>
5:13 pm - Tuesday April 19, 0631

በጤነኞችና በዕብዶች መካከል በሚደረግ ጦርነት የድሉ ባለቤት እንጂ የጉዳት መጠኑ አይታወቅም (ይነጋል በላቸው)

በጤነኞችና በዕብዶች መካከል በሚደረግ ጦርነት የድሉ ባለቤት እንጂ የጉዳት መጠኑ አይታወቅም

ይነጋል በላቸው (yinegal3@gmail.com


እንደመግቢያ፡- በቀደመው ትግሮሙማም ሆነ በተከተለው ኦሮሙማ ውስጥ የሚታዩት ዋና ዋና ተዋንያንና የዕልቂት አበጋዞች ዘሩን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት በፈረንጅኛው አጠራር “ጄኖሳይድ” ካወጁበት የአማራ ነገድ ተዋልደውና ተጋብተው፣ ከደሙም ከባህሉም ተዋርሰው ሳለ አንዳች አፍራሽ ኃይል ሽው ብሎባቸው ግማሽ አካላቸው ላይ መዝመታቸው ይገርማል፡፡ ከፊል ጎጃሜው መለስ ዜናዊ እና ከፊል ወሎዬው አቢይ አህመድ ለዚህ አባባል ጥሩ ምሣሌ ናቸው፡፡ የሁለቱም ሚስቶች አማሮች ናቸው፤ (“ሊያውም” ብል የሚያኮርፍ ይኖር ይሆን?)- አዎ፣ ሊያውም ጎንደሬዎች – ምን አገባኝ ማንም ቢያኮርፍ፡፡ በመሆኑም ሁለቱም ደማቸው ከአማራ ደም ጋር ተዋህዷል፡፡ ለነገሩ በዓለማችን አንድም ንጹሕ ዘር የሚባል እንደሌለ ብዙ ጥናቶች ይገልጻሉ፤ በዚያ ላይና ከዚያም በፊት በሃይማኖት ረገድ ካየን ሁሉም ከአዳምና ከሔዋን የመጣ በመሆኑ አንዱ ለሌላው ባዳ አይደለም፡፡ ቋንቋና ባህል ለሰው ባዕድ ናቸው – ሰው ለሰው ግን አይደለም፡፡

አቢይ ሲደመር ሽመልስ ይሆናል አቢሽመል፡፡ የአቢሽመል የኦሮሙማ ፍልስፍና በፈጠረው ሁከት አሁን አገር እየታመሰች ነው፡፡ አቢሽመላውያን መነሻ ዓላማቸው ምንም ያህል ትክክለኛ ሊሆን ቢችል እንኳን ያን ዓላማ ለማሣካት የሚጠቀሙበት ዘዴ ወይም ሥልት ግን ስህተት ብቻ ሣይሆን የሰማይንም የምድርንም ህግጋት አንድም ሳያስቀር የሚጥስ ትልቅ ጥፋት ነው፡፡ የአቢይሽመላውያን ፍላጎት ድንበር የለሽ ከመሆኑ አንጻር ይመስላል ፍላጎታቸውን እውን ሊያደርጉበት የሚከተሉት መንገድም እንደዚሁ ወሰን አልባ ሆኖ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ተቸግረናል፡፡ ግርዛትን የማያውቀው የአቢሽመሎች ገደብየለሽ የሥልጣንና የሀብት ፍላጎት በትምህርት እንኳን ሰከን ሊል አልቻለም፡፡ እንጂማ የእውነትም ይሁን የፌክ፣ የይስሙላም ይሁን የምር … ቢኤውንም፣ ማስተርሱንና ዶክትሬቱንም ታቅፈውታል – ለአንዲት ዳቦና ለአንድ የሥልጣን ወንበር ሲሉ የአራት ዓመት ሕጻን ከማረድ ግን አላቆማቸውም – በአንድ በኩል እነሱም ተረግመው ነው፡፡ ከሃይማኖትና  ከጤናማ  ኅሊና መውጣትና የለዬለት ዐውሬ መሆንን መርጠውት አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ወንድሞቻችን በዐረመኔነት ከአይሲሶችም በልጠው እነሱን ሳይቀር እያስደመሙ ይገኛሉ፡፡ አይሲሶች ሕጻናትን ሲያርዱ አልታዩም፤ አልቃኢዳዎች ሴቶችን በአደባባይ ሲረሽኑ አላየናቸውም፡፡ አይሲሶች አልጋ ላይ የተኛ የ80 እና የ90 ዓመት በሽተኛ አዛውንት አንገት ሲቀሉ አልታዘብናቸውም፡፡ አልቃኢዳዎች የነፍሰ ጡርን ሆድ ዘርግፈው ሽልን አውጥተው ጉበቱን ሲበሉ አላየንም፡፡ ከዚህ አንጻር አቢይሽመሎች አዲስ ታሪክ እያስመዘገቡ ነው፡፡

የአቢሽመል ኦሮሙማ ከሴቶችና ከሕጻናት ጋር የሚያጧጡፈው “የተጋጋለ ጦርነት” በስፋት ቀጥሏል፡፡ በዚህ ‹ጦርነት› አቢሽመሎች የማይጠቀሙበት የመሣሪያ ዓይነት እንደሌለ እያየንም እየሰማንም ነው – በአንዲት ድሃ አገር ሁሉ በጁ ሁሉ በደጁ የሆነው የአቢሽመል  ጥምር የክልልና የፌዴራል መንግሥት ከኔና ካንተ ኪስ በግብርና መሰል አርዕስት ስም በሚዘርፈው ገንዘብ አንዱ ብቻ በአራት መቶ ሽህ ብር የሚገዛ ስናይፐር ለሚያሰለጥናቸው በብዙ ሽዎች የሚቆጠሩ የጦር አባላቱ በማስታጠቅ አማራን እየረፈረፈ ይገኛል፡፡ በዓለም የጦርነት ታሪክ ያልተመዘገበ፣ ታራጅን አንበርክኮ በሣቅና በፈገግታ በመሞላት የመደሰትን ጭራቃዊ ታሪክም እያስመዘገቡ ነው – ወንድም በወንድሙ ላይ እንዲህ ሲጨክን በምድራችን ታሪክ የመጀመሪያው ሳይሆን አይቀርም፡፡ አንዱ አለቃቸው ታዬ ደንደኣም “ይህን ግድያ ትዘግቡና ወይም በዚህ ግድያ ላይ መግለጫ ታወጡና የ2011 ዓመተ ምሕረቱን የባሕር ዳር ‹አሳዛኝ› የግድያ ታሪክ ታስደግሙናላችሁ” እያለ ደንገጡሮቹን በማስፈራራት ላይ ነው፡፡ ዕብሪት እንደሽሮ እንዴት እንደሚያንተከትክ እያየንና ዕብዶቹም ብዙ ታሪክ እየሠሩ ናቸው፡፡

መነሻየን አልረሳሁም፡፡ በወቅቱ የአነጋገር ቅኝት ሃሳቤን ስገልጽ አትቀየሙኝም መቼም፡፡ እናም አማራ ውስጥ ዕብድና ሆዳም የሞላውን ያህል ትግሬውም፣ ኦሮሞውም፣ ሌላውም ውስጥ እንደዚሁ ዕብድና ወፈፌ አይጠፋምና የሀገራችን ታሪክ ከድጡ ወደማጡ እየሆነ የእግዜሩን ተዓምር ብቻ ክፉኛ በሚያቁነጠንጥ ትግስት እንድንጠብቅ ተገደናል፡፡ እንጂ እዚህ መዓት ውስጥ የከተተን እንደሚባለው የጭቆናና የገዢ-ተገዢነት ታሪክም አይደለም፤ የቁጥር መበላለጥም አይደለም፤ የተረኝነት ጉዳይም አይደለም፡፡ መሆን ያለበት መሆን ስላለበት እንጂ፡፡ በነገራችን ላይ የአማራው ክልል አመራሮች እየፈጸሙት ያለው ግፍ ታሪክ ይቅር የማይለው ነው፡፡ የሚታረዱ ወገኖችን ቀድመው ከያሉበት በማውጣት በክልሉ ቦታ ፈልገው እንደማስፈር እንደምንም ያመለጡትንና ወደአማራ ክልል የገቡትን አማሮች ማባረራቸውን ተያይዘውታል፡፡ እነዚህ ሰዎች ወዴት ይሂዱ? ቀድሞውም ከትግራይና ከወሎ ሳይወዱ በግዳቸው በደርግ የሠፈራ ፕሮግራም ወደ ወለጋና ቤንሻንል ጉሙዝ የሄዱት በመንግሥት እንጂ በራሳቸው ፈቃዳቸው አልነበረም፡፡ አሁን እዚያ መኖራቸው ካልተፈለገ መመለስ እንጂ የምን ጭፍጨፋ ነው? 

ገዳዮች በአቀዋሽና በአደንዛዥ ኦፒየም-መሰል ፕሮፓጋንዳ ለረጂም ጊዜ ተበክለው ለዚህ ዕልቂት ኅልው ግልጠት ምቹ ወቅት ሲጠብቁ ከርመዋል፡፡ የአቢሽመል ዕቅድ አራማጆችም አመራሩን እያመረሩ መጥተው አሁን አሁን ዙሩን እጅግ አክርረውታል – ጊዜያቸውም ነው፡፡ ያሰለጠኗቸው ገዳዮችም እንደሰው ሳይሆን እጅግ ዐረመኔና ጨካኝ ከሚባለው የአንስሳት ዝርያም በከፋ መልኩ አማሮች ላይ ብርታታቸውን እያሳዩ ነው፡፡ አማሮች ምንም እንኳን በቁጥርም በውጊያ ብቃትም ከነዚህ ዐረመኔዎች ባይተናነሱም ያደጉባቸው ሃይማኖታዊና ሞራላዊ እንደዚሁም ባህላዊ ዕሤቶች በብዙ መልኩ ቀፍድደው ስለያዟቸው እንደአጥፊዎቻቸው ጭካኔን በቀላሉ መለማመድና የሚወርድባቸውን የግፍ ዶፍ መከላከል አልቻሉም – ባህልና ሃይማኖት ጠቃሚ የመሆናቸውን ያህል ጎጂም ናቸው – የሚደርስብህን በደል የሚመጥን ምላሽ ለማዘጋጀትና ለማስወንጨፍ ራሱ ብዙ ዓመታትን ሊፈጅብህ ይችላል – ሊያውም እንደጠላቶችህ ወደመናኛ አስተሳሰብ ከወረድክ፤ ምክንያቱም ጠላትህ የመጣብህ አንተ ባላሳብከውና ባልጠበቅኸው እንዳመጣጡ ለመመለስም ኅሊናህ በማይፈቅደልህ አስቀያሚ መንገድ ናውና፡፡ ትግስትህን እንደፍርሀት የሚቆጥረው ጠላትህ ያንተን መዘናጋት እየተጠቀመ በላይህ ላይ ይጠዳዳብሃል፤ ብዛትህና የሚያውቅልህ ጀግንነትህ በምን እንደተጀቦነ ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ይሰለጥንብሃል – ወያኔም ያደረገችው ልክ እንደዚሁ ነበር ፤ አየህ! የተቃዋሚህን ደካማ ጎን ማወቅ ጦርነቱን  ቀድመህ ቢያንስ በግማሽ ያህል እንዳሸነፍክ ያህል ነው፡፡ እንጂ ከ40 እና 50 ሚሊዮን የማያንሰው አማራ ለነዚህ ዕብዶች የሚሆን አንድ ሽህና ሁለት ሽህ “አስማረና ስንዴው” አጥቶ አይደለም፡፡ “የጊዜ እንጂ የሰው ጀግና የለውም” መባሉ አንዳንዴ ትክክል ነው፡፡ 

ዕብድና ጤነኛ ጦርነት አይገጥሙም በመሠረቱ፡፡ ከገጠሙም ዕብዱ የእውነት፣ ጤነኛው የቀልድ በሚመስል ሁኔታ ለተወሰነ ጊዜ ጤነኛው እየተጎዳ ጦርነቱ ይቀጥልና ጦርነቱ በርግጥም የእውነት መሆኑን በቆይታ የሚረዳው ጤነኛው ወገን ሲያመር አዲስ ታሪክ መፈጠሩ የማይቀር ነው፡፡ ግፍና በደል ሲበዛ የተኛን ይቀሰቅሳል፤  የዛለ ጉልበትንና ወኔንም ያድሳል፡፡ በዚያ ላይ ለምሳሌ የአዲስ አበባ ወጣት በፍቅርና በሰላማዊ መግባባት፣ በሥርዓትና በወግ ተኮትኩቶ እንደማደጉ (“ስም ይቀድሞ ለነገር” እንዲሉ ያ አንካሣ የሚሉት ወፈፌ የብልጽግና ዕጩ “አዲስ አበቤዎች የሴተኛ አዳሪ ልጆች ናችሁ” እንዳለን ሳይሆን) ዕብድ ሲመጣበት ይሸሻል እንጂ ፊት ለፊት ለመግጠም ድፍረቱም ዝግጅቱም የለውምና ዕብዶች ለተወሰነ ጊዜ ትልቅ ጉዳት ማድረሳቸው የሚጠበቅ ነው፡፡ ከዚህ አኳያ አዲስ አበቤዎችና መሰል የተዘናጉ አካባቢዎች መጠንቀቅ ያለባቸው ከዚህ መሠረታዊ ነጥብ አንጻር ነው፡፡ የማትመጣጠነው ጠላት በማትገምተው ሁኔታ ሲገጥምህ አስቸጋሪ ነው፡፡ (አንድ ባለነፍጥ – በዱላ እያባረረው የነበረውን ባላጋራውን “ከዚህ ሬሣ ገላግሉኝ!” ብሎ ያካባቢ ሰዎችን የለመነው ወዶ አልነበረም፡፡)

ተነበብኩም አልተነበብኩም መሰናበት አለብኝ፡፡ ዕብዶቹ ዶን ኪሾቶች – አቢሽመላውያን በወለጋና በመተከል ከፍተኛ ጀብድ እየፈጸሙ የኦሮሙማ አቀንቃኞችን በማስደሰትና አብዛኛውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን በማስለቀስ ላይ ይገኛሉ – ለተወሰነ ጥቂት ጊዜም ቢሆን፡፡ ይህ በዚህ አይቀጥልም፡፡ ፀጉርን ሹርባ ተሠርቶ ከሕጻናትና ከሴቶች ጋር የሚደረግ የጦር ሜዳ ውሎ ያበቃና ከወንዶች ጋር የሚደረገው ጦርነት ይቀጥላል፡፡ ያኔም ከታላቅ ይቅርታ ጋር አንዴ ብቻ ልጠቀመው በምፈልገው አነጋገር ሴትና ወንዱ ይለያል፡፡ ጊዜውም ብዙ ሩቅ አይደለም፡፡ እንግዲህ ገዳይም መግደልህን ቀጥል፤ ሟችም ሰማዕትነትህን ግፋበት – ቢቻልህ ግን ለማምለጥ ሞክር፡፡ የመጨረሻ አሸናፊ ማን እንደሆነ ግን ሁሉም ይወቀው፡፡ ስለሆነም ጤነኛ ነን የምትሉ ኦሮሞዎች፤ ጤነኛ ነን የምትሉ አማሮች፤ ጤነኛ ነን የምትሉ ሌሎች ዘውጎች ሁሉ የጊዜውን መቅረብ አጢኑ፤ ከዕብዶች ዕጣ ፋንታም ላለመቋስ ለራሳችሁ ተጠበቁ፡፡ በነፈሰው ሁሉ አትንፈሱ፡፡ ሙታንን በአግባቡ ቅበሩ፤ የሚጎዱትን አክሙ፤ የሚራቡትን መግቡ፤ የማይበላ ሀብትና ንብረት ከማጋፈርም ተጠንቀቁ፡፡ በበሽታ አታትርፉ፡፡ በወገናችሁ ጉዳት አትክበሩ፡፡ ኑሮን በማጦዝ ወገናችሁን ለተደራራቢ ስቃይ አትዳርጉ፡፡ ባለቀ ሰዓት እንኳን አእምሯችንን ለመጠቀም እንሞክር፡፡ በየሀኪም ቤቱ የሚሰማው ዘረፋ ይዘገንናል፡፡ አንዳንዶቹማ ያከሙህ ሳይሆን ነፍስህን የሰጡህም ይመስላቸዋል፡፡ ልትወልድ ለሄደች ሴት ልጁን ራሳቸው ፈጥረው የሚያስረክቡ የሚመስሉ ገንዘብ አምላኪዎች ሞልተዋል፡፡ በተለይ በኮሮና የምትነግዱ አደብ ግዙ፡፡….

እንደመውጫ፡- በሽተኞች ሀኪም ያስፈልጋቸዋል፡፡ ዕብዶች ወይንም ንኮች የአእምሮ ህክምና ስፔሻሊስት ድጋፍን ይሻሉ፡፡ ከዚህ አንጻር በአእምሮ ህመም ምክንያት ሕጻናትንና ሴቶችን ባልተወለደ አንጀት የሚፈጁ አቢሽመሎችን መርዳት ተገቢ ነው፡፡ ሰው ሳይታመም የሦስትና የአራት ዓመት ሕጻን ገድሎ አይጨፍርም፡፡ መታከም አለባቸው፡፡ ማራቅና መጥላት የለብንም፡፡ እኛን እንደነሱ ሆነን ማሰብ አለብን፡፡ አንድ ሰው ጤንነት ካልራቀው በስተቀር መሰል ፍጡራንን በእሳት አያጋይም፤ በጥይት አይቆላም፤ በሳንጃም አንገትን አይቀላም፡፡ ስለሆነም በተለይ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ጤናማነትና ተሰሚነት ያላችሁ አባላት ለምሣሌ ወዳጄ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሣና መምህር ታዬ ቦጋለ ለየት ያለ የማስተማር ሥልት በመንደፍ ከመስመር የወጡና ለዲያብሎስ የጨለማው መንግሥት ያደሩ ወንድሞቻችንን ምከሩ፡፡ በጀመሩት መንገድ ጥፋት እንጂ ልማት እንደማያስገኙ ይነገራቸው፡፡ ሰውን በማረድ ምንም ዓይነት ዓላማ ግቡን አይመታም – ለጊዜው የመታ ቢመስልም እንኳ ዘላቂነት የለውም፡፡ ከተመለሱ እሰዬው፡፡ ካልተመለሱ መሞከራችን በፈጣሪም በሰውም ያስከብረናልና ኪሣራ የለውም፡፡ ሠላም፡፡

Filed in: Amharic