>

መንግሥታዊ እሳት በጉማይድሌ...!!!  (ዘመድኩን በቀለ)

መንግሥታዊ እሳት በጉማይድሌ…!!! 

ዘመድኩን በቀለ

… የጌታ ልደት በዓል ዋዜማ ጀምሮ በጉማይድሌ ህዝብ ላይ ግርግር ማስነሳት የጀመረው የደቡብ መንግሥት ልዩ ኃይል ይህንኑ መንግሥታዊ ሽብር ትላንት ጥር 02/2013 እና ዛሬ ጥር 03/2013 አጠናክሮ መቀጠሉን ከሥፍራው የሚደርሱኝ መረጃዎች ያመለክታሉ። በተለይ ጉማይዴ ኃይሎታና ጋራጣራ በሚባሉ ቀበሌዎች በኮንሶና ደቡብ ልዩ ኃይል ፖሊስ ድጋፍ ሰጭነት እንደዚህ እንደምናየው የምስኪኖች ቤት በእሳት እየነደደ ነው። የጉማይዴ ህዝብ ለፌደራል መንግሥቱ አቤት ኧረ አስጥሉን ቢልም ጆሮ ዳባ ልበስ መባላቸውን ነው ነዋሪዎቹ የሚናገሩት።
… ዛሬ ጠዋት ልዩ ኃይሉ ሐይበና ቀበሌ ገብቶ የመሣሪያ እሩምታ ከፍቶ የቀበሌውን ነዋሪ  ሙሉ በሙሉ ማፈናቀሉም ተነግሯል። በዚህ ሰዓት በካቡራ ኢየሱስ ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ የተጠለሉትንም ጥይት ተኩሰውባቸው በትነዋቸዋል ተብሏል። ከልዩ ኃይሉ ጋር ሰገን ከተማ ላይ በአስተዳደር ግቢ ውስጥ እየተቀለቡ ሁለት ዓመት የጨረሱት አመራር ነን የሚሉት አካላት ይሄን አሸባሪ ጦር እየመሩ እየፈጁን ነውም ይላሉ መረጃውን ያደረሱኝ ወዳጆቼ።
… ዛሬ ጠዋት አንድ ሽማግሌና አንዲት ሴት ልጅ በጥይት ተመተው ሞተዋል። ከትላንት ወዲያ በጥር አንድ አንድ ኩሴ ከበደ የተባለ ወጣት ሞቷል። ንብረት ከጉማይዴ እየተዘረፈ ወደ ኮንሶ እየተጋዘ ነው። ሌቦች በልዩ ኃይሉ እየታጀቡ ነው የዘረፉትን ዕቃ የሚያጓጉዙትም ተብሏል።
… አሁን በዚህ ሰዓት በቀን 3/2013 ዓም ቀን ከቀኑ 8:15 ጀምሮ በቾ ቀበሌን እያነደዱት ነው። ግበረ ሽበራው ሰገን ከተማ ለመድረስ 3 ኪሎሜትር ብቻ ነው የቀረው። በርካታ ሰው በዛሬው ዕለት ሞቷል እየተባለ ነው። ስንት ሰው ነው? ማነው? ለማረጋገጥና ሬሳ ለማንሳትም አልተቻለም። ብቻ ሁኔታው በክልሉ መንግሥት ስለሚደገፍ አርሶአደሩ እራሱን ለመከላከል እንኳን አልቻለም። የክልል ጸጥታ ከአቅሙ በላይ እንዳልሆነ ይታወቃል። አሁን ቤቾ ኪዳነምህረት አከባቢ ከባድ ቃጠሎ ይታያል። እግዚአብሔር ሆይ ሌላ ቃጠሎ አርገው እያልኩኝ ነው። ይላል መረጃውን ያደረሰኝ ወዳጄ።
… አሁን በዚህ ሰዓት ዲራሼ ወረዳ ሆልተ ቀበሌ ትምህርት ቤት በጉማይዴ ተፈናቃዮች ተጨናንቋል። ከላይ ወደታች የሚፈሰውን ሌላውን ሕዝብ ደግሞ የደቡብ ልዩ ኃይል እንዳያልፉ መንገድ ዘግቷል። ለክልሉ ገጽታ ግንባታ መሆኑ ነው መሰለኝ። መድኃኔዓለምም ይጠብቀንም ብሏል።
… ትግራይ ህወሓት ባመጣችው ጦስ አሁን ተፈታለች። ጎንደር በሱዳን ጦር እንዲወረር የማርያም መንገድ ተከፍቶላታል። ኦነግና ብልጽግና ከወለጋ፣ ከምዕራብ ሸዋና ከመተከል ዐማሮቹን እያጸዱ ነው። በአፋርና በሱማሌ በኩል አልነድ ያለ ክብሪት እየተጫረ ነው። ደቡብ በአባ ዱላ ገመዳ መሪነት ወደ አስር ትንንሽነት እየተሸነሸነ ነው። ደቡብ ይፈርስ፣ ይጨፈለቅና ከዚያ ሰላማዊት፣ ልማታዊትና የገዳ ዲሞክራሲ ባለቤት የሆነች ታላቋን ኦሮሚያ በኢትዮጵያ መቃብር ላይ መገንባት። ይሄውን ህልሙ። ይሄው ነው ሩጫው።
… ኢትዮጵያን ለዚህ ጦስ የዳረግሽ ህወሓት ሆይ አቦ ነፍስሽን አይማረው።
Filed in: Amharic