>
5:13 pm - Sunday April 19, 1676

ሱዳን ትናንት በትህነግ አገዛዝ የኢትዮጵያን ድንበር ያለከልካይ ጥሶ ይገባና አማራውን ያጠቃ ያ አሰራር  ዛሬም አልተለወጠም!!!  (ደረጄ ከበደ)

ሱዳን ትናንት በትህነግ አገዛዝ የኢትዮጵያን ድንበር ያለከልካይ ጥሶ ይገባና አማራውን ያጠቃ ያ አሰራር  ዛሬም አልተለወጠም!!! 
ደረጄ ከበደ

ፖሊቲካው የረቀቀ ነው። ይቺን ወርና ይቺን ሰሞን አማራው ከአንገቱ ቀና ብሎአል። ሌላው ቀርቶ የአቢይ ዋና ጉዳይ አስፈፃሚ የሆነው ብኤዴን(አዴፓ፣የአማራ ብልፅግና) እነ አበረ አዳሙን ጨምሮ ሳይወዱ በግዳቸው ከአማራው ጋር የተሰለፉ እንዲመስሉ አስገድዶአቸዋል። ልብ እንበል የነዚህ ሰዎች አማራን መደገፍ አማራው በሚያስደንቅ ጀብዱ ትህነግን መደምሰሱ፣ መከላከያውን ደግሞ ባረጀ ጠመንጃና ጥይት   ከከበባና ከምርኮ ማዳኑ፣ እርስቱንም በአስደናቂ ብቃት ከማስለቀቁ የተነሳ ነው። ወደው ግን አይደለም። የመርህ ለውጥም ኖሮአቸው ግን አይደለም። እንዲያውም እኔ በማንኛውን ነገር እወራረዳለሁ የአማራ ብልፅግናዎች፣ ኢዜማዎች፣ የአማራው ክልል ፖሊስ ኮሚሽነር (አማራውን ለአመታት ሲሸጡና ሲለውጡ የነበሩ አካላት) ዛሬም ከአቢይ አህመድ ጋራ ሆነው በአማራው ላይ እየሸረቡ ነው።
ጠ/ሚኒስትሩ አንጀታቸው ደብኖአል፣ አማራ በክልሉ ያለውን ብአዴኖች ያሰሩትን የማሸማቀቂያ ሃውልት(Statue) ያለምንም ልዩ ፈቃድ አፍርሶአል። በተመለሱት እርስቶቹ ውስጥ መጠነኛ ስራም ጀምሮአል። የተመለሱትን ግዛቶች በቀድሞውና በትክክለኛው ስማቸው ሰይሞአቸው “እንኩዋን በደህና ወደ ራያ አማራ ክልል መጡ”  የሚሉና የመሳሰሉትን አይነት አማራዊ የመንገዳር ምልክቶች አቁሞአል፣፣ የአማራ ክልል አስተዳደር ካርኒና ደረሰኝም ማህተምም አሰርቶአል። ይህ ሁሉ ጠ/ሚኒስትሩ ለተመለሱት እርስቶች ማንነት ግልፅ እውቅና ባልሰጡበትና የአማራ እርስቶች መሆናቸውን ባላፀደቁበት ሁኔታ እየተገበረ ያለ ነው። ስለዚህ አማራውን ለማንበርከክና ያስመለሰውን ክብሩን ለመንጠቅ በአራቱም ማእዘናት ጉርጉዋዶች እየተቀፈሩ ነው።
ጠ/ሚኒስትሩና ብልፅግና ፓርቲ ጊዜ እየገዙ ነው!! ያ በእንደዛ እያለ እነታዬ ደንደአንና ኢዜማዎችን እየላኩ ግን የሳቸውን አቁዋም በግልፅ ከማሳወቅ አልቦዘኑም።  ችግሩ አሁን አማራው ወኔው ተመልሶ ከ 28 አመታት ባርነት ተላቆ በደስታ ስካር ላይ ስላለ የመሪውን ሸፍጥ የሞላበት ውለታቢስ ውሳኔና እቁዋም ልብ ብሎም ሊሰማ አልፈቀደም። ያለውን ቁርጠኝነትም በየጊዜው ሰልፍ እየወጣ በርችት ተኩስ አሳይቶአል። ጠ/ሚኒስትሩም በጦርነት ባሩድ ሽታ የተቆጣውን አማራ ሊገዳደሩት አልሞከሩም። ብአዴንም ይህ ወላፈን ይለፍ የሚል አቁዋም ይዞ እንደ እስስት የ 28 አመት አማራ ጠል አቁዋሙን ከለር ለውጦ የአማራው ወዳጅ ሆኖ ታይቶአል። የሚሞኝለት ግን አይኖርም።
ትኩረት ሊሰጥበት የሚገባው ነገር ግን መንግስታችን በዚህ ወቅት ስጋቶቹ ትህነግና ህወሃት ሳይሆኑ አማራው መሆኑን ነው። ስለዚያ ነው ከጦርነቱ በሁዋላ የአማራው ወከባ የበዛው።
የሱዳንን ጉዳይ ስናነሳ፣ ትዝ ይለን ከሆነ በህዋሃት መንግስት ዘመን አማራው ትንሽ ቀና ሲል ሱዳን በድንበር ገብቶ እንዲበጠብጠው ይታዘዝበት ነበር። የወያኔ ጦርና ሱዳኖች የአማራን ገበሬ መሃል አስገብተው ይወጉት ነበር። ሱዳን በኢትዮጵያ ፖሊቲክስ ውስጥ የአማራው የጎን ውጋት እንዲሆን በኛው መንግስት ተፈቅዶለት የሚሰራ ነበር።
ዛሬም ያው ነው!!!!
የሰሞኑ የሱዳን ጥቃት ፌዴራል መንግስታችን ላይ ያነጣጠረ ሳይሆን አማራው ላይ ያተኮረ ነው። የሱዳኑ መሪ መጥቶ በአንድ ቀን መመለስ የሱዳን መንግስትና ኢትዮጵያ ተጋጭተዋል የሚል ግምት እንዲፈጥር ታስቦ ነው። ሱዳንና ኢትዮጵያ የድንበር ግጭታቸው አገርሽቶአል እንዲባል የሱዳኑ መሪ ጉብኝታቸውን ገና ሳይጀምሩ ተመለሱ። ምክንያቱም አቢይ የሚፈልጋቸው አማራውን እንዲበጠብጡ ነው እንጅ ወዳጅነታቸው እንዲታወቅ አይደለም። በተጨማሪም በአባይ ጉዳይ ሁለቱ መንግስታት ልዩነት ቢኖራቸውም የጋራ ጠላታቸው የሆነውን አማራን ለማጥቃት ግን ልዩነታቸውን ወደጎን ይተዋሉ። አማራውን በሱዳን ማስወጋት ለሃያ ስምንት አመታት የተሰራበት ጉዳይ እኮ ነው።የወያኔ ፖሊሲ ቅጥያ ነው !! ድንበር ተጣሰ ብሎ ወያኔ አማራውን አግዞት አያውቅም፣ ይህም የአቢይ እስተዳደር ድንበራችን ተነካ ብሎ ጦሩን አልሰደደም አይሰድምም። ሱዳኖች በተለያዩ ወቅቶች ከወያኔ ጦር ጋር ተሰልፈው አማራውን ወግተውታል። በአቢይም እንደዛው ነው። ስለዚህ አማራው ዙሪያውን እንደተከበበ ማወቅ አለበት።
ጠ/ሚኒስትሩ እኮ እንደጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ የመለስ ዜናዊን ፈቃድ እያስፈፀሙ ነው ያሉት። ህገመንግስት አለመቀየር ይሁን፣ አማራን በክምር መግደል፣ ኤትኒክ ፌዴራሊዝምን የሙጢኝ ማለት፣ አንቀፅ 39ኝን አለማስወገድ፣ የአቢዮታዊ ዴሞክራሲ ፓትሪያርኩ መለስ ዜናዊ የፃፉትን መመሪያና በሞታቸው ወቅት የተናዘዙትን ኑዛዜ አንድ ሳይቀር እኚህ ጠ/ሚኒስትር እየተገበሩ ነው ያሉት።
ይህንን የሻገት አገር አጥፊ ስርአታቸውን መገርሰስና መደምሰስ ግን የኢትዮጵያ ህዝብ ሃላፊነት ነው። ኢትዮጵያ ከመፈራረስና የአንድ ብሄር መፈንጫ ከመሆን ለመታደግ የሚፈልግ ሁሉ፣ መዋደቅ አለበት፣ ደሙን ማፍሰስ አጥንቱን መከስከስ አለበት። የሃገሬ ሰው ሃገሩን ለማዳን ዋጋ መክፈል አለበት። የብሄርና የቁዋንቁዋ ክልል ኢትዮጵያን ሳያጠፋ ብልፅግናን ከነ ጠ/ሚኒስትሩ ጭምር፣ የኢትዮጵያ ህዝብ መፋለም አለበት። ሌላ ምንም አማራጭ የለም።
Filed in: Amharic