>

ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን መኖር የሚችል ማሰብ ያቆመ ብቻ ነው! አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)

ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን መኖር የሚችል ማሰብ ያቆመ ብቻ ነው!

አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)

martyrof2011@gmail.com


ማሰብ ሲባል ዓይነቱ ብዙ ነው፡፡ ስለፍቅረኛህ፣ ስለሚስትህ/ስለባልሽ፣ ስለሥራህ፣ ስለወደፊት ሕይወትህ ወዘተ. ልታስብ/ቢ ትችላለህ/ያለሽ፡፡ ሰው ሆኖ የማያስብ የለም፤ ሃሳቡ ቢለያይም፡፡

እኔ የምለው ማሰብ ግን ከራስ ባለፈ ስለሰው ልጅና ስለዓለም፣ ስለማኅበረሰብና ስለአገር ኅልውና በአጠቃላይ ከአንድ ጤናማ ዜጋ የሚጠበቀውን ጤናማ የማሰብ ችሎታ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ካየነው በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ መኖር የሚችል ሰው ከራሱ የዕለት ከዕለት ኑሮ ባለፈ ስለሀገርም ሆነ ስለሕዝብ ምንም ማሰብ የማይችል ልቦናው የተደፈነና አእምሮው የዛገ መሆን አለበት፡፡ አእምሮው የሚሠራና ልቦናው የሚያመዛዝን ከሆነ ተራው የዕለት ከዕለት ኢኮኖሚያዊ ሕይወት የሚከብደው ከመሆኑም ባሻገር በሀገር ጉዳይ በሚገጥመው ጭንቀት ብቻ ኅሊናውን ስቶ ሊያብድም ይችላል፡፡

በበኩሌ እንደ ኤርየል ሻሮል መሆንም ያምረኛል፡፡ ኤርየል ሻሮል የእስራኤል ፕሬዝደንት የነበረና ከአምስት ዓመታት ለሚበልጥ ጊዜ ሰመመን ውስጥ ቆይቶ ይህችን ዓለም የተሰናበተ ሰው ነው፡፡ ለበርካታ ዓመታት ሳይሰማና ሳይለማ በህክምና ድጋፍ ሰመመን ውስጥ ገብቶ ሲረዳ ነበር፡፡ እኔም ልክ እንደዚያ ሰው ሰመመን ውስጥ ገብቼ ኢትዮጵያ ስትነሳ ብነቃ ደስታው አይቻለኝም፡፡ የሚገርም ዘመን ላይ ነን፡፡

ከተማ ይፍሩ የተባለ የደርግ ዘመን አንድ ሚንስትር ለሥራ ጉዳይ ይመስለኛል ከሀገር ወጥቶ በዚያው በጠፋበት ወቅት እንዲህ ብሎ ነበር ይባላል – “Fly out of Ethiopia while you can!” እኔ ደግሞ “እንደዚያ ማለትስ አሁን ነበር” እላለሁ፡፡ የአሁኑ ሁኔታችን ለመጥፋት ከመመኘትም የዘለለ ነውና፡፡

  1. “ለአዲስ አበባ ፋንዲያ ያስፈልጋታል” የሚል የሀገርም በለው የክልል ኩታራ መሪ ጋር ተቻችለህም ይሁን ተስማምተህ እንዴት ትኖራለህ? በአንድ በኩል “ስንኖር ኢትዮጵያ፣ ስንሞትም ኢትዮጵያ” እያለህ በሌላ በኩል በምሥጢር በሚያደራጃቸው ዐረመኔና ቦቅቧቃ ታጣቂዎቹ አማራን ከያለበት ከሚያሳርድ የአናኮንዳ ዝርያ እባብ ጋር እንዴት በአንድ ሀገር ዜግነት አብረህ ትኖራለህ? በአንድ በኩል “ኢትዮጵያ ሱሴ ናት” እያለህ በሌላ በኩል ከሶማሊያና ከአርሲ፣ ከባሌና ከወለጋ ኦሮሞን በገፍ እያመጣ የአዲስ አበባን ቀደምት ነዋሪዎች በማፈናቀል የከተማዋን የሕዝብ አሰፋፈር በቅጽበት ከሚለውጥ አጭበርባሪ ጋር እንዴት ኅብረት ይኖርሃል? “ተረኝነት የለም” እያሉህ ከሞላ ጎደል ሁሉንም የሥልጣንና የሀብት ምንጭ በቂ ትምህርትና ዕውቀት በሌላቸው የሀገር ቤት ኦሮሞዎች ከሚያሲዙና አንተን በገዛ ሀገርህ ባይተዋር ከሚያደርጉህ “ሰዎች” ጋር እንዴት አብረህ ትኖራለህ? ጉድ ነው ዘንድሮ! …
  2. አንዲት ከተማ የሁለት አገሮች ዋና ከተማ የምትሆነው በምን ሥሌት ነው? አንዲት ከተማ በሁለት ስም እየተጠራች ሰሚን ግራ የምታጋባበት ሀገር ያለው በየትኛው ክፍለ ዓለም ነው? አዲስ አበባን ለማጥፋት እየተካሄደ ያለው የኦሮሙማ ሁለገብ ዘመቻ መቼና በማን ይቆማል? ዝርዝሩ ብዙ ነው! አሁን አሁን እኮ አዲስ አበባ ላይ እየኖርክ የሀገር ባቤትነትና የዜግነት ስሜት ሊኖርህ በፍጹም አይችልም፡፡ እኔ ለምሣሌ አዲስ አበባ ከመጣሁ 40 ዓመት ከአራት ወር ሆነኝ – ጃዋር ሳይወለድ ማለት ነው፡፡ አዳነች አቤቤም ሳትጸነስ፡፡ አቢቹም አንቀልባ ላይ እያለ መሆኑ ነው … ተመልከት! አሁን እነዚህ አስተዳደግ የበደላቸው የኦነግና የሕወሓት ሥሪቶች እኔን ከአዲስ አበባ ሊያስወጡ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፡፡
  3. አክራሪ ኦሮሞ በሦስት ዓመታት ውስጥ ብቻ የናጠጠ ሀብታም እየሆነ ነው፡፡ ስማቸውን እንኳን አስተካክለው የማይጠሯቸው “ሪቮሉሽን” እና “ሐመር” የተሰኙ ቅንጡ ዘመናዊ መኪኖችን እያሽከረከሩ ምድርን ተጠይፈው ሰማይ ወጥተዋል፡፡ የአዲስ አበባ መሬት በኦሮሞ እየተወረረና እየተቸበቸበ ሌላው ሙልጭ ሲወጣ እነሱ በአንድ አዳር መክበርን ሥራየ ብለው ተያይዘውታል፡፡ በዚያ ላይ ቀበሌውን፣ ወረዳውን፣ ከፍተኛውን …. ሁሉንም እነሱ ስለያዙት የዘረፉትን ሀብትና ንብረት ህጋዊ መደላድል ለመስጠት አይቸገሩም፡፡ በበታችነት ስሜት ራሱን ያጎሳቆለ ሰው ከሚያደርሰው ጥቃት አምላክ ይጠብቅ፡፡ በሙስናው ረገድም ዐይን ያወጡ ሆነዋል፡፡ ለምሣሌ አሥር ሽህ ብር ለምታገኝበት ጉዳይ 50 ሽህ ብር ጉቦ ቢጠይቁህ ከዕውቀት የጸዱ በመሆናቸው ስታስረዳቸው “ኡሱ ያንቴ ጉዳይ ነው” ብለው ያመናጭቁሃል እንጂ አይረዱህም ማለትም አይገነዘቡህም፡፡ ለመጽናናት ያህል ሀገር አለች እንላለን እንጂ ከፈራረሰች ቆየች፡፡
  4. አዲስ አበባ ልትፈነዳ ነው፡፡ መኪና መንገዶች በሁሉም ዓይነት ተሸከርካሪዎች ጢም ብለዋል፡፡ በሥራ ሰዓትም ከሥራ ሰዓት ውጪም መኪናና ሰው እንደጉድ ይርመሰመሳል፡፡ የሁሉም ዜጎች መሸሻ አዲስ አበባ እንደመሆኗ ከየትም አቅጣጫ በሚተሙ ዜጎች እየሞላች ልትፈነዳ ተቃርባለች፡፡ የትራፊክ እንቅስቃሴው ከመኪናና ከሰው መንገዶች አቅም በላይ ሆኗል – የመንግሥትና የፖለቲከኞች ትኩረት ግን የሕዝብ ችግር ላይ ሳይሆን ሥልጣን ላይ ሆነና ነገሩ ሁሉ “የነብር ዐይን ወደ ፍየል፣ የፍየል ዐይን ወደ ቅጠል” እንዲሉ ሆኖ ሀገራችን ወደማይቀርላት አርማጌዴዖን እያመራች ይመስላል፡፡ የመኪኖችን ሞዴል በተመለከተ አንዳንዶቹ ዘመናዊ መኪኖች አሜሪካና አውሮፓ ስለመኖራቸውም ያጠራጥራል፡፡ ሀበሻ ማንነቱን የሚያሳውቀው፣ ጀብዱን የሚያሳየው ቆንጆ መኪና በመያዙ፣ ቆንጆ ቤት በመሥራቱና ቆንጆ ሚስት በማግባቱ/ሀብታም ባል በማግባቷ ይመስላል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ መኖርህን በሚያጠራጥር ሁኔታ  የሀብት ውድድሩ ጦፏል (በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ድሃ አፈር ደቼ እየበላ የእህቱን ሠርግ በ40 እና 50 ሚሊዮን ብር ድል አድርጎ የሚደግስ ደንቆሮ ሀብታም የምታገኘው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነው፤ የከበረው ደግሞ ድሆችን እንደትኋን ደማቸውን መጥጦና ስንጥቅ አትርፎ በጥቂት ዓመታት ውስጥ መሆኑን ስትረዳ ይበልጥ ያምሃል)፡፡ በዚህ መሀል አብዛኛው ድሃ በቁሙ መቀመቅ እየገባ ነው፡፡ በየደቂቃው ሽቅብ የሚወነጨፈው ሰው ሠራሹ የኑሮ ውድነት ደግሞ በቃላት አይገለጽም፡፡ ዛሬ ሁለት መቶ ብር የገዛኸውን ዕቃ ከሦስት ቀናት በኋላ ከአንድ ሽህ ብር በላይ ልትጠየቅበት ትችላለህ፡፡ ሁለት ምርጫ አለህ – ካለህ መግዛት፤ ከሌለህ ትተህ መሄድ፡፡ የነዳጅ ጭማሬው ነገር አይነሳ፡፡ እንዲያም ሆኖ ዕጥረት አለ መሰለኝ የቤንዚን ወረፋው ዙሪያ ጥምጥም ነው፡፡ በትራፊክ ጭንቅንቁ ምክንያት አንድ ቦታ ተገትረህ ወይም በጥቂት ኪሎ ሜትሮች መንፏቀቅ መኪናህ ላፍ የሚያደርጋትን አንዲት ሊትር ቤንዚን ከማደያዎቹ ሽቀባ ጋር ከ30 ብር በላይ ገዝተህ ምን ጉዳይ እንደምታከናውን ይታይህ (ህጋዊው ዋጋ አሁን 25.86 ነው)፡፡ ነዳጁና ዶላሩ በኑሮ ውድነቱ ላይ ትልቅ ጫና አላቸው፡፡ … መተዛዘንና መተሳሰብ በመዝገበ ቃላት ውስጥም የሉም፤ ጠፍተዋል፡፡ ዐውሬነት ነው የነገሠው፤ ጅብነት ነው እግር አውጥቶ እየተራመደ የሚታየው፡፡ ዋጋን የሚያረጋጋና ለምሥኪን ዜጎች “አለሁላችሁ” የሚል መንግሥትም ሆነ የግል ድርጅት የለም፡፡ ሃይማኖቱም የተዘፈቀው በብልጽግና አስተሳሰብ ነው፤ መንግሥትም የብልጽና ወንጌል ተከታይ ነው – ሁሉም ድሃ ጠል ናቸው፡፡ አቅልን የሳተ የሥጋ ሩጫ በሀገራችን ተንሰራፍቶ ኅሊናና ነፍስ ጫጭተዋል፡፡ የዘር ሐረግ ከሰውነት በልጦ፣ ነገዳዊ የበላይነት ጥርሱን አግጥጦ ሀገርና ሕዝብ መቅ እየወረዱ ነው፡፡ ያሳዝናል፡፡ 
  5. የመንግሥት ባለሥልጣናት በደሞዝ ስለማይኖሩ አቶ ደሞዝን ከነመፈጠሩ ረስተዋል፡፡ የመንግሥት ሠራተኛ በሁለት ሽህ ደሞዝ የ30 እና 40 ሽህ ኑሮ እንዲኖር እየተገደደ ነው፡፡ ሀገራችን በኳስ አበደች የውቂው ደብልቂው ዕብደት ላይ ትገኛለች፡፡ ኩንታል ነጭ ጤፍ አምስት ሽህ ብርን ካለፈ ሰነበተ፤ አንድ ሊትር ዘይት 100 ብርን ከዘለለ ቆዬ፤ ስንቱን አንስተን እንዘልቀዋለን? ሕዝብ ርስ በርሱ ተባልቶ ሊያልቅ ነው፡፡ ሮሮ ቢበዛም መንግሥትም እግዚአብሔሩም ከተደበቁበት ብቅ ብለው የድሃን ጩኸት ሊሰሙ አልቻሉም፡፡ ህግ የለም፡፡ ሥርዓት የለም፡፡ የተፈጥሮ ህግ ብቻ እስካሁን አልተዛነፈም – ይነጋል፤ ይመሻል፡፡ ፀሐይ በምሥራቅ ትወጣለች፤ በምዕራብ ትገባለች፡፡ በተረፈ የመንግሥት ህግ ብሎ ነገር የለም፤ በገንዘብና በዘረኝነት፣ በአምቻና ጋብቻ፣ በዘመድ አዝማድና በትውውቅ የማይደረመስ ህግና የወንጀል ወይም የፍትሐ ብሔር አንቀጽ የለም፡፡ ገንዘብህን ይጭነቀው እንጂ ገድለህ በሟች ልታስፈርድ ትችላለህ፡፡ ሰውና ገንዘብ ካለህ ቀጭን ጌታ ነህ፡፡

ለማንኛውም ኢትዮጵያ ውስጥ መኖር ከፈለግህ ጭንቅላትህን ሣጥን ውስጥ ቆልፈህ እንደመጋጃ ከብት ማንም የሚጭንህን ለመሸከም ፈቃደኛ ሆነህ መገኘት አለብህ፡፡ አለበለዚያ አስባለሁ ካልክ ማምሻህን ወይም ዘገየህ ቢባል በማግሥቱ ራስህን የምታገኘው ደህና ዘመድ ያለህ ከሆንክ አማኑኤል ሆስፒታል አለበለዚያ በሚቀርብህ ባቡር መንገድ ላይ ራቁትህን ሆነህ የትራፊክ እንቅስቃሴን በበጎ ፈቃደኝነት ስታስተናግድ ነው – ማንም ላይሰማህና ትዕዛዝህን ላያከብር፡፡ ኢትዮጵያ ይህን መስላልሃለች፡፡ “እግዜር ሲቆጣ ሽመል አይቆርጥም፤ ያደርጋል እንጂ ነገር እንዳይጥም” ይባላል፡፡ የኛም ነገር እንደዚያው ነው፡፡ እንትናቸውን በቅጡ ያልጠረጉ ውሪና ዘረኛ መሪዎችን ጫንቃችን ላይ አሸከመንና ገደል መግባታችን ግድ ሊሆን ነው፡፡ አዳሜ ታዲያ ቢጨንቀው ወይም የበላው ቢያብላላው የአጋንንቱን ልዑክ እያመለከ “ጊዜ እንስጠው፤ ወዶ አይደለም፤ ታስሮ ነው፤ አላሠራ ብለውት ነው….” እያለ ራሱን ያታልላል፤ ሌላውንም በዶሮ-ማታ ሊያሞኝ ይሞክራል፡ የተደገሰልን የሚለበልብና የሚሰነፍጥ የበርበሬና የሰናፍጭ ግብዣ ከፊት ለፊታችን አለ፤ መልካም ድግስ እንዲሆንልን ለሁላችን እየተመኘሁ ለዛሬ ተሰናበትኩ፡፡ አሻም!

Filed in: Amharic