>

ጊዜው የኢትዬጵያና የሕዝቧ ጠላቶች የመጨረሻው መጨረሻቸው ብቻ ነው !! (አንድነት ለኢትዮጲያ)

ጊዜው የኢትዬጵያና የሕዝቧ ጠላቶች የመጨረሻው መጨረሻቸው ብቻ ነው !

አንድነት ለኢትዮጲያ 
 
* ተነሳ ተራመድ ክንድህን አበርታ 
ለአገር ብልጽግና ለወገን መከታ ።
ሀሁ ኢትዬጵያ ትቅደም !!!!
ሀሁ ኢትዬጵያ ትቅደም !!!!
 ኢትዬጵያ ትቅደም !!!!
 

 
ብሔርና ሐይማናታችን ብርቅዬ እሴቶቻችን ናቸው። ከኢትዬጵያችን ጋር የሚጋጩብን ሳይሆኑ የኢትዬጵያችን ውብ ቀለማት ናቸው ።
 በየብሔር ስማችን  እየተጠራን በቋንቋና በባሕላችን እያጌጥን  በኢትዬጵያ ጥላ ስር አብረን  ደምቀን  እንኖራለን። ሙስሊም ፣ ክርስትያን…  እያልን እንጠራበታለን ፣ እንሰግድበታለን ፣ እንጸልይበታለን ፣ እንቀራበታለን። እንሰብክበታለን ፣ እናስቀድስበታለን።
ይኸን ተሰባስበን የምናደርግባት ጥላ ከለላችን ዋርካችንና ታሪካችን ኢትዬጵያ ነች። በምንናገረው ቋንቋ ፣ ባሕልና እሴቶች አገራችንን አብረን እንገነባበታለን እንጂ አንባላበትም። ጠላት በጥፋታችን ይድላው ብለን ያዘጋጀልንን መርዝ ተግተን የምንጠፋ ተስፋ ቢሶች ፈጽሞ አይደለንም።
በምንማልክበት የአገራችንን ሰላም በመለኮታዊ ሀይል እገዛ ጭምር እንገነባበታለን እንጂ ያለ እምነት አላማችን ለጠላት ሲሳይ አድርገን ለጥፋታችን መሳሪያ አድርገን  አንገብርም።
 ያለ ኢትዬጵያ እነዚህ ውብ ቀለማቶቻችን እንደሚረግፉ እናውቃለን ።  በሐይማኖትና በብሔር  ጫፍ ተነታርከን እንድንረግፍ የሚሹ ፣ የሚያቅድና የሚራወጡ የውጭና የውስጥ ቅጥረኞቻቸው በእርግጥ  በከንቱ ደከሙ። ዛሬም ሆነ መቼም ኢትዬጵያ በደገሱላት ድግስ ስትጠፋ አያዩም። አመጻቸው ተመልሶ በአናታቸው ይነዳል።ይበላቸዋል። ያጠፋቸዋል።
 እነሱ እንደ ብናኝ ሲጠፉ እናያለን እንጂ ስንጠፋ መቼም አያዩንም። አንድ ጊዜ ሊያጠፉን ቢሹ አንድ ሺህ አንድ ጊዜ ሞተን ጥፋታቸውን በጥፋታቸው እንማግደዋለን።  አንድ ሺህ ጊዜ ለጥፋታችን ቢዘምቱ አንድ መቶ  አስር ሚሊየን ጊዜ ሞተን በሞታችን የጥፋት ሀይሎችን ቀብረን አገራችንን ለቀጣዩ ትውልድ እናስረክባለን።  ዘላለማዊ እናደርጋታለን። ኢትዬጵያችን ክብራችን ነች። ሕልውናችን ነች። እናታችን ነች።
ተነሳ ተራመድ ክንድህን አበርታ
ለአገር ብልጽግና ለወገን መከታ።
አንድነት ለኢትዮጲያ ስንል
ይህ ሀረግ ወይም መሪ ቃል የተለመደ ሊመስል ይችላል። ይሁን እንጂ መለመዱ አንድ ነገር ሆኖ ከደማችን ጋ መዋሀድ፣ በመንፈሳችን ውስጥ መንቀልቀል አለበት።
አንድነት ለኢትዮጲያ ሰሞነኛ መፈክር ወይም ወቅት ጠብቆ የሚመዘዝ ሀረግ አይደለም። ኢትዮጲያ እንደ ሀገር ታፍራ እና ተከብራ መኖር ካለባት ኢትዮጲያዊ አንድነት ዜጎች ሁሉ ልባቸው ውስጥ የሚገነቡት ሀውልት፡ ባንደበታቸው የሚቀባበሉት ጥኡም ዜማ መሆን አለበት
ኢትዮጲያን እንደ ሀገር ቀጥላ፣ ባኩሪ ታሪኮችና ገድሎች አሸብራቃ፣ በታሪክ ድርሳናት አንቱታን ተጎናፅፋ እኛ ጋ እንድትደርስ ያስቻላት ጉልበት ከላይ የማያንቀላፋው ፈጣሪዋ ጥበቃ ከታች የልጆቿ አንድነት ነው። ትውልድ ለትውልድ እየተቀባበለ ይረካከባት ዘንድ አንድነት የግድ ነው። ሀገር አደራ ነች። አደራ ተብለን ስንቀበላት፡ አደራችንን አክብረን ለልጆቻችን ማስከብ ብቻ ሳይሆን፡ ልጆቻችን የኛን አደራ በዘመናቸው ጠብቀው ለልጆቻቸው በአደራ እንዲያስረክቧትም ጭምር አደራ በማለት ነው። አደራው ደምና ስጋ ለብሶ ምሉእ የሚሆተው ደሞ በሀገራዊ አንድነት ነው።
ዛሬ የምናያቸው ምስቅልቅሎች ሲጠቃለሉ የብሄራዊ አንድነት መሳሳት ውጤቶች ናቸው። የውስጥና የውጪ ጠላቶቻችን ኢትዮጲያ ላይ ለመረባረብ ዛሬን የመረጡበት ምክንያትም፡ የውስጥ አጀንዳዎቻችንን ለመፍታት ከመቀራረብ ይልቅ፡ ተለያይተን ካብ ለካብ እንደ እባብ መተያየትንና መጠነቋቆልን በመምረጣችን ነው። ከትልቋ ኢትዮጲያ ህልውናና ክብር ርቀን፡ እጅግ በወረዱ አጀንዳዎች ላይ ስንወዛገብ፡ እንደ ሀገር አፅንቶ ያቆመን አውድ ይነቃነቃል። ባደራ የታሰርንለትን ትልቁን ማንነታችንን ጥያቄ ውስጥ ባስገባነው ቁጥር፡ ሀገራችን የቆመችባቸው ምሶሶዎች መሰረት ይናጋል።
ሀገር በልጆቿ ተሰብስባ የምትመሰጠር፣ በማያቋርጥ ቅብብሎች በስጋ እና በነብስ ጭምር ተዋጅታ የምትፀና እንጂ ተበትና የምትለቀም ጥሬ አይደለችም። በማንኛውም ሁኔታ ስለ ሀገር ቀጣይነት ቅድመ ሁኔታ ሊቀመጥ አይገባም። በራሳችን ውስጥ ሀገራችንን ማዬትና፡ በሀገራችን ውስጥ ራሳችንን ማዬት፡ የማይነጣጠሉ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፆች ናቸው። ራሳችን ውስጥ ሀገራችንን ስናይ ካለ ሀገር ባዶ መሆናችንን፡ በሀገራችን ውስጥ ራሳችንን ስናይ ደሞ፡ ሀገራችን ካለኛ ምንም መሆኗን እንረዳለን። እኛ ስንል የሞቱትንም፡ ያለነውንም፡ መጪውንም ጨምረን ነው። ለሀገር መሞት ሀገርን ለማንበር ከሆነ፡ ሀገር እስካለች ድረስ አልሞትንም ማለት ነው።ለሀገር መሞት ማለት ነፍስን በሀገር ህልውና ውስጥ ማስቀጠል ማለት ነው።  ለሀገር  መሞት አቅቶን፡ ከመሬት በላይ መኖር ግን፡ ከህያውነት ሊቆጠር አይችልም፣ “መኖር ማለት በደምሳሳው መተንፈስ መቻል ነው” እስካልተባለ ድረስ።ለሀገር መኖርም: ለሀገር መሞትም “ምሉእ” ለሆነ ዜጋ ሁሉ የመንፈስ ብፅእና ነው። ለልጆቻችን በክብር የምናስረክባት፣ እኛም የምንኖርባት የቀደሙ በኩራቶቻችን አፅምም በሰላም የሚያርፍባትን ሀገር፡ ተረኛ በሆንንበት ዘመን ሁሉ፡ በሀገራዊ አንድነት እስከ ህይወት መስዋእትነት ከፍለን፡ ልናነብራት የሚያስችለን ግዴታ፡ ከውጪ ሳይሆን ከውስጥ የሚመነጭ መሆን አለበት። አገር የጋራ ቤታችን መሆኗ ላይ ከተግባባን፣ ለኢትዮጲያ አንድነት እያንዳንዳችን መክፈል ስለሚገባን ዋጋ መጠራጠጠር የለብንም። የሰው ልጅ “ነብስ”የከበረ ነው። መከፈል ካለበት ግን ለሀገር ብቻ መሆን አለበት። ቀደምቶቻችን ዘር፣ ጎጥ፣ ሀይማኖት ሳይለዩ ባንድ ጉድጓድ እየተቀበሩ፣ ቀያቸውን ሰብላቸውን፣ ቤተሰባቸውን ጣጥለው እንደ ወጡ የቀሩት፡ ለዚህች ተአምረኛ ሀገር ህልውናና ክብር ነው።
ኢትዮጲያዊ አንድነት ከመፈክርነት በላይ ሀገራዊ ፅንሰ ሀሳብ መሆን አለበት። ለሀገሩ እስከ መቃብር ደጅ ለመጓዝ የማያመነታ ትውልድ ለመፍጠር ሀገራዊ አንድነት በሁላችንም አይምሮ ውስጥ መንቀልቀል አለበት።  አንድነትን ባንደበታችን የምናነበንበው ብቻ ሳይሆን፡ ልባችን ላይ የምንነቀሰውና መንፈሳችን ውስጥ የምናውለበልበው ሰንደቅ እንዲሆን ያስፈልጋል።
ዛሬ ሀገራዊ አንድነታችን በመሳሳቱ በርካቶች ምሳር ይዘው ኢትዮጲያን ሊጠርቧት ተጠራርተዋል። አስተሳስሮ ያቆየን መስተጋብራችን እንደ ዳንቴል እየተረተረ ነው። ከፅሞናና ከአስተውሎ ስለራቅን የመከራ ፅዋ ሊያስጎነጩን በመሀከላችንም በዙሪያችንም ተሰግስገዋል። የተከበራችሁ የሀገሬ ልጆች እስኪ መፃኢውን አስተውለን ይሄንን ክፉ ቀን በመላ እናሳልፈው። ይህ መላ ኢትዮጲያዊ አንድነት ነው።
እስኪ ሁላችንም በዚህ መንፈስ እንመላለስ። ኢትዮጲያዊ አንድነት መስተሰሪያ አድርገን እንቀባበለው። መተሳሰሪያ ፀበል አድርገን እንራጨው። እኔ ይሄንን ህብረ ቃል የህይወቴ ታላቁ መርህ ለማድረግ ከአሁኗ ቅፅበት ጀምሮ ከአይምሮዬ ጋ ኪዳን አስሬያለሁ! ሀገሬን አንዳች ነገር አድርጊልኝ ብዬ ላላጨናንቃት በልቤ እፀናለሁ። እዳዋ በበረታ  ጊዜ ዋስ ሆኜ ልታደጋት እምላለሁ። በአንድነቷ ውስጥ ተስፋዋ እንደሚሸመን አምናለሁ። እስዎስ?
UnityForEthiopia 
አንድነት ለኢትዮጲያ
ኢትዬጵያ ታሸንፋለች !!!
ጠላቶቿ እንደ ብናኝ ይጠፋሉ !!!
Filed in: Amharic