>

መንግሥት ያገለላቸውን እምዬ ምኒልክን ህዙቡ በድጋሚ አንግሷቸው ውሏል...!!! (ዘመድኩን በቀለ)

መንግሥት ያገለላቸውን እምዬ ምኒልክን ህዙቡ በድጋሚ አንግሷቸው ውሏል…!!!

ዘመድኩን በቀለ

… ትናንት የካቲት 23/2013 ዓም በመላ ኢትዮጵያ ሃገራችን ታላቁን የዓድዋ የድል በዓል ህዝብና መንግሥት በአቋምም በበዓል ማክበሪያ ቦታም ተለያይተው ሆድና ጀርባ ሆነው እንደምንም አክበረውት አልፏል። መንግሥት ተብዬው ተረኛው የዐቢይ አህመድ የኦሮሙማ አፓርታይድ መንግሥት በዓሉንና የበዓሉን መንፈስ በመክፈል፣ በማደብዘዝ፣ እንዲሁም በድሉ መሪ በእምዬ ምኒልክ ጥላቻ ሰክሮ አክብሮታል። ዐቢይ አህመድ ከዚህም ባሻገር የምኒልክን ቤተ መንግሥት እንደወረሰው ሁሉ የምኒልክንም ድል በይፋ ወርሶ የምኒልክን ፎቶ ከቴሌቭዥን መስኮቶች፣ ከከተማ፣ እስከ ፌደራል ድረስ አሳግዶ እና አስወርዶ በምኒልክ ፎቶ ምትክ የራሱን ፎቶ አሰቅሎ፣ አሸክሞም ብቻውን ለመንገሥ ሞክሮ ውሏል።
… ፀረ ኢትዮጵያው እና አፈ ቅቤ ልበ ጩቤው ዐቢይ አሕመድ የምኒልክን ምሥል ብቻ ሳይሆን ስማቸውም ጭምር በመንግሥት ሚድያ እንዳይጠራ ያደረገ እና ከ125 ዓመት በኋላ እቴጌ ጣይቱንና ንጉሠ ነገሥት ምኒልክን ለማፋታት የሞከረም መሰሪ ነው። እሱ ምን ያውቃል? የካድሬዎች፣ የሽመልስ ጥፋት ነው የሚሉ አሉ። ነገር ግን እሱ ሳያውቅ የሚደረግ አንዳችም ነገር አይኖርም። ለማንኛውም የትናንቱ የዓድዋ በዓል እንኳንም ከምርጫው በፊት ሆኖ የዐቢይ አህመድን ድብቅ ማንነት ግልጥልጡን አውጥቶ ርቃኑን ያስቀረ በዓልም ሆኖ አልለፈ። ኢትዮጵያውያን በሙሉ ማለት በሚያስችል መልኩ በሰውየው ድብቅ ሴራ በግነው እና ነቅተውም ያለፉበት በዓልም ሆኖ ነው በዓሉ ያለፈው።
… በሌላ በኩል ደግሞ መላው የአዲስ አበባ ህዝብ ከቤቱ የቀረ የሌለ እስኪመስል ድረስ ግልብጥ ብሎ ወደ አደባባይ በመውጣት የድል በዓሉን ሲያጣጥምም ውሏል። የአገዛዙን ነውር በግጥም፣ በቀረርቶ፣ በሽለላ፣ በፉከራ፣ በፉተታም ሲገልጥ ውሏል። ” ዴ በል አንዴ” ን ልብ ይሏል። መንግሥት ያገለላቸውን እምዬ ምኒልክን ህዙቡ በድጋሚ አንግሷቸው ውሏል። ደስ የሚል ውሎ፣ ደስ የሚል ቀንም ነበር።
… ሌላው መልእክት የአዲስ አበባ ነዋሪና የዲሞግራፊ ነዋሪዎችም በሚገባ የተዋወቁበት እና የተያዩበት ትከሻ ለትከሻም የተለካኩበትም በዓል ሆኖ ነው ያለፈው የትናንቱ የዓድዋ የድል በዓል። ዲሞግራፊ በአበል መስቀል አደባባይ ብቻውን ሲያቅራራ አዲስ አበቤ በአራዳ ሰፈሩ ፦
ቢመችሽም ባይመችሽም
ሸገር ፊንፊኔ አይሆንልሽም…  ሲል ውሏል።
… ከትናንቱ የዓደዋ በዓል አከባበር ተነሥተን በመጪው ምርጫ ከሱሉልታ፣ ከሰበታ፣ ከቡራዩ፣ መንግሥታችን ተነካ ብለው ለምርጫ በአይሱዙ ተጭነው ከሚመጡት በቀር የአዲስ አበባ ዕጣ ፈንታ ምን እንደሚመስልም በትናንቱ የዓድዋ የድል በዓል ላይ በግልጽ ተመላክቷል። (ምርጫው የተበላ ዕቁብ ካልሆነ በቀር ማለት ነው)።
ቪቫ ምኒልክ  !! 
… ቪቫ ጣይቱ  !! 
… ብራቮ አዲስ አበባ  !! 
… እምጷ ኢትዮጵያዬ !!
Filed in: Amharic