>

በ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› የጀመርነው ነጻነታችን የማስመለስ ትግል ይቀጥላል! [ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሠጠ መግለጫ]

ትብብራችን ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› በሚል መርህ እያካሄደ ያለው የጋራ እንቅስቃሴ መነሻና መሰረት የትብብሩን መግባቢያ ስምምነት ከመፈራረማችን በፊት በ14 ፓርቲዎች ‹‹የተቃውሞ ጎራው ዲሞክራቲክ ኃይሎች በትብብር ለመሥራት ያደረጉት ተደጋጋሚ ጥረት ለምን ከሸፈ?›› በሚል የተደረገው ጥናትና የጸደቀው መግባቢያ ሰነድና በእነዚህ ላይ የቆመው በትብብር አባላት የተዘጋጀው የተግባር ዕቅዳችን ነው፡፡

በእነዚህ ሰነዶች መሰረት የትብብሩ አባላት በሦስት መሰረታዊ ጉዳዮች ማለትም በምርጫ፣ በፖለቲካ ምህዳርና በዜጎች ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ዙሪያ በደረሱት የጋራ ግንዛቤዎች መሰረት ካስቀመጥናቸው ሁለት ግልጽ ዓላማዎች አንዱ የፖለቲካ ምህዳሩን በማስፋትና የምርጫ ሜዳውን በማስተካከል መጪው ምርጫ ነጻ፣ ፍትሃዊ አሳታፊና ተኣማኒ የማድረግ የጋራ የተባበረ ትግል ማካሄድ እንደመሆኑ ለዚህ ተፈጻሚነት ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› በሚል መርህ የጋራ እንቅስቃሴ ከጀመርን ወራት መቆጠራቸው ይታወቃል፡፡
በመጀመሪያ ዙር የጋራ እንቅስቃሴኣችን የተያያዝነው ትግልን አስፈላጊነት፣ ወቅታዊነትና የዓላማችንንና የትግል ስልታችንን ትክክለኛነት በተግባር አረጋግጠን፣ ባደረግነው ትግል ያስመዘገብናቸውን ውጤቶች መዝግበን በሁለተኛውን ዙር ዕቅዳች ላስቀመጥናቸው ተግባራት በዝግጅት ላይ እንገኛለን፡፡
በተደጋጋሚ እንደገለጽነው የ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› ተግባራት ተመጋጋቢና ተደማማሪ እንደመሆናቸው የተያያዝነው የጋራ ትግል ተጠናክሮ መቀጠል አጠያያቂ አይደለም፡፡ በአምባገነን ሥርዓት የነጻ ዲሞክራሲ ተቋማት እንቅስቃሴ አስቸጋሪ መሆኑ እንዳለ ሆኖ በምርጫ አስፈጻሚነት የተሰየመው አካል (የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ) በዕውቀትና ፍላጎት በህገመንግስቱና በአዋጅ የተሰጠውን ሥልጣንና ተግባር ወደጎን ገፍቶ በህግም ሆነ በአሰራር ወደማይመለከተው ተግባር በመግባት ባልተጠየቀበት መገኘቱ ትግሉን የበለጠ ከባድ እንደሚያደርገው መረዳት ቀላል ነው፡፡ ሆኖም ትግላችንም ሆነ የምጠይቀው መስዋዕትነት የቱንም ያህል ይክበድ ዓላማችን ከግቡ ለማድረስ የጀመርነውን የጋራ ትግል አጠናክረን ምርጫውን ነጻ፣ ፍትሃዊ አሳታፊና ተኣማኒ የማድረግ የህዝባዊ ንቅናቄ ማቀጣጠል ተግባራችን ለአፍታም አይገታም፣ ወደግባችን ለመድረስ የሰነቅነው ተስፋ አይደበዝዝም፣ የተጀመረው ጉዞ ህዝቡን ዞ ወደፊት ይጓዛል እንጂ አያፈገፍግም፤ በዚህም የተዘጋውን በር እንደምናስከፍት እምነታችን ነው፡፡ በመሆኑም በተያያዝነው የ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ ›› ትግላችን ህዝቡን ከዳር እስከ ዳር በማነቃነቅ ነጻነቱን፣ መብቱንና ክብሩን የማስመለስ ትግል በቆራጥነት መርተን ህዝቡን የሥልጣን ባለቤት እንደምናደርግ አንጠራጠርም፡፡
የጋራ ትግላችን ህገመንግስታዊ፣ ህጋዊና ሠላማዊ በመሆኑ ህዝቡ የሥልጣን ባለቤትነቱን ካረጋገጠ፣ አስተማማኝ የተባበረ አማራጭ የፖለቲካ ኃይል ካገኘ ማንን እንደሚመርጥ አያጣውምና ትብብራችን አማራጭ ሆኖ በመቅረብ በምርጫው እንደምናሸንፍ እናምናለን፡፡ ለዚህም ከጅምሩ የትብብሩ አባል ፓርቲዎች በተናጠልና በጋራ ከነጻነት ትግሉ ጎን ለጎን የምርጫ ዝግጅታቸውን እንዲያደርጉ አቅጣጫ አስቀምጠን ወደ ተግባር ገብተናል፡፡ ይህም ዛሬም ትግላችን በጨለማው ውስጥ የምታየንን ጭላንጭል የነጻነት ብርሃን ፍንጣቂ የማስፋት ፣በህዝቡ ውስጥ የሚንቦገበውን የለውጥ ፍላጎት የማስተባበርና የማቀናጀት ፣የተባብራችሁ ምሩን ጥያቄውን የመመለስ እንጂ ‹‹ውድድረት በሌለበት፣ ነጻነታችን በታፈነበት ምርጫ አይኖርም›› ከሚለው አቋማችን ዝንፍ ያለ አይደለም፡፡ የእምነታችን መሠረትም እምቢ ለነጻነቴ ያለን ለለውጥ ቆርጦ የተነሳን የህዝብ ኃይል አሸንፎ አምባገነንነት በሥልጣን ሊዘልቅ የቻለበት የተመለከትነው፣ ተመዝግቦ የተቀመጠና የተማርነው ታሪክ የለም የሚለው ነው፡፡
ስለሆነም፡-
1ኛ/ የትግሉ ቀዳሚና ዋነኛ ባለቤት የሆንከው መራጩ ህዝብ ነጻነትና ክብርህን ለማስመለስ በምናደርገው ትግል በንቃት እንድታሳተፍ፣ ዛሬውኑ በመመዝገብ የሥልጣን ባለቤትነትህን የምታረጋግጥበትንና ይህን አምባገነናዊ ሥርዓት የምትቀጣበትን ትጥቅ ‹‹የምርጫ ካርድህ››ን በእጅህ እንድታስገባ፤
2ኛ/ በውጪ አገር የምትኖሩ ኢትዮጵያዊያን ለተያያዝነው እልህ አስጨራሽ ትግል ሁለንተናዊ በተለይም የዲፕሎማሲና የፋይናንስ ድጋፍ የጀመራችሁትን ጥረት አጠናክራችሁ እንድትቀጥሉ፤
3ኛ/ ሃቀኛ የታቀውሞ ጎራው ፓርቲዎች በተለይም የጥናቱና የመግባቢያ ሰነዱ ባለቤት የሆናችሁ በዚህ የተባበረ ትግልና የተቀናጀ እንቅስቃሴ ያለ ቅድመ ሁኔታ እንድትቀላቀሉና ለህዝቡ የጠራ የፖለቲካ አማራጭ ኃይል ሆነን ለመቅረብ የምናደርገው ጥረት አካል እንድትሆኑ፤
4ኛ/ በአስፈጻሚ ተቋማት በተለያየ ዘርፍ የተሰማራችሁ የህወኃት/ኢህአዴግ አባላትና ሲቪል የመንግሥት ሠራተኞች፣ የፖሊስና መከላከያ ኃይልና የፀጥታና ደህንነት አባላት የትግላችን ትኩረት ከጥቂት አምባገነኖችና በሙስና የታወሩ ጥቅመኛ ጭፍን ደጋፊዎቻቸው ላይ በመሆኑ ሰልፋችሁን ከህዝብና አገር ጥቅም፣ ከነጻነታችሁና ክብራችሁ ጎን አስተካክላችሁ የድላችን ውጤት የእኩል ተጋሪና ተጠቃሚ እንድትሆኑ፤
5ኛ/ የምርጫ ቦርድ ባለሙያዎችና በተለያየ ደረጃ የምትገኙ የምርጫ አስፈጻሚዎች ትግላችን ለአገርና ህዝብ ዘላቂ ጥቅም በመሆኑ በገለልተኛነትና ወገናዊነታችሁን ለህዝብና ህገ መንግስቱ አድርጋችሁ ሙያዊ ግዴታችሁን በኅሊና ተጠያቂነት መንፈስ እንድታከናውኑ፤
6ኛ/ የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና መንግስታት የሚያልፉ ህዝብና አገር የማያልፉ በመሆናቸው አጋርነታችሁ ከማያልፉት ጋር መሆኑን እንድታረጋግጡና ለአምባገነኑ ሥርዓት ቀጣይነት የምታደርጉትን ድጋፍ እንድትመረምሩ፤ ጥሪያችንን አበክረን እናቀርባለን፡፡
በእኛ በኩል ለአገራችንና ህዝባችን የምንቆጥበው አንዳችም የለምና ትግሉ የሚጠይቀንን መስዋዕትነት ሁሉ በመክፈል የተባበረ አመራር ለመስጠት ያለንን ቁርጠኝነት ደግመን እናረጋግጣለን፡፡
ለመስዋዕትነት የተዘጋጀ የተባበረና የተቀናጀ ህዝባዊ ትግል ያሸንፋል!!
ጥር 12/2007 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ

Filed in: Amharic