>
5:13 pm - Thursday April 19, 8818

"የትግራይ አሜሪካ ካህናት" - ሀገርን መዝለል ከባህር ያሰምጣል...!!! (አባይነህ ካሴ)

“የትግራይ አሜሪካ ካህናት” – ሀገርን መዝለል ከባህር ያሰምጣል…!!!

አባይነህ ካሴ

ዘንድሮ የማንሰማው የለም። ማኅበረ ካህናት ዘትግራይ አሜሪካ  የተባለ ቡድን መግለጫ አውጥቻለሁ አለ። መግለጫ የጊዜው ወግ ኾኗልና እሱ ባልቸገረ። ግን መጀመሪያ ስሙን ማስተካከል ነበረበት። ሲጀመር ስም አጠራሩ ውል አልባ ነው።
እንደምንም አጠጋግቼ ስተረጉመው የትግራይ አሜሪካ የካህናት ማኅበር እንደማለት ይመስላል። እንዲህ ብሎ ስም የለም። የትግራይ  አሜሪካ የምትባል ማን ናት? የሀገር ቤቱ የተስፋፊነት መንፈስ እዚህም ያልለቀቃቸው ባይኾን የትግራይ አሜሪካ እያልን እንጽናና ብለው መኾን አለበት። የስንቱ አሜሪካ ልትኖርላቸው ፈለጉ?
ስማቸውን መጻፍ ሳይችሉ ለመግለጫ የቸኮሉ ብለናቸዋል። በፈለጉት ይጠሩ ብንል እንኳ በትግራይ እና በአሜሪካ መካከል ኢትዮጵያ የምትባል ቅድስት ሀገር አለች። በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የትግራይ ማኅበረ ካህናት ቢል እንኳ አንድ ነገር ነው። ለኢትዮጵያ ያላቸውን ጥላቻ ያሳዩበት መኾኑ ነው።
ለወቀሳ ጊዜ ኢትዮጵያን እና ቅዱስ ሲኖዶሱን ያነሣሉ። በመዋቅር ግን አንዱም ጋ የሉበትም። በየትኛው ሀገረ ስብከት ምን ዕውቅና አላቸውና? ሀገርን እንዘላለን ብላችሁ ከባሕር መስመጣችሁ ነው። ከሀገር ወዲያ ያለው ውቅያኖስ ነው። እናንተ የአሮጊቶች ቡድን ካድሬዎችን እንጅ የትግራይ ካህናትን አትወክሉም። አታጭበርብሩ።
ቤተ ክርስቲያንን ለመክሰስ ለመውቀስ መጀመሪያ በመዋቅር ግቡ። ከዚያም ጥያቄአችሁን አቅርቡ። ተሳዳጁ የአሮጊቶች ቡድን እንኳ ቢያንስ በዐደባባይ ኢትዮጵያን ደፍሮ አልዘለላትም። የእናንተ የክህደት እግሮች ግን ፖለቲከኞቹን ያስናቁ ፈጣኖች ናቸው። ላስጠንቅቃችሁ ሀገርን መዝለል ፍጻሜው ስጥመት ነው።
ሌላው ዝባዝንኬያችሁ የሚሰማ አይደለም። ያ ሁሉ ክርስቲያን በኦሮሚያ፣  በሶማሌ፣  በድሬዳዋ፣  በሲዳማ፣  ቤንሻንጉል ሲያልቅ ትንፍሽ ያላለ የዘር አቁማዳ የሚያለፋ ሁላ አሁን መንጫጫቱ መልእክቱ ግልጽ ነው። በጥቃቱ አለንበት። በተደሰትንበት እንዴት ብለን እናዝናለን? ማለታችሁም አይደል።
ለነገሩማ የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎችም አብረው አልቀው ነበር። ከአሮጊቶቹ በላይ ያረጃችሁ ከፖለቲከኞቹ በላይ የቦለጠቃችሁ ድኩማን እንጅ ካህናት አትባሉም።
Filed in: Amharic