>

ፍርድ አደላዳዩ የጦሩ ጌታ አባ መላ ሀብቴ ዲነግዴ....!!! (ሔቨን ዮሐንስ)

ፍርድ አደላዳዩ የጦሩ ጌታ አባ መላ ሀብቴ ዲነግዴ….!!!

ሔቨን ዮሐንስ

ፊታውራሪ ሀብተ ጊርጊስ ዲነግዴ (አባ መላ) ከፈተኛ የአመራር ችሎታ፣ የተዋጊነትና የጦርነት ጥበብ አዋቂነት፣ የፖለቲካ ጠቢብነት እንዳላቸው ይነገርላቸዋል፡፡ ከዚህ ሁሉ በተጨማሪ ደግሞ አስገራሚ የፍርድ አዋቂ እንደበሩና #አጼ_ምኒሊክም ብዙ ጉዳዮችን ወደ እሳቸው መምራት ይቀናቸው እንደነበር በርካታ ድርሳናት ይመሰክራሉ፡፡ ፕሮፌሠር ባህሩ ዘውዴ የዘመናዊ ኢትዮጵያ ታሪክን በጻፉበት መጽሐፋቸውም ሆነ “ሀብቴ አባ” መላ በሚል ርዕስ የሕይወት ታሪካቸውን በጻፉበት መጽሐፍ ከዝነኛ የፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ ዲነግዴ ፍርዶች የተወሰኑትን አካፍለውናል፡፡
በጣም የሚገርመውን አንድ ከእንግሊዞች ጋር የተፈጠረ ውዝግብ ላይ ፊት ሀብቴ የሰጡትን ፍርድ ላጋራችሁ :-
እንግሊዝ ኬንያን ቅኝ ስተገዛ ወደ ኢትዮጵያ በመስፋፋት ደቡቡን እና ደቡባዊ ምሥራቅ ኢትዮጵያን ለመውረር ያሰበችውን ትልም በአጼ ምኒሊክ አዝማችነት ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ የጀግናው ራስ ጎበናን ጅምር ይበልጥ በመስፋት፣ በተለይ ቦረና ከተቀረው ኦሮሞ ተቆርጦ እንዳይወሰድ የአውሮፓን ወራሪ እግር በእግር ተከትለው የኢትዮጵያን ዳር ድንበር አስከብረዋል፡፡ አጼ ምኒሊክም ለሀብተ ጊዮርጊስ በመስጫ ግዛታቸው ላይ ነፃ ያወጧቸውን የደቡብ ግዛቶችን ሲዳሞን ጨምሮ ቦረናን እንዲገዙ አጽድቀውላቸዋል፡፡
ታድያ ፊት ሀብቴ በድንበር አቅራቢያ የነበሩትን ገበሬዎች ግዛታቸውን ይከላከሉ ዘንድ እንዳስታጠቋቸው ይነገራል፡፡ በአንድ ወቅት ታድያ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ሥር የነበሩት የኬንያ ገበሬዎች የኢትዮጵያ ድንር ጥሰው ይገባሉ፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ገበሬዎች ነገሩን ዝም ብለው አልተመለከቱትም፡፡ ገበሬዎቹ ላይ ተኩስ ከፍተው ድንበራቸውን ለማስከበር ጥረት ያደርጋሉ፡፡ ከወድያ በተነሣ አጸፋዊ ጥቃት ምክንያትም ነገሩ ጠንክሮ አንድ የእንግሊዝ ኮለኔል ይሞታል፡፡ በእንግሊዞቹ ክስ መሠረት በርካታ የኬንያውያ ከብቶችም ይዘረፋሉ፡፡ ይህ አቤቱታ አዲስ አበባ ባለው የእንግሊዝ ቆንስላ በኩል አቤቱታው ለአጤ ምኒሊክ ይደርሳል፡፡ አጤ ምኒሊክ እንደ ወትሮው ሁሉ ይሄንንም ጉዳይ “አባ መላ ይመለከተው” ብለው ወደሱ ይመራሉ፡፡
በፊታውራሪ ችሎት እንግሊዞች ክስ ብቻ ሳይሆን የካሳ ውሳኔ ሀሳብም ይዘው ቀረቡ፤ ይዘውት የቀረቡት:-
1. ስለ ሞተባቸው ኮለኔል ከሳ እንዲከፈላቸው
2. የተዘረፉባቸው ከብቶች እንዲመለሱላቸው እና
3. ለከብቶቻቸው የግጦችና የውኃ ቦታ ከኢትዮጵያ ግዛ እንዲሰጣቸው እና መሰል ጥያቄ ነበር።
ይህንንም ጥያቄ አባ መላ #ሀብቴ ክሱን አድምጣው ሲያበቁ “ምንም ችግር የለውም! ጥያቄዎቻችሁ ተገቢዎች ናቸው፣ ያላችሁት ሁሉ ይደረጋል” ሲሉ ፈረዱ ይባላል፡፡ በዚህ ጊዜ እንግሊዞች ሲደሰቱ ፊታውራሪ ሀብቴ ለፍርዱ ተፈጻሚነት ግን አንዳንድ ቅድመ ሁኔታዎች እንደሚያስፈልጉ ገልጸው፤ የአስተዋይነታቸውን እና ኢትዮጵያዊ አርበኝነታቸውን የሚያሳይ የሚከተለውን አሏቸው።
“የኛ ተኳሾች ለገደሉት ኮሎኔላችሁ ከሳ የምንከፍለው እናንተ ከሀገሩ ወስዳችሁ እዛ ለገደላችሁት ልዑላችን ለዓለማየሁ ቴዎድሮስ ካሳ ስትከፍሉ ነው፡፡ ስለ ተዘረፉ ከብቶች ደግሞ እናንተም ከመቅደላ የዘረፋችኋቸውን ቅርሶችና ሀብቶቻችንን ትመልሳላችሁ፡፡ መሬትን በተመለከተ እኛም እንሰጣችኋለን፣ ለኛም ከአውሮፓ መሬት ያስፈልገናል እና አስቡበት” ብለው ሸኟቸው!
ዛሬስ በአገሩ የማይደራደር ሰው ዲፕሎማት አለን? ስለ አገሩ ሲጠየቅና ሲጠይቅ የማያዳግም መልስ የሚሰጥና ተፅኖ የሚፈጥር ብልህ ድፕሎማት አለን? ሌላው አንዳንድ የኦሮሞ ብልፅግና አመራሮች ከፍተኛ ስልጣን ይዘው ከብሔር አቅማዳ ወጥተው አገራዊ እሳቤ ማሰብ ለምን ተሳናቸው? ኦሮሞ ነኝ ከሚል ወጥተው ታሪክ የሰሩ እነ ጉበናን እነ ፊታውራሪ ሀብቴን መላ እና የአገር ፍቅር ለምን መልበስ አልፈለጉም? ነው ታሪካቸውን በቅጥ ሳያቁ ነው ወሬ የሚያደቁት በተለይ በተለይ እነ ታየ ደንደአ በሚያስገርም ሁኔታ ስልጣናቸውን ለአክቲቭስትነት ሲያወርዱት አይተናል ስለ አገራቸው በንቃት ሲሰሩ አላየንም እና ለምንድን ነው ይህን ያህል የትውልድ ክፍተት የኖረው? የሚል ጥያቄን ያስነሳል። በጥቅሉ እናስተውል፣ ታሪካችንን እንመርምር ስለ አገራችን ምን እንስራ ብለን የሚቀድመውን እናስቀድም ለማለት ነው!
Filed in: Amharic