>
5:13 pm - Friday April 20, 9506

የተፈራው አልቀረም ሙሉ ነጋ(ዶ/ር)  ዳግማዊ ስብሃት ነጋን ሆነው መጥተዋል!?! (ታምሩ ገዳ)

የተፈራው አልቀረም ሙሉ ነጋ(ዶ/ር)  ዳግማዊ ስብሃት ነጋን ሆነው መጥተዋል!?!

ታምሩ ገዳ

 

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ሙሉ ነጋ(ዶ/ር) ስብሃት ነጋን መሆን እንዳያምርዎ ብለን ባለፈው ሰሞን በማህበራዊ ገጻቸው የጻፉትን አንስተን ለማስጠንቀቅ ፈልገን ነበር። ሰዉዬውን ከአራት ኪሎ  ጭነው ትግራይ ያደረሷቸው አለቆቻቸውን አጀንዳ ይዘው ብቅ ብለዋል። የአማራ ክልል ልዩ ኃይል ከወልቃይት ጠገዴ፣ጠለምትና ራያ ይወጣ።
 እነ ስብሃት ነጋ በጉልበት ይዘው ሕዝቡን ማንነትን በግድ እንዲክድ ሲጨፈጭፉት የኖሩትን ብልግና ለመድገም ነው። እነ ስብሃት  በጥጋባቸው በለኮሱት ጦርነት ውርደት እንዲከናነቡ ካደረጉ ጀግኖች መካከል መከላከያ ሰራዊቱን  ጭምር ያስደነቀውና አጋርነቱን ያሳየው የአማራ ልዩ ኃይል በጥላቻ መክሰስ አስቀድሞ ስም ማጥፋት እርስ አስመላሽ ማለቱም የመጣው ያው ከአራት ኪሎ ነው። ታማኝ ሎሌዎችም ሰሞኑን ባህር ዳር ላይ ይሄንኑ እነ ታዬ ዳንደአ አፉን ሲያላቅቁበት የነበረውን ልዩ ኃይል በግምገማቸው ያዋክቡት ይዘዋል። ተናቦ መስራት ብልጽግና ቤት እንዲህ ነው።
የሆነው ሆኖ ሙሉ ነጋ እንደተፈራው ስብሃት ነጋን ለመሆን የትግራይን ክልል ማስተዳደርና ተዘረፍኩ፣መድሃኒት አጣሁ የኤርትራን ወታደሮችን በተመለከተ መግለጫ ስጡ እያለ በየስብሰባ አዳራሹ  የሚያስጨንቃቸውን ህዝብ የሚበላውን ምግብ ከመስጠት፣መድሃኒት ከማቅረብ ይልቅ እንደ ህወሓት መሪዎች በጉልበት እርስት ማስፋፋትና ጫጫታ ለመፍጠር መሯሯጡን ሥራዬ ማለት ፈልገዋል።
ባህር ዳር ያሉ አደርባዮች ደግሞ ንጹሃን ሲጨፈጨፉ አብረው ድምጻቸውን ማጥፋታቸው ሳያንስ አለቆቻቸው የሰጡዋቸውን የግምገማ አጀንዳ ይዘው ጀግኖቹን እየነዘነዙ ነው። የዚህ ድምር ውጤት ከኦሮሚያ እስከ ቤንሻንጉል ከአራት ኪሎ እስከ ትግራይ ከባህር ዳር እስከ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት እርብርቡ አማራ የተባለን ሁሉ እረፍት መንሳት ነው።
አበው “ግዛኝ ግዛኝ ስለው ለመሸጥ አሰበኝ” ያሉት ወደው አይደለም። የበሻሻው አራዳ ንጹሃን የህይወት መስዋዕትነት ያገኙትን ነጻነታቸውን ለመንጠቅ ለእነ ስብሃት “ፌደራል” እና “ህገ አራዊት” (ህገ መንግሥት) ጥብቅና መቆሙ ሳያንስ እሱው ጠፍጥፎ ለሰራው የማንነትና የወሰን ጉዳይ ኮሚሽን(ዛሬም ድረስ አየር ላይ ነው) ችግሩ ይፈታል ለቀው ይወጡ ያለውን ነው ሙሉ ነጋ መንገር የፈለጉት። ያልገባቸው ዛሬ ውጡ ያሉዋቸው ከየት ነው የሚወጡት ብለው መጠየቅ ጠፍቶዋቸው ሳይሆን ጌታዋን የተማመነች አይነት ነው።
ለሁሉም ሰከን የሚለው የሱዳን ወታደርና መሪዎች ብቻ ሳይሆኑ በንጹሃን ሞት እየቆመራችሁ ያላችሁ የብልጽግና ቁማርተኞች ጭምር ናቸው። ሙሉ ነጋ የሚገባዎትን ቢያውቁ መልካም ነው እብሪት እንኳን ለእርስዎ ለእነ ስብሃት ነጋም አልሆነም።
Filed in: Amharic