>
5:13 pm - Thursday April 19, 6751

ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ተሰቀለ?(ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም)

በዚህ ርእስ ላይ የምጽፈው ሃይማኖትን ለመስበክ ፈልጌ አይደለም፤ ከውስጥ የሚኮረኩረኝን ነገር ለማውጣት ነው፤ በኢትዮጵያ የተስፋ ሕልም አይታየኝም፤ የሚታየኝ የጥፋት ቅዠት ነው፤ ከሃያ ዓመት በላይ በመለስ ዜናዊና በጓደኞቹ በኩራትና በእብሪት የተዘራው ጥላቻ የኢትዮጵያ ሕዝብ ልቡ የደም መግል እንዲቋጥር አድርጎታል፤ ይህንን የማይገነዘብ ያለ አይመስለኝም፤ ነገር ግን ባህል ሆኖብን አደጋ ማስጠንቀቂያን አንወድም፤ በአንጻሩ ግን በባዶ ሜዳ ለሽለላና ለፉከራ የሚጋብዘንን እንወዳለን፤ እኔ ማንንም የሚያስፎክር ነገር አይታየኝም፤ ማንንም የሚያሳብይ ነገር አይታየኝም፤ ክርስቶስ የተሰቀለበት ምክንያት ግን በድፍን ጨለማው ውስጥ ብልጭታን ያሳየኛል፤ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዋናው ምክንያት ‹‹ክፉን በክፉ አትመልሱ ስላለ ነው፤ የኢየሱስ ክርስቶስ አብዮት ይኸው ነው።

‹‹ባልንጀራህን ውደድ ጠላትህንም ጥላ እንደተባለ ሰምታቸኋል፤ እኔ ግን እላችኋለሁ፤ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ የሚረግሟችሁንም መርቁ፤ ለሚጠሏችሁም መልካም አድርጉ፤ስለሚያሳድዷችሁም ጸልዩ፤›› ማቴ. 5/43

አልፎ አልፎም ቢሆን እያንዳንዳችን ራሳችንን ልንጠይቀው የሚገባ ጥያቄ ነው፤– ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ተሰቀለ? የኢየሱስ ክርስቶስ መሠረታዊው ትምህርት ክፉን በክፉ አትመልሱ የሚል ነው፤ እስቲ ይህንን የምታነቡ ሰዎች ይህን ሦስት ቃላትን ብቻ የያዘ ዓረፍተ ነገር ደጋግማችሁ አንብቡት፤ ቀላል ነው ብላችሁ አትለፉት፤ ይህ ትምህርት እንዴት ነው አስጊ ሆኖ የታየው? እንዴት ነው ለስቅላት የሚያበቃ ወንጀል የሆነው?mesfin-woldemariam
እንራመድና ሌላ ጥያቄ እንጠይቅ፡- ዛሬ ከሁለት ሺህ ዓመታት በኋላ የክርስቶስ ትምህርት ገብቶናል ወይ? በየአህገሩ፣ በያገሩ‹ በየመንደሩ ስናይ የሰው ልጆች የክርስቶስን ትምህርት የሰሙ አይመስልም፤ ወይም ሰምተው ክርስቶስ የተናገረው ለመላእክት ነው ብለው ይሆናል! በአለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት ውስጥ የሰው ልጆች በአጠቃላይ በተለይ ክርስቲያኖች ስንት ጦርነቶችን አካሄዱ? ስንትስ ሚልዮን ሰዎች አለቁ? ስንት ሚልዮን ተፈናቀሉ? ስንት ለዕድሜ ልክ አካለ-ስንኩላን ሆነዋል? ከሁሉም ይበልጥ በመስቀሉ ላይ ሆኖ ፍቅርን የሰበከውን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምህርት ለጥልና ለመነታረኪያ እየተጠቀሙበት ነው።

ለትንሣኤ ለመብቃት ከሞት ጋር መጋፈጥ ያስፈልጋል፤ ያውም ተራ ሞት አይደለም፤ ለዓላማ በፈቃደኛነት የሚቀበሉት የመከራ ሞት ነው፤ መስዋእትነት የሚባለውም ይህ ነው፤ የኢትዮጵያ ዜና ማሰራጫ ሰዎች ሞት የሚለውን ቃል ይፈሩታል፤ አይጠቀሙበትም፤ ህልፈት በሚል ቃል ተክተውታል፤ እንደመለስ ያለ ሰው እንዴት ይሞታል፣ ያልፋል እንጂ! እንደዓለማየሁ ያለ ሰው እንዴት ይሞታል ያልፋል እንጂ! ይበልጥ የሚያስደንቀው በክብር ተሸኝተው የሞቱትን መስዋእት ሆኑ ማለታቸው ነው! ሞትን ስሙን እንክዋን ለመጥራት እየፈሩት መስዋእትነትን ሊያከብሩ ይከጅላቸዋል፤ ክርስቶስ ተደብድቦና ተገርፎ፣ በምስማር እጆቹና እግሮቹ በአንጨት ላይ ተከርችሞበት፣ በራሱ ላይ የእሾህ አክሊል አስቀምጠውበት ሰቅለው ከሞተ በኋላ ቀበሩት፤ በሞቱም ለሰው ልጆች ኃጢአት ራሱን መስዋእት አደረገ፤ ሞትንም፣ መቃብርንም አሸንፎ ተነሣ፤ ትንሣኤ ይህ ነው፤ ይህ ከባድ ነው፤ ክፉን በክፉ አትመልሱ የሚለው ትምህርቱ ከሁለት ሺህ ዓመታት በኋላ ያልገባን ለዚህ ነው።

በሌላ በኩል ስናይ አንዳንድ ሰዎች እንደእናት ቴሬዛ፣ እንደእናት አበበች ጎበና፣ እንደወንድም ብንያም (የመቄዶንያ)፣ … ያሉ ሰዎች በግለሰብ ደረጃ ለክርስቶስ ትምህርት ቅርብ ሆነው እናገኛቸዋለን፤ አብዛኛው በጣም ሲርቅ እነዚህ ሰዎች አብዛኛዎች ሰዎች የተሸነፉበትን ዳገት አንዴት ወጡት? እነሱ በብዛት ያገኙት ጸጋ ለሌሎች እንዴት አልደረሰም? እንደሚመስለኝ ሳይደርስ ቀርቶ አይደለም፤ ይኸው ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ሰው ለሁለት ጌቶች አይገዛም ብሏልና በሁለት እጆቻቸው ሌላ ነገር እንቅ አድርገው የያዙ ሰዎች ጸጋውን የሚቀበሉበትና የሚይዙበት እጅ የላቸውም፤ የክርስቶስ ጸጋ ማጋበስን ይጠየፋል፤ የጤፍ ቅንጣት ያህል እምነት ቢኖራችሁ ተራራውን ና ብትሉት ይመጣል፤ ሂድ ብትሉትም ይሄዳል፤ ያለውንም እናስታውስ፤ ቀይ ባሕርን ለሁለት ከፍሎ፣ በአምስት ዓሣዎች አምስት ሺህ ሰዎችን መግቦ በተግባር አሳይቷል።

በኢትዮጵያውያን መሀከል የሚካሄደውን ንትርክ በጥሞና የተከታተለ ሰው አንድ አገር አንድ ማኅበረሰብ መሥርተን አንድ ሕዝብ ሆነን የምንቀጥልበት መንገድ አለ ወይ ብሎ ለመጠየቅ ይገደዳል፤ በአንድነት እንድንቀጥል የሚፈልጉትም ራሳቸውን ያታልላሉ፤ በታትነን እንቃረጣለን የሚሉትም ራሳቸውን ያታልላሉ፤ በሁለቱም ወገን ያሉት ለሚፈልጉት ነገር አልተዘጋጁም፤ ያቀፉት ተቃራኒ ምኞቶችን ብቻ ነው፤ የአንዱ ጥላቻ አባትና እናቱን እንዲያፋታ ይገፋፋዋል፤ የሌላው ጥላቻ ደግሞ የተጣሉ እናትና አባቱን አንድ ቤት ውስጥ ቆልፎባቸው፣ በግድ ተፋቀሩ! ይላቸዋል፤ ሁለቱም ከየራሳቸው ምኞት ውጭ የሚያዩት የለም፤ በአርሲ የተገነባውን ሐውልት እንዴት ያለ አእምሮ ጸነሰው? ጡት መቁረጥ የየት አካባቢ ባህል ነው? የኦሮሞን ባህል አያስታውስም? እኔ በሻሸመኔ ያየሁት በጦር ተገድሎ የተሰለበው ሰውዬስ ሐውልት የሚቆምለት መቼ ይሆን? እንዲህ ዓይነቱ ቁስል መፋቅ አብሮ የሚያኖር አይደለም።

ባህል ያልሆነ በጦርነት ጡትን መቁረጥ ከባህላዊው እንትንን ከመቁረጥ የበለጠ ሆኖ ሐውልት የሚሠራለት አዙሮ ማየት ሲጠፋ ነው፤ ራስን ሰድቦ ለሰዳቢ መስጠት የሚባለው ይህ አይደለም? ዶር. በድሉ ዋቅጅራ እንዳለው ‹‹ኑ ሀውልት እንስራ!! … ኑ ሀውልት እንስራ ለልጅ ልጅ የሚዘልቅ፣

የጥላቻ ጥንስስ
የቂም በቀል ድግስ።››

መጥፎ ምርጫ ነው፡- እየተደባደቡ፣ እየተጋደሉ ሲመች ለወንጀሉ ሐውልት እየሠሩ ማለፍ አንድ ምርጫ ነው፤ አንዱን ሰው ከታችም ይሁን ከላይ ምኑንም ይሁን ምኑን የቆረጠውን ኮንነን፣ ክፉን በክፉ አትመልሱ የሚለውን አርማ ይዘን ለአዲስ ግንባታ በኅብረት ወደፊት መገስገስ ሁለተኛ ምርጫ ነው፤ የክርስቶስን ትምህርት ብንከተል ከዚህ ያወጣን ነበረ፣ እንግዲህ በጥበቡ ያውጣን።

Filed in: Amharic