>
5:13 pm - Wednesday April 19, 6017

መቆሚያ ያጣው የእጩዎች ግድያ!!! ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን)   የተሰጠ የሐዘን መግለጫ!

መቆሚያ ያጣው የእጩዎች ግድያ!!!

 
ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን)   የተሰጠ የሐዘን መግለጫ!

በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመተከል ዞን ወንበራ ወረዳ ለክልል ምክር ቤት እጩ የነበረው አባላችን በሪሁን አስፈራው ላይ በመተከል ዞን በለስ ልዩ ቦታው ካርባር ግድያ የተፈፀመበት መሆኑን እያሳወቅን ፓርቲያችን በአባላችን ግድያ የተሰማውን መሪር ሐዘን ይገልጻል።
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን) በቀጣይ ግንቦት 2013 ዓ.ም በሚደረገው አገራዊ ምርጫ ተሳታፊ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በሁሉም የአገራችን ክፍሎች በርካታ እጩ ተወዳዳሪዎችን ያስመዘገበ መሆኑ ይታወቃል። ይሁን እንጅ በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች በመንግስት ካድሬዎች በአባላቶቻችን ላይ ተደጋጋሚ ዛቻ፣ እስር እና ድብደባ እየፈተፀመ ይገኛል። በተለይ በኦሮሚያ ክልል እና በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች በስፋት እንዲሁም አልፎ አልፎ በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች የአባላት ማጉላላት፣ እስር እና ድብደባ እየደረሰ ይገኛል ።
በተደጋጋሚ ጊዜ ሰላማዊ ዜጎችን ከመጨፍጨፍ እስከ ጅምላ ማፈናቀል የዘለቀው የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቀደም ብሎ የክልሉ ካድሬዎች የተወዳዳሪዎች ምዝገባ እንዳይሳካ ለማድረግ ብዙ ጥረት ያደረጉ ቢሆንም በምርጫ ቦርድ ትብብር ምዝገባው ሊከናወን ችሏል። ከዚያ በኋላም የምርጫ ተወዳዳሪ እጩዎቻችን ቅስቀሳ ላይ በነበሩበት ወቅት ያለመከሰስ መብታቸውን በጣሰ መልኩ አስሮ በማጉላላት እና በማስፈራራት እጩዎቻችን ላይ አላስፈላጊ ጫና ለማሳረፍ ሞክሯል።  ይህ ሁሉ አልበቃ ያለው ቤኒሻንጉል ጉሙዝ መንግስት የፀጥታ ሰወች ለክልል ምክር ቤት እጩ ተወዳዳሪያችን የነበረውን አቶ በሪሁን አስፈራው ከቻግኒ ወደ በለስ ጉዞ ላይ እያለ ልዩ ቦታው ካርባር ላይ ግድያ ፈፅሞበታል።
አብን ግድያው ፖለቲካዊ መሰረት ያለውና ንቅናቄው በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለመገደብ ሆነ ተብሎ የተደረገ እንደሆነ ያምናል። ለዚህም የወንድማችንን ግድያ ጨምሮ በአሶሳ እና አካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ በእጩዎቻችንና አመራሮቻችን ላይ ሲፈፀሙ የነበሩ ምክንያት አልባ እስሮችና ወከባዎች ከበቂ በላይ አስረጂዎች ናቸው።
በመላው ኢትዮጵያ በተለይም የግጭት ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ምርጫ ሲቃረብ መሰል ግድያዎች፣ ጭፍጨፋዎች፣ ማፈናቀሎችና ወከባወች እንደሚኖሩ ደጋግመን ለመንግስት ያሳሰብን ቢሆንም ከስሕተቱ መማር ያልፈለገው መንግስት ዛሬም ድረስ ዜጎች በጅምላ እና በተናጥል ሲገደሉ፣ ሲፈናቀሉ እና ኃብት ንብረታቸው ሲወድም በዝምታ እየተመለከተ ይገኛል። ፓርቲያችን አብን ይህ ጉዳይ ቀስ በቀስ አገር የሚያፈርስ አደገኛ ጉዳይ መሆኑን ይገነዘባል። ሰላማዊ እና ፍትኃዊ ምርጫ ይደረጋል የሚለውን የዜጎች ተስፋም ከወዲሁ ያጨለመ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሰናል። አስቸኳይ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድም አበክሮ የሚታገልበት ይሆናል።
ስለሆነም አብን መንግስት በምርጫ እጩ አባላችን ላይ የተፈፀመውን ግድያ በአስቸኳይ እንዲመረምር እና ገዳዮችን ለፍርድ እንዲያቀርብ በአንክሮ እየጠየቀ፤ መሰል ነገሮች አፋጣኝ ምላሽ ተሰጥቶባቸው ለምርጫ እጩዎቻችን ተገቢው የጸጥታ ከለላ በመንግስት በኩል እንዲሰጥ እናስገነዝባለን። ይህ ሳይሆን ቀርቶ በእንዝላልነት ተጨማሪ ሕይወት ቢጠፋ እና አገራችን ወዳልተፈለገ ምዕራፍ ብትገባ ተጠያቂነቱ ሙሉ ለሙሉ መንግስት የሚወስድ መሆኑን ከወዲሁ አብክረን ማሳሰብ እንወዳለን።
ለሰማዕቱ ወንድማችንና ጓዳችን አቶ በሪሁን አስፈራው ቤተሰቦችና ለመላው የንቅናቄያችን አባላትና ደጋፊወች መጽናናትን እንመኛለን።
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን)
ሚያዝያ 1፣ 2013 ዓ/ም
አዲስ አበባ፥ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ!
Filed in: Amharic