>

ከ ሃምሳ ሺ በላይ አባላትና ደጋፊዎች  የሚሳተፉበት የጎዳና ላይ ትርዒት በአምስት ፓርቲዎች ጥምረት ተዘጋጀ...!!!

ከ ሃምሳ ሺ በላይ አባላትና ደጋፊዎች  የሚሳተፉበት የጎዳና ላይ ትርዒት በአምስት ፓርቲዎች ጥምረት ተዘጋጀ…!!!
ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት 
አዲስአበባ 
ጉዳዮ:-የምርጫ ቅስቀሳ የመክፈቻ ስነስርዓት ዝግጅትን ስለማሳወቅ

እንደሚታወቀው በኢትዮጵያ የብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት የምረጡኝ ቅስቀሳና የምርጫ ዘመቻ የካቲት 8/2013ዓ.ም በይፋ ተጀምሯል። ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ /ባልደራስ/ አማራ ብሔራዊ ንቀናቄ/አብን/ ፣ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት/መኢአድ/ ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዋ አንድነት ፓርቲ/አብአፓ/ ከየካቲት 14-16/2013ዓ.ም ድረስ የሚቆይ የምርጫ ቅስቀሳ የመክፈቻ ስነስርዓት አዘጋጅቷል ስለሆነም 1ኛ.የካቲት 14/2013ዓ.ም በ8፡00 ስዓት(ከስዓት) ከላይ የተዘረዘሩት ከጽ/ቤታቸው መነሻ ለማድረግ የጉዞ መስመሩ 4 ኪሎ አዲስ አበባ፣በፒያሳ፣ በቸርቸር ጎዳና፣ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ወደ ብሔራዊ ቲያትር አድርጎ በለገሀር በማድግ ወደ መስቀል አደባባይ የሚደርስ ከ50.000/ ሃምሳ ሺ / በላይ የፓርቲያችን አባላትና ደጋፊዎች በመታጀብ የጎዳና ላይ ትርዒትና የቅስቀሳ ጉዞ የምናደርግ ሲሆን በዚህም ትርዒትና ጉዞ ላይ ፡- 1ኛ. የምርጫ ቅሰቀሳ የመክፈቻ ፕሮግራሙ ደማቅ እና ለህብረተሰቡ ተደራሽ እንዲሆን በማርሽ ባንድ በሚለቀቁ ጥዑመ ዜማዎች የታጀበ ይሆናል። 2ኛ. ሀገራችንን ውድ የሆነ ህይወታቸውን በመስጠት ደማቸውን በማፍሰስና አጥንታቸውን በመከስከስ ለዚህ ያደረሷት የጀግኖች አርበኞች ተወካዮች ከፊት በሚያሰሙት ቀረርቶና ፉከራ የሚመራ፣ 3ኛ.የምርጫ ቅስቀሳችን በሰላም ተጀምሮ በድል እንዲጠናቀቅ እንዲሁም ሰላማዊ መሆናችንን ለማረጋገጥ በሀይማኖት አባቶች ፀሎትና ምርቃት የሚጀመር እና የሚታጀብ ይሆናል። 4ኛ.የመክፈቻ ስነስርአቱ ታሪካዊነቱን ለማሳየት እና የአብሳሪነት ሚና እንዲኖረው በነጋሪት ጉሰማ እና በእንቢልታ ነፊ የታጀበ ይሆናል። 5ኛ.የመክፈቻ ስነስርአቱ ደማቅና ሳቢ ለማድረግ በሰረገላ የሚመራ ይሆናል። 6ኛ.የፓርቲያችንን አርማ ፣ሞቶ ፣የምርጫ ምልክት እና የተለያዮ መፈክሮችን የሚይዙ ሞተር ሳይክሎችና መኪናዎች የሚታጀብ ሲሆን በተጨማሪም ከመኪና ላይ በድምፅ ማጉያ (ሞንታርቦ) በመጠቀም መዝሙሮች፣መፈክሮች እና የተለያዮ የቅስቀሳ ስራወችን በመስራት የምንጓዝ ሲሆን በመዳረሻው በመስቀል አደባባይ የምረጡኝ ቅስቀሳው መጀመሩን ለማብሰር የመክፈቻ ንግግር በማድረግ የፕሮግራሙ ፍፃሜ የሚሆን ይሆናል።
2ኛ.የካቲት 12 እና 13 2013 ዓ.ም ከጥዋቱ 3:00-11:00 በ 10ሩም ክፍለ ከተሞች በመኪና በመዘዋወር ሞንታርቦ በመጠቀም የምርጫ ቅስቀሳ ስራ የምንሰራ መሆኑን አውቃችሁ ለቅስቀሳው ለስራው መሳካት የሚረዱ የፀጥታ እና የመንገድ ደህንነት አካላት እውቅና እንዲኖራቸው እንድታሳውቁልን እየጠየቅን ለሚደረግልን ትብብር በቅድሚያ ምስጋናችንን እናቀርባለን።
ከሰላምታ ጋር
ለጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር አዲስ አበባ 
ጉዳዮ:- የዝግጅታችን ተሳታፊ እንዲሆኑልን ስለመጠየቅ ፓርቲያችን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ለሀገራችን አንድነት ካለው የፀና አቋምና ያልተዛባ ታሪካዊ ግንዛቤ ጀግኖች አርበኞቻችን ሀገራችንን ህይወታቸውን ያለምንም ስስት ለሀገራችን በመስጠት ደማቸውን በማፍሰስ አጥንታቸውን በመከስከስ በነፃነት ያቆዩልን በመሆኑ ያለንን ክብር ለማሳየት እና ለጀግኖች አርበኞቻችን ያለንን የላቀ ምስጋና ለመግለፅ የካቲት 14/2013 ዓ.ም ከስዓት 8:00 ስዓት ስድስት ኪሎ ከሚገኘው የፓርቲያችን ዋና ፅ/ቤት ባዘጋጀነው የምርጫ ቅስቀሳ የመክፈቻ ስነስርዓት ላይ በመገኘት ታሪካዊ ሀላፊነታችሁን ድጋሚ ታሪክ በመስራት እንድትወጡ በማክበር ጠርተነወታል ።
ከሰላምታ ጋር
ለፌደራል ፖሊስ ኦርኬስትራ አዲስ አበባ 
ጉዳዮ:- በማርሽ ባንድ እንድታጅቡን ስለመጠየቅ ፓርቲያችን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ከየካቲት 14-16/2013 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ የምረጡኝ ቅስቀሳና የምርጫ ዘመቻ የመክፈቻ ዝግጅት አሰናድቷል።ስለሆነም የማርሽ ቡድናችሁ የካቲት 14 /2013 ዓ.ም ከስዓት 8:00 ስዓት 6ኪሎ ከሚገኘው ዋና ፅ/ቤታችን በመገኘት ላዘጋጀነው የመክፈቻ ስነስርዓት እስከ መስቀል አደባባይ በምናደርገው የጎዳና ጉዞ እና የምርጫ ቅስቀሳ ድምቀት እንድትሆኑ እየጠየቅን ለሚደረግልን ትብብር በቅድሚያ ምስጋናችንን እናቀርባለን።
ለ —————-ሚዲያ አዲስ አበባ ጉዳዮ:-የሚዲያ ሽፋን እንድትሰጡ ሰለመጋበዝ በኢትዮጵያ የምርጫ ቦርድ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት የምረጡኝ ቅስቀሳና የምርጫ ዘመቻ የካቲት 8/2013 ዓ.ም በይፋ ተጀምሯል። ፓርቲያችን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ከየካቲት 14-16/2013 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ የምርጫ ቅስቀሳ የመመክፈቻ ፕሮግራም አዘጋጅቷል።ስለሆነም የናንተ ሚዲያ የካቲት 14/2013 ዓ.ም 6 ኪሎ ከሚገኘው ዋና ፅ/ቤት ከስዓት 8፡00 ስዓት በመገኘት ያዘጋጀነውን ደማቅ የሆነ የምርጫ ቅስቀሳ የመክፈቻ ስነ ስርዓት የሚዲያ ሽፋን እንድትሰጡልን በማለት ጥሪያችንን እናቀርባለን።
Filed in: Amharic