>

ጥያቄው የርስት ጉዳይ ከሆነ እንኳን ወሎ ኦሮምያ የሚባለው ርስት ሊሆን ኦሮምያ የሚባለው የጀርመን ዝርያ ራሱ የኦሮሞ አይደለም! (አቻምየለህ ታምሩ)

ጥያቄው የርስት ጉዳይ ከሆነ እንኳን ወሎ ኦሮምያ የሚባለው ርስት ሊሆን ኦሮምያ የሚባለው የጀርመን ዝርያ ራሱ የኦሮሞ አይደለም!

አቻምየለህ ታምሩ

ታዬ ደንደአ የፖለቲካ ዐይነ ጥላውን የገፈፈው የኦነግ “ጁንታ” በመሆን ነበር። በኦነግ “ጁንታነቱ” የሕወሓት “ጁንታ” ለዓመታት ዘብጥያ አውርዶታል። ታዬ ዛሬ ከኦነግ ወደ ብልጽና “ጁንታነት” ቢሮ ቢቀይርም የአስተሳሰብ አድማሱ ግን  በልቡ የተጻፈው  በፖለቲካ ጥርሱን የነቀለበት ኦነጋዊነት ነው።
ታዬ እንደ እናት ድርጅቱ ኦነግ ሁሉ ሰው ሁሉ ልክ እንደ ቄሮ ለማሰብ ፈቃደኛ ያልሆነ፤ የኢትዮጵያ ታሪክም  የሚጀምረው ከዳግማዊ ምኒልክ  ይመስለዋል።  እንዲህም በማሰቡ የራያ ጥያቄ የርስት ጉዳይ ከሆነ ራያ ብቻ ሳይሆን ወሎ ጭምር የኦሮሚያ አካል ይሆናል ሲል ጽፏል። ወሎ የኦሮሚያ አካል መሆኑን ለማሳየትም  ወረ-ያጁ፣ ወረ-ኢሉ፣ ወረ-ኢመኑ፣ ወረ-ባቦ ወይም ወረ-ቃሉ እንዴት ሌላ ይባላል? ሲል ይጠይቃል።
ያገራችን ሰው «ርስት በሺ ዓመቱ ለባሌቤቱ» የሚል አባባል አለው። ሺህ ዓመታትን  ወደ ኋላ ሳንሄድ ሶስት መቶ ዓመታት ብቻ ወደ ኋላ ብንሄድ ከኦሮሞ ወረራ በፊት ወረ-የጁ ገንቴ፤ ወረ-ኢሉ ቤተ ጊዮርጊስ፤ ወረ-ባቦ ቤተ ሳባ፤ ወረ-ቃሉ መካነ ሠላም፤ ራያ አንጎት፤ ወሎም ቤተ አማራ የሚል የጥንት ስም ነበራቸው። ስለዚህ የርስት ጉዳይ ከሆነ ከኦሮሞ ወረራ በኋላ  ወረ-የጁ  የሆነው ወደ ገንቴ፤ ወረ-ኢሉ የሆነው ወደ ቤተ ጊዮርጊስ፤ ወረ-ባቦ  የሆነው ቤተ ሳባ፤ ወረ-ቃሉ  የሆነው ወደ መካነ ሠላም፤ ራያ የሆነው ወደ አንጎት፤ ወሎም ወደ ቤተ አማራ መመለስ አለባቸው። እስካሁን አለመመለሳቸውም የኛ ስህተት ነው።
ጥያቄው የርስት ጉዳይ ከሆነ በኢትዮጵያ ምድር ኦሮሚያ የሚባል ርስት የለም። ዛሬ “ኦሮምያ” የሆነውን ስያሜ  ያወጣው በሚሲዮን ስም ወደ ኢትዮጵያ የገባው ጀርመናዊው ሰላይ ዮዋን ክራምፍ ነበር።  ኦሮምያ በአፍሪካ ምድር የመጀመሪያው የጀርመን ኢምፓዬር አካል እንዲሆን ለታሰበ ምድር የተሰጠ ስያሜ ነው። ይህንን ታሪክ ዮዋን ክራምፍ ራሱ አፍሪካ ውስጥ ለጀርመን ቅኝ ግዛት የሚሆን ምድር ማግኘቱን፣ ለቦታውም ኦርማኒያ [ኦሮምያ] የሚል ስም ማውጣቱን “Travels, Researches and Missionary Labours During an Eighteen Years’ Residence in Eastern Africa” በሚል ርዕስ በ1861 ዓ.ም. ባሳተመው የጉዞ ማስታወሻ ገጽ 73 ላይ ነግሮናል።
ዮዋን ክራምፍ በጉዞ ማስታወሻው ገጽ 73 ላይ ጨምሮ እንደጻፈው የቦታ መጠሪያ ስያሜ ለማውጣት የገፋፋውን ምክንያት ሲናገር “ጋሎች ለራሣቸው እና ለሚኖሩበት አካባባቢ አጠቃላይ የወል መጠሪያ ስለሌላቸው ነው” ሲል ነግሮናል። የዮዋን ክራምፍ ተማሪዎች የሆኑት ኦነጋውያን የመንፈስ አባታቸው የሆነው ዮዋን ክራምፍ ያወጣውን የቦታ ስም እየተጠቀሙ የስሙ ፈጣሪ ራሱ ስሙን ለመፍጠር የተነሳሳው “ጋሎች ለራሣቸው እና ለሚኖሩበት አካባባቢ አጠቃላይ የወል መጠሪያ ስለሌላቸው” መሆኑን እየነገራቸው እነሱ ግን “ከጥንት ጀምሮ ኦሮምያ የሚባለ ምድር ነበረን” ፤ “የርስት ጉዳይ  የሚነሳ ከሆነ ራያና ወሎም የኦሮምያ አካል መሆን አለባቸው” በማለት ለመመርመር ፍቃደኛ ያልሆነውን መንጋቸውን ያደነቁሩታል።
ዮዋን ክራምፍ በጉዞ ማስታወሻው ገጽ 76 እና 122 ላይ ለጀርመን መንግሥት ምክር የሰጠ ሲሆን “ኦሮሚያ” ብሎ የሰየመውን የኢትዮጵያ ክፍል መቆጣጠር ማለት ምሥራቅን እና መካከለኛውን አፍሪቃ መቆጣጠር መሆኑን ያወሳና የጀርመን መንግሥት ዐይኑን ወደዚያ ምድር እንዲያነጣጥር ምክር ይለግሳል። በገጽ 122 ላይ ደግሞ “ኦሮምያ” ብሎ የፈጠረውን ቦታ “የአፍሪካ ጀርመን” ሲል ይጠራዋል።
ባጭሩ ጉዳዩ የርስት ጉዳይ ከሆነ እንኳን ወሎና ራያ የኦሮምያ ርስት ሊሆን ኦሮምያ የሚባለው የጀርመን ፍጥረትም ርስቱም ሆነ ስያሜው የኦሮሞ አይደለም። ይህንን ለመገንዘብ ሌላ ቦታ ሳንሄድ ፕሮፈሰር  መሐምድ ሐሰን፣ ፕሮፈሰር ተሰማ ጠአ፤ ፕሮፌሰር ሕዝዔል ጊቢሳ፣ ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ፣ ወዘተ የጻፏቸውን የዲግሪ ማሟያ ወረቀቶች፤ የሁለቱ ወለጋዎች[ቄለምና ነቀምት] ፣ የጅማ፣ ወዘተ ነገሥታት የጻፏቸውን ታሪከ ነገሥቶችና የትውልድ ታሪኮች ማንበብ ብቻ በቂ ነው።
ታዬን ደንደአን እስቲ አንድ ጥያቄ ጠይቁት። በየትኛውም የኢትዮጵያ ክፍል የራሱ ያልነበረን የሰው ርስት የወረረ ማነው? በሌላው ላይ በደል ያደረሰው ማነው? በታሪክ ሂደት በደል ያደረሰ ማነው? መጤና ሰፋሪው  ማነው? የሚሉ ጉዳዮችን የሚያጣራና ወንጀል የፈጸመው ቢኖር እንዲክስ፣ የሌላውን ቅድመ አያት አጽመ ርስት የያዘውን ማንኛውንም መሬት ቢኖር ወደ ትክክለኛው ባለቤቶች እንዲመለስ የሚያጠና አለማቀፋዊው ኮሚሽን እንዲቋቋም ትደግፋለህ ወይ በሉት እስቲ?
Filed in: Amharic