>
5:13 pm - Sunday April 19, 9068

በቢሮክራሲያዊ ሴራ የዜጎችን ህገመንግሥታዊ መብት ማፈን ሠላማዊ ትግሉን አያቆመውም!! [ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ መግለጫ]

ዘጠኝ /9/ ህጋዊ ሰውነት ያለን ፓርቲዎች በትብብር ለመሥራት በተስማማነው መሠረት የአጭር ጊዜ የጋራ ዓላማችንን ማስፈጸሚያ ተግባራት የመጀመሪያ ዙር ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› በሚል መርህ የአንድ ወር ዕቅድ አውጥተን ወደ ሥራ መግባታችን ይታወሳል፡፡ የዚሁ የአንድ ወር ዕቅድ አካል ከሆኑት ተግባራት ቅዳሜ በ6/03/07ዓ.ም ‹‹ዲሞክራሲያዊ ምርጫና የአፈጻጸም መርሆዎች›› በሚል ርዕስ የአዳራሽ ውይይት በተሳካ ሁኔታ አከናውነን በትናንትናው ዕለት በ07/03/07ዓ.ም ደግሞ ከአዲስ አበባ ሰሜን ምስራቅ /ከአራት ኪሎና አካባቢው / ህዝብ ጋር በአደባባይ በቤልኤር ሜዳ ተገናኝተን በምርጫ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት የትብብራችን አባል የሆነው ሰማያዊ ፓርቲ ስብሰባውን እንዲያስተባብር በሰጠነው ኃላፊነት- የፖለቲካ ስብሰባ ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 3/1983 የምጠይቀውን ሁኔታ አሟልቶ ለከንቲባ ጽ/ቤቱ የሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ክፍል በ02/03/07 ደብዳቤ ማስገባቱ፣ የጽ/ቤቱ ክፍልም ለደብዳቤው በ04/03/07 ዓ.ም መልስ መስጠቱ ይታወቃል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ከክፍሉ የተጻፈለት ደብዳቤ፡-

1. የተሰጠው መልስ ዕውቅናውን በተመለከተ ግልጽ ያለመሆኑን፤

2. ከላይ በተጠቀሰው አዋጅ መሰረት አንቀጽ 2 ንዑስ አንቀጽ 2 ላይ የተገለጸውን የሚጻረር መሆኑን፣

3. በአዋጁ አንቀጽ 6 ንዑስ አንቀጽ 1 ላይ ከተደነገገው ጋር የሚቃረን፤
በጥቅሉ በክፍሉ የተጻፈው ደብዳቤ በአዋጁ መሰረት በ12 ሰዓት ውስጥ የተሰጠ ምላሽ ካለመሆኑም፣ ጊዜና ቦታውን ለመቀየር እንኳ አማራጭ ያልቀረበበት፣ ለስብሰባው ዕውቅና ለመንፈግ እንደ ምክንያት የቀረበውም ግልጽ ሆኖ ባለመቅረቡ ፓርቲው የተጻፈውን ደብዳቤ አሳማኝ ሆኖ እንዳላገኘውና እንዳልተቀበለው፣ በመሆኑም ስብሰባው አስቀድሞ በተገለጸው ቦታና ጊዜ እንደሚካሄድ በ05/03/07 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ መልስ በመጻፍ ለክፍሉ ገቢ አድርጎ ዝግጅቱን ቀጥለናል፡፡ ከዚህ በኋላ ባለው ጊዜ ክፍሉ በደብዳቤም ሆነ በአካልና ስልክ ሳያገኘን ዝግጅታችንን አጠናቀን በዕለቱ በተገጸው ሰዓት ወደ ቦታው ስንሄድ ያጋጠመን ሁኔታ ፡-

1ኛ/ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 9 የተቀመጠውን ‹‹የህገመንግስት የበላይነት›› ያልተከተለ፤

2ኛ/ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 10(2) የተቀመጠውን የዜጎች መብት በመዳፈርና ለማፈን፤

3ኛ/በህገ መንግስቱ አንቀጽ 12 የተቀመጠውን ‹‹የመንግስት አሠራር ተጠያቂነት›› በጣሰ
ሁኔታ፤

4ኛ/ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 13 የተቀመጠውን የህገ መንግስት ‹‹ተፈጻሚነትና አተረጓጎም›› በመተላለፍ፤

የተፈጸመ ኢህገመንግሥታዊና ኢ-ዲሞክራሲያዊ፤ በሠላማዊ ዜጎችና በፖሊስ መካከል ግጭት የሚፈጠርበትን ሁኔታ የሚጋብዝ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ ይህ ሁኔታ በወቅቱ በቦታው የተገኙት
የአካባቢው ፖሊስ ጣቢያ ባልደረባና የተልዕኮው ቡድን መሪ ከመሆናቸው ውጪ የራሳቸውን ማንነት/ሥምና ኃላፊነት ለመግለጽ ድፍረት በማጣታቸው፣ በአንድ በኩል ‹‹የእንጀራ ጉዳይ ሆኖባቸው የታዘዙትን የማስፈጸም ግዳጅ›› በሌላ በኩል ከስብሰባው አስተባባሪዎችና የትብብሩ አመራሮች ለቀረቡላቸው አዋጁን ያጣቀሱ ህገ መንግስታዊ የመብት ጥያቄዎች ‹‹አሳማኝ መልስ ለመስጠት በመቸገራቸው ›› በጭንቀት ውስጥ መውደቃቸውን አረጋግጠናል፡፡ በቦታው የነበረን ቆይታ በተራዘመና ጥያቄኣችንም በተደጋገመ መጠን በአንድ በኩል ‹‹የቡድን መሪው›› ጭንቀት ወደ ኃፍረት፣ ብስጭትና የግጭት ስሜት የፖሊስ አባላቱ መንፈስ ደግሞ ወደ ሥጋት ሲሸጋገር፣ በሌላ በኩል ደግሞ የስብሰባውን ጥሪ ተቀብለው የመጡ ዜጎች ‹‹ስብሰባው ይጀመር፤ እዚህ የመጣነው በመብታችን ልንደራደር አይደለምና የሚያመጡትን እናያለን ›› ግፊት እያየለ በተሰብሳቢውና በፖሊስ መካከል እሰጥ አገባውና ፍጥጫው እየተጠናከረ ሄዷል፡፡

የትብብራችን አመራር መስተዳድሩ በደብዳቤው የገለጸውን ማለትም ‹‹ጥያቄ በቀረበበት ቀን ቀድም ብሎ ዕውቅና የተሰጣቸው ፕሮግራሞች ስላሉ በዕለቱ የፀጥታ አስከባሪዎች የኃይል እጥረት ሊያጋጥም ስለሚችል›› የተባለውን በወቅቱ በህዝቡ ውስጥ ፈሶ ከነበረው ከ100 በላይ የአዲስ አበባና ፌዴራል ፖሊስ ቁጥርና በተጠባባቂነት በአንድ ማክ መኪና ተጭኖ በጋራዥ ውስጥ ተደብቆ ይጠባበቅ ከነበረ የፖሊስ ኃይል ጋር በማገናዘብ በሂደቱ ሴራ እንዳለበት ማረጋገጥ ችሏል፡፡ በመሆኑም አመራሩ ሂደቱን ከትግሉ ዓላማና መርህ ፣ለዓላማው ማስፈጸሚያ በተከታታይና በቀጣይነት በታቀደው ሰላማዊ ትግል ላይ ከሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ፣ ለእንዲህ ዓይነቱ ሴራ ከተደረገው ዝግጅትና በፖሊስ በኩል ከታየው የ‹‹ጭንቅ›› ስሜትና ተደጋጋሚ ውትወታ ካለበት ኃላፊነት ጋር በማገናዘብ የዕለቱ ፕሮግራም በሰላም እንዲጠናቀቅ የማረጋጋት ተግባር በማከናወን ህዝቡን በሠላም አሰናብቷል፡፡ ከዕለቱ ውሎ በመነሳት አመራሩ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ የሚከተሉትን የጋራ ግንዛቤዎች ጨብጧል፡፡

1ኛ/ ትብብሩ በመርሃ ግብሩ መሰረት በዕለቱ የተሞከረው ህዝባዊ ስብሰባ ለታሰበለት የድምር ውጤትና የትግሉን ቀጣይነት የማረጋገጥ ፋይዳ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቷል፤

2ኛ/ የዕለቱ ውሎ ገዢው ፓርቲ የደረሰበትን የፍርኃት እርከን የሚመለክት ነው፤ ደፍሮ ባይናገረውም በተግባር በሠላማዊ ህዝባዊ ንቅናቄዎች የቱን ያህል እንደሚሸበር በተግባር ያረጋገጠበት ነው፤

3ኛ/በስብሰባው ላይ የተገኙ ኢትዮጵያዊያን ያሳዩት ቆራጥነትና ለመብታቸው ለመቆም ያላቸው ጽናትና የቱንም ዋጋ ለመክፈል ያላቸው ዝግጁነት ለቀጣዩ ትግል ከፍተኛ ሥንቅ ነው፡፡ይህም ለተያያዝነው የጋራ ትግል በእጅጉ አበረታች ነው ፤

4ኛ/ገዢው ፓርቲ/መንግሥት ከገባበት ከፍተኛ የፍርኃት ስሜት ለመውጣት ያስቀመጠው የሴራ መፍትሄ መስዋዕትነቱን ይጨምር እንደሆን እንጂ፣ ትግሉን አያቆመውም፡፡

ከእነዚህ ግንዛቤዎች በመነሳት-

1. በተለይ ፡-

1.1.ከገዢው ፓርቲ የማስፈራሪያ ፕሮፖጋንዳ ራሳችሁን ነጻ አውጥታችሁ በተጠራው ስብሰባ ላይ ተገኝታችሁ ለነጻነታችሁና መብታችሁ ያላችሁን ቀናኢነት የገለጻችሁ፣ የቱንም መስዋዕትነት የመክፈል ዝግጁነታችሁን ላረጋገጣችሁ ኢትዮጵያዊያን ያለንን አድናቆት እየገለጽን ትግላችን ጥያቄዎቻችን እስኪመለሱና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ አውን እስከሚሆን ተከታታይና ቀጣይ ስለሆነ የተጽዕኖ አድማሳችሁን አስፍታችሁ የበለጠ ተሳታፊ ይዛችሁ በትግሉ እንድትቀጥሉ፤

1.2. በህዝብ ኃይል የሚተዳደሩ መገናኛ ብዙሃን ሙሉ በሙሉ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ውለው ገዢውን ፓርቲ ከማገልገል አልፈው በሠላማዊ ትግል የፖለቲካ ኃይሎች ላይ አፍራሽ ፕሮፖጋንዳ በሚነዙበት ወቅት የህዝብ ዓይንና ጆሮ ሆናችሁ የምታገለግሉ በአገር ቤትና በውጪ የምትገኙ የመገናኛ ብዙኃን ሁሉ ስላደረጋችሁልን ድጋፍ እያመሰገንን፣ በቀጣይም በህዝብ ወገናዊነታችሁ በመቀጠል ከጎናችን እንድትቆሙ፤

1.3.ገዢው ፓርቲ ከገባበት ከፍተኛ ሥጋትና ፍርኃት ለመውጣት እየተከተለ ካለው የሴራ ፖለቲካ ወጥቶ የህዝብ ጥያቄዎችን በመመለስ ራሱን ለለውጥ እንዲያዘጋጅ፤

1.4. እንደ ፖሊስ ኃይል ያላችሁ የመንግሥት አስፈጻሚ አካሎች ለገዢው ፓርቲ ሴራ ራሳቸውን በማጋለጥ ከሠላማዊ የመብት ታጋዮች ጋር አላስፈላጊ ግጭት ውስጥ እንዳይገቡና ከህገ መንግሥቱና ከህዝብ ጎን ቆመው ከህግና ታሪክ ተጠያቂነት ራሳቸውን ነጻ እንዲያወጡ፤

2. በአጠቃላይ፡-

2.1. የትግሉ ዓላማ የአገርና የህዝብ፣ቀዳሚ ባለቤቱም እኛው – ነጻነታችንም በእጃችን ነውና በጋራ ‹‹በቃን›› በማለት ለነጻነት በምናደርገው ትግል በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጪ የምትገኙ ኢትዮጵያዊያን በሙሉ አገራችንን ከወረደችበት አዘቅት እኛም ከሚደርስብን ጭቆናና ሥቃይ ለመውጣትና የዜግነት ክብራችን ለማስመለስ በሚደረገው ቀጣይና ተከታታይ ሠላማዊ ትግል ለምናቀርበው ጥሪ አዎንታዊ ምላሽ በመስጠት ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ፤

2.2. የትግሉ ባለቤት ሁላችንም በመሆናችን ብቻ ሣይሆን ‹‹አገራችን ላለችበት ምስቅልቅል ሁኔታ በተናጠል ተመጣጣኝና ዘላቂ መፍትሄ መስጠት ከአንድ ፓርቲ አቅም በላይ ነው›› ከሚለው የጋራ ድምዳሜያችን አንጻር በትብብሩ ያልታቀፋችሁ በተለይም በሂደቱ ከጅምሩ እስከ መጨረሻው ተሳትፋችሁ የስምምነቱን ሰነድ ያልፈረማችሁና እስከዛሬም ያልተመለሳችሁ እንዲሁም ሌሎች ሠላማዊ ዲሞክራቲክ የተቃውሞ ፖለቲካ ፓርቲዎች ከጋራ ትግሉ እንድትቀላቀሉ፤
2.3. የዓለም አቀፉና የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት መንግስታት ተለዋዋጭና አላፊ፣ አገርና ህዝብ ግን ቋሚ ናቸውና በግንኙነታችሁ የህዝብ ለህዝብ ዘላቂ ጥቅምንና የአገራትን ታሪካዊና ፖለቲካ ግንኙነት ከግምት በማስገባት ሰልፋችሁን ከህዝቡ ጎን እንድታደርጉ፤

ጥሪያችንን ስናስተላልፍ በእኛ በኩል ለአገራችንንና ህዝቧ የምናደርገው የጋራ የተባበረ ትግል የሚጠይቀንን መሥዋዕትነት ሁሉ ለመክፈል ያለንን ዝግጁነትና ቁርጠኝነት በድጋሚ እናረጋግጣለን!

የተቀናጀና የተባበረ ህዝባዊ ሠላማዊ ትግልን አሸንፎ በሥልጣኑ የዘለቀ አንድም አምባገነናዊ መንግሥት ዓለማችን አታውቅም!!

ስለሆነም እናሸንፋለን!!

ሕዳር 08 ቀን 2007 ዓ.ም

አዲስ አበባ

ምንጭ:- ነገረ ኢትዮጵያ

Filed in: Amharic