>

በጊዳ አያና ወረዳ  ያሉ ዐማሮች "... ኦነጎቹን ወገኖቻችንን አርደውብናል እና እንረዳቸው፣ ገድለውብናልና እንግደላቸው" ሳይሉ ለሕግ አቀረቡ ...!!! (ዘመድኩን በቀለ)

በጊዳ አያና ወረዳ  ያሉ ዐማሮች “… ኦነጎቹን ወገኖቻችንን አርደውብናል እና እንረዳቸው፣ ገድለውብናልና እንግደላቸው” ሳይሉ ለሕግ አቀረቡ …!!!
ዘመድኩን በቀለ
… በምዕራብ ወለጋ በሊሙ ወረዳ በአርቁምቤ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር አርሶ አደሮች ላይ ጭፍጨፋ ለመፈጸም አቅደው ወደ ሥፍራው የኦነግ ጦር ይሄዳል አሉ። የኦነግን መምጣት የሰማው ታናሽ ወንድሙ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል ከስፍራው ሸሽቶ ገበሬዎቹን ለነፍሰ በላው አራጅ ጦር ታላቅ ወንድሙ አጋፍጦም መሸሹም ይነገራል።
… ይኸነዜ ገበሬዎቹ ከመንግሥት እርዳታ እንደማይደርስላቸው እንደማይታደጋቸው ሞትም በደጃፋቸው እንደቆመ በተረዱ ጊዜና ኣሃ ዝም ብለን እጃችንን አጣጥፈን ተቀምጠን እንደ በግ ከምንታረድማ እየተከላከልን የወንድ ሞት እንሙት እንጂ ጎበዝ በማለት ወንበዴውን ቡድን ቤት ባፈራው ሁሉ ገጠሙት አሉ። ገጠሙት። ፈጣሪም የወንበዴውን ኃይል ዓይኑን ጨለማ ጉልበቱንም ቄጠማ አድርጎ ያዘላቸው። ከወንዶች ጋር መታኮስ የጀመረው ኦነግ እስካሁን ባለው መረጃ መሠረት ከ80 በላይ የተዋጊው ሽፍታና ኦነግ ሸኔ የሚል የዳቦ ስም የተሰጠው የሽፍቶች ቡድን ዳግም ላይመለሱ አሰናብቷዋቸዋልም አሉ።
… እነዚህ በቪድዮው ላይ እጅ እግራቸውን ተጠፍረው የሚታዩትም እዚያው ምዕራብ ወለጋ ላይ ዐማሮችን ሲያርዱ የነበሩ የኦነግ ሰራዊት አባላት ናቸው አሉ። ገሚሱ የዐማራ ገበሬዎች ናቸው፣ የኦሮሚያ ኃይል እያሰቃያቸው ናቸው ብሎ ሲጽፍ አይቻለሁ። ገሚሱ ደግሞ ትግራይ ነው። የኤርትራና የዐቢይ ጦር በትግራይ ላይ ጦርነት ዐውጆ ዜጎችን እያሰቃየ ነው ብለው የነጮችን ሆድ ለማራራት ሲንበጫበጩም አይቻለሁ። እውነታው ግን እንዲህ ነው ይላሉ የአካባቢው የመረጃ ምንጮቼ።
… ይኸውልህ ዘመዴ ይሄ የምታየው ቪድዮ ደግሞ ከአርቁምቤ ቀበሌ ውጊያ አፈትልከው በመሸሽ በጊዳ አያና ወረዳ ወረቦ ቀበሌ ውስጥ ሰርገው በመግባት ሁለት ንጹሐን ዐማሮችን አርደው ገድለው ሲያበቁ ለመሸሽ ሲሞክሩ ህዝቡ በዱላ ብቻ ሆ ብሎ ወጥቶ ከነትጥቃቸው በመያዝና በመማረክ አስሮም በማቆየት ፍትህ አዋቂው የዐማራ ሕዝብ የመንግሥት አካላት እስኪመጡ ድረስ ጠብቆ ያስረከባቸው የኦነግ ሠራዊት ተዋጊዎች ናቸው።
… አስቀድሞ ኦነግ መጣ ሲባል ሸሽቶና ፈርጥጦ ከቦታው ጠፍቶ የነበረው የኦሮሚያ ልዩኃይል ተብየው እስኪመጣ ደረስ ጠብቀውም ዐማሮቹ አስረክበዋቸዋል። የሚገርመው ዐማሮቹ እንዚህ ኦነጎች ወገኖቻችንን አርደውብናል እና እንረዳቸው፣ ገድለውብናልና እንግደላቸው ሳይሉ ለሕግ ሰዎች በዚህ መልኩ ነው አስረው ያስረከቡአቸው። ልዩ ኃይሉም እስረኞቹን ኦነጎች ከተረከባቸው በኋላ አንድም ጓደኞቻቸውን ጭምር የገደሉባቸው ናቸውና፣ በሌላ በኩልም እንዴት በዐማራ ገበሬ እጅ ትማረካላችሁ በማለትም በንዴት ጦፈው ወንጀለኞቹን ፍርድ ቤት ሳያቀርቧቸው እዚያው በአደባባይ የደቦ ፍርድ በመፍረድ ሕገወጥነታቸውን ምርኮኞቹን በአደባባይ በሰዉ ሁሉ ፊት በመረሸን አሳይተውዋልም ተብሏል።  ( ይሄም ልክ አይደለም።)
… አሁን ይሄ እንደ ግሪሳ ግር ብሎ መጥቶ ታሳሪዎቹ ላይ የሰፈረው እና በአደባባይ ያለ ፍርድ ወንጀለኞቹን በጥይት ረሽኖ የሚገድለው ልዩኃይል ተብዬው እኮ ገበሬው በገዛ ጥረቱ ወንበዴ ሽፍቶቹን ተዋግቶ፣ ተከላክሎም እጅ እግራቸውን ጠፍሮ አስሮ ባቆያቸው ኑሮ እንዲህ እየፎለለ እየወበራም፣ እየፎከረ፣ እያቅራራም በጫማጥፊ፣ በእርግጫ ከመውገር አልፎ ራሱ ፈራጅ ሆኖ በጥይት ባልረሸነም ነበር። መጀመሪያማ ራሱ ፈርጥጦ እግሬ አውጪኝ ብሎ ድራሽ አባቱ የጠፋ መንጋ እኮ ነው አሁን ደርሶ እንዲህ የሚወበራው።
… ትናንት በተሰማ ዜና ደግሞ የኦቦ ሽመልስ መንግሥት በወለጋ የሚኖሩት የዐማራ ገበሬዎች ላይ ሄጵ ማለቱ ተሰምቷል። ይህቺ ነገር ከአሁኑ በጊዜ ካልቀጨናት ነገ ሌሎች አካባቢም እንዲሁ ሄጵ የሚሉ ይበዙና ስንገድላቸው፣ ስናፈናቅላቸውም ጦር ይመዙብናል በማለት ዐማሮቹ ራሳቸውን ይከላከሉበት ዘንድ መንግሥት ራሱ ያስታጠቃቸውንና በነፍስ ወከፍ በግልም በመንግሥት ዕውቅና የታጠቁትን ጠመንጃቸውን ለማስወረድ እየተንበጫበጨም ነው ተብሏል። ኦነግ ሸኔ የሚል የዳቦ ስም የተሰጠውና የራሳቸው የእነ ዐቢይ ሽመልስ የግል ድብቅ ጦር የሆነውን ቡድን ዐማሮቹ በመከላከላቸውና በመደምሰሳቸው ምክንያት ፒፒ መበሳጨቱንና ገበሬዎቹን የጦር መሳሪያቸውን በማስፈታት ለጅምላ እልቂት ለማመቻቸት እየደከመ መሆኑም ተነግሯል። የኦሮሚያ ልዩ ኃይልም በተደመሰሰው የኦነግ ጦር ምትክ ገብቶ አሁንም ከዐማራ ብሔር ገበሬዎች ጋር በጠብመንጃ እየተጠዛጠዘ መሆኑም ተሰምቷል።
… የጦሩ ጠቅላይ አዛዥ ዐቢይ ኖ፣ የጦሩ ሚንስትር፣ ኦሮሞ ኖ፣ የጦሩ ሎጀስቲክ ብርሃኑ ጁላ ኖ፣ የኦሮሚያ ብሬዘዳንት ሽማሊስ ኖ፣ ኦነግና ኦነግ ሸኔ ወንድማማች ኖ። ዐማራ ደግሞ ዓይኔ እያየ፣ እየተመለከተም አልሞታትም ባይ ኖ። ብአዴን ደግሞ በድን ኖ። እንኳን በወለጋ ላለ ዐማራ ይቅርና ደብረማርቆስ ላለውም ዐማራ ግድም አይሰጠው። ብቻ መጨረሽታውን ማየት ነው።
… ይሄ ማለት ለኦፒዲኦ ጥሩ ምልክት አይደለም። ሁሌ ዐማራ ማረድም ይደብራል። ባስ እያለ ሲመጣ ግን ነገር ሁሉ ይገለበጣል። ትዕግስትም ልክ አለው። መታረድ የሰለቸው ነገድም የሆነ ቀን ከሆነ ቦታ ሆ ብሎም ይነሣል። ራሱንም መከላከል ህዝቡንም ከአራጆች ነፃ ማውጣትም ይጀምራል።
… ሰምታችኋል  !! 
ይሄ አንደኛው የምርኮኞቹ ቪድዮ ነው  ተብሏል። ሁለቱን ቀሪ ቪድዮዎች ደግሞ ቆየት ብዬ እለቅላችኋለሁ። በየፌስቡኩ እንደሚጯጯኸው አይደለም። በቪድዮው ላይ የሚታዩት የዐማራ ገበሬም፣ የትግራይ ወጣቶችም አይደሉም። እነዚህ በምዕራብ ወለጋ በዐማራ ገበሬዎች የተማረኩ የኦነግ ታጣቂዎች ናቸው። ዐማራ ሕግ ዐዋቂ ነው። ምርኮኛ አይገድልም። አይደለም ምርኮኛ ሱሪውን አውልቆ ሽንትቤት የተቀመጠን ጠላቱንም አይገድልም። ዐማራ መጀመርታ ነገር ሱሪህን ታጠቅ ነው የሚለው። ቀበቶው የላላ፣ ሱሪው የተፈታ፣ የተማረከም ጠላት አይገድልም። 
 
እንግዲህ ብልጽግና ለምን ተማረኩ ብሎ ነው አሁን ከዐማሮቹ ጋር በወለጋ ጦርነት የገጠመው።
Filed in: Amharic