሊስ፣ መከላከያ ሠራዊትና ደህንነት አባላት፤ ህገመንግስቱና የተሻሻለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጁ (573/2000) አንቀጽ 58 ከፓርቲ አባልነት/ተጽዕኖ ነጻነታችሁን ስለሚያረጋግጡ፣በኢትዮጵያዊያን ወገኖቻችሁ ላይ ህገ- ወጥ ትዕዛዝ በመፈጸም ከሚደርስባችሁ ህጋዊና ህሊናዊ ተጠያቂነት ራሳችሁን ጠብቃችሁ፣እንዲሁም የትግላችን ውጤት እኩል ተጠቃሚ መሆናችሁን ተረድታችሁ፣ ራሳችሁን የሚጠበቀው የስርዓት ለውጥ ‹‹ለማኞች ያደርጋችኋል ›› ከሚለው ፕሮፖጋንዳ ሰለባነት ነጻ አውጥታችሁ፣ የአምባገነኖች መጠቀሚያ መሳሪያ ከመሆን እንድትታቀቡና ህዝባዊና ህገ መንግስታዊ ወገኝተኝነታችሁን በማረጋገጥ፤
7ኛ/ ወጣቶችና ሴቶች በተለይም የወጣቶችና ሴቶች አደረጃጀቶች– ማኅበራት/ሊጎች፤በሥራ አጥነት፣ከአቅም በላይ የሆነው የኑሮ ውድነት … በስደት ህይወት ከሚደርስባችሁ ስቃይ ባሻገር በጥቅማ ጥቅም እንድትንበረከኩና የገዢው ፓርቲ አገልጋይ እንድትሆኑ የሚደረገውን ሁሉ በጥሳችሁ ፣በተለይ በመብታችሁ ትግል ስም የተደራጃችሁ የወጣቶችና ሴቶች አደረጃጀቶች- የሚሰጣችሁ ጊዜያዊ ጥቅምና የሚገባላችሁ አማላይ ቃል ኪዳን የምርጫ ሰሞን ማባበያ መሆኑን በተደጋጋሚ ያያችሁት በመሆኑ፣ የሚደረግላችሁም በዜግነት መብታችሁ ማግኘት የሚገባችሁን እንጂ የገዢው ፓርቲ ሥጦታ ባለመሆኑ፤
8ኛ/ መምህራንና ተማሪዎች በተለይም የዩኒቨርስቲና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች፡-በአገራችን የለውጥ ኃይል ማዕከልና ግንባር ቀደም ተሰላፊ የሆናችሁበትን ታሪክ እንድታድሱና ዛሬም እንደ ትናንቱ አገራችሁና ህዝባችሁ ከናንተ ብዙ የሚጠብቁ መሆናችሁን ተረድታችሁ፣
9ኛ/ የእምነት ነጻነት መብት ጠያቂ የማኅበረሰብ አባላት፡- በተለያዩ እምነት ተከታዮች እየቀረቡ ያሉት የእምነት ነጻነት ጥያቄዎች ከሠላማዊውና ህጋዊው የሥርዓት ለውጥና የነጻነት ጥያቄኣችን የማይነጣጠሉ በመሆናቸው በተናጠል መልስ የማያገኙና መፍትሄውም የዘላቂው ሁለንተናዊ ለውጥ አካል መሆኑን ተረድታችሁ፤
10ኛ/ ኢትዮጵያዊ የመገናኛ ብዙሃን አባላት፡- በአገር ቤትና በውጪ የምትገኙ ነጻና የአገርና ህዝብ ወገንተኛ የመገናኛ ብዙሃን አባላት፣ በተለይም በተሻለ ኃሳብን በነጻ የመግለጽ መብት በተከበረበት የምትገኙት የህዝብ ጆሮና ዓይን በመሆን የምትሰጡትን አገልግሎት በማጠናከር የተያያዝነውን ሰላማዊና ሕዝባዊ ትግል አማራጭ ኃሳባችንና የትግል ጥሪያችንን ለህዝቡ በማቅረብ የዲሞክራሲ፣ የአገርና ሕዝብ ወገንተኝነታችሁን አጠናክራችሁ በመቀጠል፤
11ኛ/ የፍትህ አካላት፡- በትምህርት ያገነባችሁትና በልምድ ያዳበራችሁት ሙያዊ ቃልኪዳንና የሰብዐዊ ኅሊናችሁ ሚዛን የሚጥልባችሁ ኃላፊነት በጊዚያዊ- የሚያልፍ ጥቅም በአገራችሁና ወገናችሁ ላይ ፍትህን እንዳታጓድሉ ያስገድዳሉና የአምባገነኖች መጠቀሚያ መሳሪያ በመሆን ከመተባበር እንድትቆጠቡ፣
12ኛ/ ሌሎች ዲሞክራቲክ ፓርቲዎች፡- በአምባገነን ሥርዓቱ በተናጠል የሚደርስብንን አፈና በጋራ ለመመከትና የመድብለ ፓርቲ ትግላችንን ቀጣይነት ለማረጋገጥ፣በሚያግባቡን የምርጫ ጉዳዮችና የብሄራዊ ውይይትና ዕርቅ ጉዳይ ላይ በአጋርነት በጋራ የመቆም አስፈላጊነት ለነገ የማይባል ነው ስለሆነ፣
13ኛ/ ፓርቲዎቻችሁን የተነጠቃችሁ የነጻነትና የዲሞክራሲ ሰላማዊ ታጋዮች፡- እስካሁን ባለው ጊዜ አፋጣኝና ወሳኝ ፖለቲካዊ ውሳኔ በመስጠት ከትብብሩ አባል ሰማያዊ ፓርቲ የተቀላቀላችሁትን እንኳን ደህና መጣችሁ እያልን፣ ሌሎቻችሁም የትብብራችን አገራዊ የጋራ ዓላማ ከወቅታዊ ሁኔታው ጋር በማገናዘብ፣
14ኛ/ በውጪ አገር የምትኖሩ ኢትዮጵዊያን/ዲያስፖራዎች፡- በተያያዝነው ሰላማዊና ሕዝባዊ ትግል ያላችሁን ሚና በግልጽ ለይታችሁ፣ ተሳትፎኣችሁና ድጋፋችሁ ለትግላችን ያለውን ከፍተኛ አስተዋጽኦ በመገንዘብ ለአገራችሁና ህዝባችሁ ባላችሁ የባለቤትነትና የወገናዊነት ኃላፊነት መሰረት፣
በምናደርገው አገራዊ፣ሰላማዊና ሕዝባዊ ትግል በማይቀረው የሥርዓት ለውጥ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር በአንድነትና በቆራጥነት እንድትሰለፉ፤ የየካቲት 22/07 ቀጠሮኣችንም የማይቀርበት በመሆኑ በየከተሞቹ በቦታውና በሰዓቱ እንድትገኙ ጥሪያችንን አበክረን እናቀርባለን፡፡
በተቀናጀ የጋራ አመራር የተባበረ ህዝባዊ ሠላማዊ ትግል በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንደምትገነባ አንጠራጠርም!

ያለ መስዋዕትነት ድል የለም!

የካቲት 10/ 2007 ዓ.ም፣ አዲስ አበባ

 

Filed in: Amharic