>

እንቅልፋም እና ገልቱ አምባሳደሮቻችን ሲያንኮራፉ ....!!!! (ሙክታሮቪች ኡስማኖቭ)

እንቅልፋም እና ገልቱ አምባሳደሮቻችን ሲያንኮራፉ ….!!!!

ሙክታሮቪች ኡስማኖቭ

አስቸኳይ ፩
በውጪ የኢትዮጵያ ኢንባሲዎች አሁን ሀገራችን የተደቀነባትን የተቀናጀ የጁንታው ቅሪቶች እና ተከፋዮቻቸው ዘመቻ የመመከት ፍላጎት ፈፅሞ የላቸውም። አምባሳደሮቹ ዲፕሎማሲ የማያውቁ የጎሳ ውክልና፣ የአኩራፊ ፖለቲከኞ መለማመጫ እና የጡረታ ቦታቸው እንደሆነ ነው ቦታውን የሚያስቡት። ከስር የሚሰሩ ከዘበኛ እስከ ፀሀፊና ብሎም ኦፊሰሮች ጁንታው የህገወጥ ንግዱን እንዲያሳልጡ የመደባቸው የጁንታው የውጪ ክንፍ ናቸው። በሌለ ዶላር በአስራሺዎች ዶላር እየከፈልን በኢትዮጵያ ላይ የሚዘምቱት እነሱ ናቸው። በሌላ አነጋገር እየከፈልናቸው ፀረ ኢትዮጵያ ዘመቻቸውን እየደገፍን ነው። በቲዊተር ኢትዮጵያን የሚወጉት እነሱ ናቸው። መንግስት በሀገር ታክስ ከፋዮች ገንዘብ ሀገርን እያስጠቃ ስለሆነ ከፍተኛ ማጣራት አድርጎ እርምጃ ሊወስድ ይገባል።
አስቸኳይ ፪
በአውሮፓ በርካታ አምባሳደሮች አሉን። የአውሮፓ ህብረት የውጪ ጉዳይ ሚኒስተሮች ጉባኤ ትናንት ኢትዮጵያን ሲኮንን አመሸ። ይህ ህብረት የስፔን ግዛት አካል የሆነቸው ካታሎኒያ ለመገንጠል ስታምፅ መሪዋን አሳልፎ የሰጠ ነው። በሀገር አንደነት ቀልድ አያውቅም። በኢትዮጵያ ጉዳይ ግን ወደ ጁንታው ያደላ አቋሙን የሚኮንን አንድም አምባሳደር አልታየም። እኛ በኑሮ ውድነት ስንሰቃይ ቤተሰቦቻቸውን በእኛ ዶላር የሚያስተምሩ፣ የተንደላቀቀ ህይወት የሚመሩ አምባሳደሮች ለሽ ብለው ተኝተዋል። ወታደር ለሀገሩ በየየጦር ሜዳው ተዋድቆ ያገኘውን ድል እንዴት በዲፕሎማሲ እንሸነፋለን። እንዴት? ዲፕሎማት የሀገር ወታደር ማለት አይደለምን? ከሽፈናል። እውነት ይዘን ተዋርደናል። ያሳፍራል፣ ያሳዝናል!
አስቸኳይ ፫
የጁንታው ርዝራዦች ትግራይን እንደ ሀገር ቆጥረው በዘመቻቸው “ሀገረ ትግራይ” “ትግራዊያን” እያሉ ዘመቻ ላይ ናቸው። አንድም አምባሳደር ትግራይ በሰሜን ጫፍ የምትገኝ ትንሽ የሉኣላዊቷ ኢትዮጵያ አንድ ግዛት መሆኗን፣ በትግራይ ክልል 5 ሚሊየን ህዝብ እንደሚኖር፣ ኢትዮጵያ የ120 ሚሊዮን ህዝብ ሀገር መሆኗን፣ በትግራይ ክልል ተጋሩ፣ ኩናማ፣ ኢሮብ፣ አፋር፣ አማራ እና 80 የሚደርሱ ብሄርብሄረሰቦች በስራም ሆነ በኑሮ ከ3000 አመታት በላይ የሚጋሩት ክልል መሆኑን እንዴት እያስረዳ አይሞግትም?
አስቸኳይ ፬
Tigray Genocide የሚል ዘመቻ በኢትዮጵያ ላይ ጁንታውና ተከፋይ ነጭ መሸጦ ቡችሎቹ ዘመቻ ሲከፍቱ፣ አምባሳደሮቻችን በአለማቀፍ ሰብዓዊ መብት ድርጅቶች የተረጋገጠ የጁንታው የዘር ማጥፋት ታሪክን በመዘርዘር፣ ከአርባጉጉ እስከ ኦጋዴን፣ ከጋንቤላ እስከ ሲዳማ ሎቄ፣ ከእንቁፍቱ እስከ የቅርቡ ሻሸመኔ፣ መተከል እና ማይካድራ በወጉ የተሰነደ የትህነግን የዘር ፍጅት ነውር በተጨባጭ ማስረጃ እየሞገቱ፣ የዘር ፍጅት ሊቃውንትነታቸውን እያስረዱ ለሀገራቸው አይሞግቱም? በህግ ማስከበር ዘመቻው ንፁሃንን ላለመግደል ሰራዊታችን ያደረገውን ጥንቃቄ እየጠቃቀሱ ለምን አይሞግቱም? በዶላር እየተከፈላቸው ሀገራቸው እየደማች እንቅልፋቸውን ይለጥጣሉ?
አስቸኳይ ፭
የሀገር መከላከያ ያጠቃ፣ ማይካድራ ላይ ሺዎችን የጨፈጨፈ፣ ከኢትዮጵያ ፖለቲካ በተቃውሞ ከስልጣን የተተፋ አካል በጦር ሜዳ በሁለት ሳምንት ተሸንፎ በዲፕሎማሲ ድምፁ እየተሰማ ያለው በኢምባሲዎቻችን ደካማነት ነው። መሪዎቹ ተገድለው፣ የተረፉት እጅ ሰጥተው፣ የቀሩት እንደ አይጥ ጉድጓድ ለጉድጓድ እየተሽለኮለኩ እንዴት የዲጂታሉ አካላቸው ኢትዮጵያን ያስጨንቃል?
አምባሳደሮቹ ፈርጠም በማለት ለየሀገሮቹ ከ120 ሚሊየን ህዝብና ከጥቂት እየታደኑ ያሉ ወንጀለኞች ምረጡ እያሉ ለሀገር አይቆሙም? አይቆሙም ወይ? ዝም ብላችሁ ታነባላችሁ መልሱልኝ ሀገር በዶላር እየከፈለቻቸው ምንድነው ዱንዛዜ!
አስቸኳይ ፮
•”መሀመድ_አል_አሩሲ” በዚህ ሳምንት ከ 27 በላይ ታላላቅ የዓረብ ሚዲያዎች በመቅረብ ስለ ኢትዮ-ሱዳን ድንበር፣ ስለህዳሴ ግድብ በተመለከተ የተሳካ ክርክሮችን ከታዋቂ የዓረቡ ዓለም ተንታኞች ጋር ተከራክሮ በብቃት ተወጥቷል::
•ብቻውን ባለፉት ሁለት ዓመታት ከ500 በላይ በታላላቅ የዓረቡ ዓለም ሚዲያ ቀርቦ በእጅ ስልኩ በቀጥታ ስርጭት ሞግቷል፣ ተከራክሯል።
• በቀን ከ10 በላይ ታላላቅ የዓረቡ ዓለም ጣቢያዎች ጋር ኢትዮጵያን ወክሎ ሲሞግት፣ ሲከራከር ይውላል፣ ተከራክሮም ብዙዎችን በማሳመን ዝና የተቸረው የዘመኔ ሀገር ወዳድ ሰው ነው። ማሜ እናመሰግናለን!
Filed in: Amharic