>

የመድብለ ፓርቲ ስርዓት እንዳይፈጠር የምርጫ ቦርድ ታሪካዊ ወንጀል እየፈፀመ ነው [አንድነት ፓርቲ - መግለጫ]

የአንድነት ፓርቲ በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዲፈጠር በምንም መለኪያ በገለልተኝነት የማንጠብቃቸውን የዲሞክራሲ ተቋማት በተግባር ለመፈተን እንዲቻል የሁለት ሺ ሰባት ምርጫን በሁሉም ሂደቶች ህዝቡን በማሳተፍ እንደሚወዳደር እና ህዝብን የስልጣን ባለቤት ለማድረግ እና የኢህአዴግ አገዛዝ የመጨረሻ እንዲሆን በቁርጠኝነት እንደሚሰራ መወሰኑ ይታወቃል፡፡ ይህን ስንወስን እነዚህ ተቋማት ገለልተኝነታቸውን አረጋግጠው ታሪክ የሚሰሩበት እድልም ያገኛሉ የሚል ተሰፋ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ይህን እድል ከመጠቀም እና በህግ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት ከመወጣት ይልቅ ለገዢው ፓርቲ ያለውን ወገንተኝነት በምርጫው ሂደት ዋዜማ በይፋ እያረጋገጠ ይገኛል፡፡ አሁንም ቦርዱ ወሰነ ተብሎ በሚዲያ የተገለፀው እንዲሁም ለፓርቲያችን በፅሁፍ የተሰጠው “በአስራ አምስት ቀን ውስጥ በጋራ ጉባዔ አድርጉ” የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ በተደጋጋሚ ፓርቲያችንን ደንብ እንዲያከብር እየጠየኩ ነው በማለት ከደንብ ውጭ እንድንሰራ የአዛኝ ቂብ አንጓች ሆኖዋል፡፡ የአንድነት ፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ የመጥራት ኃላፊትን ያለበት የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ወይም ደግሞ በአባላት ጥያቄ የጠቀላላ ጉባዔ አባላትን አንድ ሶስተኛ ፊርማ አስባስበው በኦዲትና ኢንስፔክሽን ትዕዛዝ መሆኑ በግልፅ እየታወቀ ከፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ ውጭ በ15 ቀን ውስጥ ጉባዔ ጥሩ የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ ከገዢው ፓርቲ ጎን ተሰልፉ እየተጫወተ አንድነትን ከጫወታ ለማስወጣት ካለሆነ ሌላ ምንም ትርጉም ልንሰጠው አንችልም፡፡ ይህ ደግሞ ቦርዱ እየሰራ ያለውን ታሪካዊ ወንጀል ይፋ የሚያደርግ ነው፡፡
ይህ በማን አለብኝ ሰሜት የተሰጠ ውሳኔ ሳይታረም ቢቀርና ገዢው ፓርቲ ያለምንም ጠንካራ ተቀናቃኝ ብቻውን ሮጦ ብቻውን እንዲያሻንፍ የሚያደረግ ተቋማዊ ሴራ ቦርዱን በታሪክ ተጠያቂ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በዚህች ሀገር ዘላቂ ሰላም ላይ ለሚፈጠረው አደጋ ቦርዱ ከተጠያቂነት እንደማይድን ለማስታወስ እንወዳለን፡፡
በዚህ አጋጣሚ አንድነት ፓርቲ የሰላማዊ ትግሉን ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ ለማድረግ እና ህዝቡን የስልጣን ባለቤት የማድረግ እንቅስቃሴውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና በቀጣይ ሳምንታትም በመንግሰትና በቦርዱ ላይ ጫና ማሳደሩን እንደሚቀጥልበት እያረጋገጥን አንድነት ፓርቲ ወደ ህገወጥነት የሚወሰደውን “የጋራ ጉባዔ” አካሂዱ የሚለው የምርጫ ቦርድ ውሳኔ የማንቀበለው መሆኑን ለመላው አባላትና ደጋፊውች ማረጋገጥ እንወዳለን፡፡

ጥር 8/2007

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ/አንድነት/

Filed in: Amharic