>
5:13 pm - Sunday April 19, 0415

“ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ እንደ ቆፍጣናው መንግሥቱ በጦር ሜዳ ተገኙ” -ፋታ ሚዲያ (ታጠቅ  መ  ዙርጋ)

“ጠቅላይ ሚኒስተር አብይ እንደ ቆፍጣናው መንግሥቱ በጦር ሜዳ ተገኙ” -ፋታ ሚዲያ

ታጠቅ  መ  ዙርጋ


ለመግለጽ የሚመጥን ቃላት ያጣንለት  የባዕድ ቅጥረኛ ወያኔዎች  በአገረ መከላኬያ ሃይል አባላት ላይ የፈጸሙትን አስከፊ ግፍ ተከትሎ፤ በሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብና በቅጥረኛ አክራሪ ተጋሮች  መካከል በመደረግ ላይ ያለው  ጦርነት ከተጀመረ ሁለት ሳምንት ሊያስቆጥር ነው  ። 

ለአድባባይ ሳይገለጽና ሳይጠበቅ  የጠቅላይ ሚኒስተር አብይ አህመድ ጦርሜዳ ላይ ከቸች ብሎ  መታየትን አስመልክቶ  የፋታ ሚዲያ ዘጋቢ “ እንደ ቆፈጣናው መንግሥቱ …….” በማለት ገለጸው ። 

‘አገር ወዳዱ መንግሥቱ! ጀግናው መንግሥቱ! ቆፈጣናው መንግሥቱ! ወዘተርፈ ‘ የተሰኙ  መፈክራዊ ሃረጎች   ስሰማና  ሳነብ  – እጅግ በጣም  ያመኛል ፣ድብርት ይሰማኛል (feel depressed) ። መልከ ጥፉ በስም ይደግፉ እንደሚባለው  ለመንግሥቱ ሃ/ማርያም በእንደነዚህ ዓይነት ቃላቶችና ሃረጎች የሚያሽሞነ       ሙኑና የሚያጋጌጡ እነማን ይሆኑ?

ውሻ በበላበት ይጮሃል እንደሚባለው  ፥ 

1) በመንግሥቱ የአገዛዝ ሥርዓት የሥልጣን ተካፋይ የነበሩ፣አገዛዙ የተመቻቸውና በአገዛዙ የተጠቀሙ( ባለሥልጣኖች፣ ግለሰቦች፣ካድሬዎች፣ ቡድኖችና  ቤተሰባቸው)  

2) መንግሥቱ ሥልጣን ላይ በነበረበት ወቅት ህጻናት የነበሩና ከዚያ በሃላ ተወለደው  (ሞያተኛ ወይም ኢ-ሞያተኛ  ጋዜጠኛ ፣ ፖለቲከኛ ፣ጦማርተኛ ወዘተ..) የሆኑ ። 

3) ስለመንግሥቱ ሃ/ማርያም በመንግሥቱ ደጋፊዮች የተዛባ ታርክ ተነግሯቸው  ሳያጣሩ ያንኑ ይዘው አደባባይ የሚወጡ  ወዘተርፈ ናቸው ። በርግጥ (ሂትለርም፣ ሞሰለኒም፣ ጀነራል ፍራንኮም፣ እስታሊንም፣ ኢዲያሚን ዳዳም ፣ ቦካሳም) ወዘተ.. ጥቂት ይሁኑ እንጂ ፀረ-ሕህዝብ ወዳጆች ነበሯቸው ።

መንግሥቱ ሃ/ማርያም  ቆፍጣና / ጠንካራ ገዢ ነበርን? የመንግሥቱ ቆፍጣናነት ምኑ ላይ ነበር? በምን አስመሰከረ? 

ሀ) ኤርትራ የተገነጠለው በማን አገዛዝ ነው? ሁለቱም የቀባህር ወደቦቻችንና የባህር በሮቻችን የተነጠቅነው በማን አገዛዝ ነው? በኤርትራ  መገንጠል  ሉዓላዊነታችን የተደፈረው  በማን አገዛዝ ነው? በኢሳያስ የተመራው ሻቤያ በወያኔዎች ታግዞ ቢቀማንም ፤ በዚያ ወቅት አገራችን የሚገዛው ማን ነበር? 

ለ) መንግሥቱ ወደ ጦርሜዳ የሚሄደው ለምን ነበር? የሠራዊቱን ሞራል ለመገንባት? ምክር ለመስጠ? አይዟሁ ለማለት? አይደለም። መንግሥቱ ወደ ጦርሜዳ ይሄድ የነበረው ፦ 

  • የትኛው ጀነራል፣ የትኛው ኮሎኔል፣ የትኛው ሺአለቃ፣ የትኛው ሻምበል ፣ የትኛው  መቶአልቃ፣ የትኛው የጦር አዛዥ ፣ የትኛው ብርጌድ ወዘተ..እያማኝ፣እያሴረብኝ፣ እያሳደመብኝ ወዘተ.ይሆን .እያለ በጦሩ ወስጥ ለስለላ ከሰገሰጋቸው  ካድሬዎችን -(ሚስጥርና  የሽኩቻ ወሬ  የየሚያሳብቁለትን ለመስማት/ለማዳመጥ 
  • መኮነኖችን በሚመሯቸው ሠራዊት ፊት ለመረሸንና ለማስረሸን
  • በሚመሯቸው  ሠራዊት ፊት  ፥ በሳንጃ ቂጣቸውን በመውጋት እና ለረዥም ዓመታት በውትድርና ሞያ ለፍተው ፣ ደክመውና ብቃት አስመዝግበው  ያገኙትን ማዕረግ  በመቀስ ከትከሻው  ለመቁረጥ 
  • በሚመራቸው  ሠራዊት ፊት በድንፋታ ፣በስድብ ፣በጥፊ በመምታት –  ስነልቦናቸውን፣ ስነ አእምሮቸውን፣ ቅስማቸውን/ሞራላቸውን  ለመስበር ወዘተረፈ ነበር መንግሥቱ ወደ ጦርሜዳ የሚሄደው ።
  • ከጅነራል እስከ የበታች መኮነኖች በንግሥቱ የጦር ሜዳ ካድሬዎች በጥፊና በቦቅስ ይመቱ ነበር
  • በጦር ሚዳ ሠራዊቱ ሚመራው በፖለቲካ ካድሬዎች እንጂ በጦር አዛዦች አልነበረም (ይህንን ለማረጋገጥ “…የጦር ሜዳ ውሎና አሳዛኝ ፍጻሜ…” በሻለቃ ንጋቱ እና ከሌሎችም በተጻፉ መጽሃፍት ማንበብ ይቻላል)።
  • መንግሥቱ ለሠራዊቱና ለካድሬዎች በገባበት ገብታችሁ ኢ.ሕ.አ.ፓን- ደምስሱ ፣ደብድቡ ፣አጥፉ ወዘተ..የሚል  ትእዛዝ  ይሰጥ ነበር እንጂ ወያኔን  አጥፉ የሚል አልነበረም ። ይህንን የሰማሁት  ከሻቤያዎችና  ከወያኔዎች  ጋር በተደረጉት ውጌያዎች ተሳትፈው  በህይወት ወደ አ/አ ከተመለሱት ወታደሮች ነው 

ሐ) አደጉ የሚባሉ አገሮች ሁሉ እድገት መሠረት ዘመናዊ ትህርትና በዘመናዊ ትምህርት የሰለጠነ  የሰው ሃይል መሆኑ ማንም አሌ የማይለው ነው ። እንደ ኢ.አ እስከ  1928 ዓ.ም ዘመናዊ ትምህርት የቀሰሙ ኢትዮጵያውያን አብዛኞቹ  ከ1928 -1933 ዓ.ም የነበሩት በጣሊያኖች ተጨፍጭፏል ። ከዚያ የተረፉትና ከደኽረ ጣልያን ወረራ  እስከ መንግሥቱ በትረ አገዛዝ የጨበጠበት ፣የኢትዮጵያ ሕዝብ ብዙ ነዋይ  አፍሶ በዘመናዊ ትምህርት የታነጹ፦

 1) ኢትዮጵያ ከኋ ቀርነት ወደ ዘመናዊ (የኢንዳስትሪ፣የኮምኒኬሸን፣የቴክኖሎጂ፣የግብርና፣የንግድ፣ የትራንስፖርቴሽን ወዘተ..ሥልጣኔ ለማሸጋገር 

2) በዲሞክራሲያዊ መርህ፣አወቃቅርና አሰራር የተመረጠ ሕዝባዊ መንግሥት እንዲመሠረት

 3) የኢትዮጵያ ሕዝብ ከነበረበት አስከፊ ድህነት ወጥቶ የተሻለ ማህበራዊ ሕይወት እንዲኖረው

4) ዘመናዊ ትምህርት ለሰፊዩ ገጠሩ ሕዝብ እንዲዳረስ እና መሬት ላርሶ አደሩ እንዲወል  ወዘተ.. ሲመኙና ሲታገሉ የኖሩ እንቁና ብረህ (enlightened)፤

  • የዩኒቭርስቲ፣የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት እና የአንደኛ ት/ቤት አስተማሪዮች፣ ኢኮኖሚስቶች፣

መሃንዲሶች፣ኬሚስቶች፣ የግብርና ሞያ  ሊህቃን ወዘተ.. 

  • እጅግ በጣም የሰከነ- ፖለቲካዊ፣ማህበራዊ ፣ዘመናዊ  ወዘተ..አስተሳሰብ የነበራቸው የዩኒቭሪሲቲና የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ተማርዮች
  • የሁለግብ በሽታ ሃኪሞች /ዶክተሮች (G P)፣ ቀዶ ጠጋኞች፣ ለተለያዩ በሽታዎች እስፔሻ ሊስቶች፣ የዓይን ሃኪሞች፣ የአእምሮ በሽታ ሊህቃኖች፣ ጠበቃዎች፣ የህግ ባለሞያዎች፣ነርሶች ወዘተርፈ
  • ለኢትዮጵያ  ሉዓላዊነት ትልቅ ባለውለታ  ሚኒስተሮች (አኪሉ ሃብተ ወልድ ዓይነቱ)
  • በዘመናዊ ትምህርትና በዘመናዊ የውትድርና ሞያ ከየትኛውም ያደጉ አገራት መኮነኖች የተሻለ እውቀት የነበራቸው   ምርጥ መኮነኖች (ፋንታ በላይና ተፈሪ ባንቲ ዓይነቶች) መንጥሮ፣ አገሪቱ ጀግና አልባ አድርጎና ለወያኔዎች  አስረክቦ ወደ ዚምቧቤ መጭ አለ ።
  • መንግሥቱን በሚነካ ፖለቲካ ከተጠረጠሩ ፤ ከ14 ዕድሜ እስከ አዛውንትነት እድሜ የደረሱትን ዜጎች በጥይት ተመተሩ
  • በቀበሌ ሱቅ ፦ዳቦ፣ስኳር፣ቡና፣ ሻይቅጠል ወዘተ..ጠፋ ወይም ተወደደ ሲሉ የተደመጡትን ሁሉ ተረሸኑ
  • አንድ ብቸኛ ልጅ የነበራቸውም ፣ስድስትና ሰባት ልጆች የነበርዋቸውም  ወላጆች ልጅ አልባ አደረጋቸው፣ህጻናት ወላጅ አልባ አደረጋቸው
  • መንግሥቱ ጸረ ጅግና ጸረ የተማረ ስው ነው ። ከሱ የተሻለ ትምህርት ያለው ሰው፣ ከሱ የበጠ የውትድርና  ማዕረግ ያለው መኮነን ማየት አይፈልግም ነበር ። 
  • አብረውት ከተሰለፉትና ቤተሰባቸው  ሳይጨምር ፤ በመንግሥቱ አገዛዝ (ያልተረሸነበት ፣የግፍ ሰቆቃ ያልተፈጸመበት፣ሞትና ሃዘን ያልገባበት ቤተሰበ) የለም
  • መንግሥቱ ሬሳ ሽጧል፤ በያንዳንዱ ሬሳ በያኔ  $250 ብር ( 125 U.S dollar) አስክፍሎዋል
  • ወላጆች የልጆቻቸውን ፣ ልጆች የወላጆቻቸውን ሞት ለቅሶ እንዳያለቅሱ  ከለከለ

 

 

ታዲያ የመንግሥቱ ቆፍጣናነት የቱ ጋ ይሆን?  የመንግሥቱ  ቆፍጣናነት ፦ መፈክሮች በማሰማት ፣የሰዎች ደም  ወይም ቀይ ቀለም  በጠርሙስ ተሞልቶ በጸረ አብዮት አደባባይ ላይ በማፈንዳት፣ የሚገደሉ ሰዎች ትእዛዝ በመስጠት አንድ የመንግሥቱ ደጋፊ የገደለ በሺ ጸረ መንግሥቱ ሃይሎች ሞት ይካሳልን መፈክር በማሰማት ፣ሁሉም ነገር እኔ አውቃለሁ ብሎ በመደንፋት፣ለስልጣን ያበቁት ጓድኞቹን  እያደባ በመንጠር  ወዘተ.. ነበር

 

የመንግሥቱ መገለጫዎች ፦ እጅግ በጣም ፈሪ፣ቡካታም፣ የራሱን ጥላ የሚጠራጠር፣ በጠመንጃ አፈሙዝ  ቤተመንግሥት (ለኔ ቤተጥፋት)  የገባ -የጎዳና ወሮበሮች ባህሪ ያለው ፣ ከሂትለር የከፋ ፋሽስት 

 

መንግሥቱ ሃ/ማርያም አንጋሾች፣ መንግሥቱ  አጼ ምኒሊክና አጼ ቴድሮስን አሳክለው፣ ጀግና አድርገው፣አገር ወዳድ አድርገው  ለአደባባይ ሲያሻሽጡት/ሲያቀርቡት ፤ በዚያ ሰቆቃና የመክራ ሥርዓት ያለፉ ኢትዮጵያውያን ፦ ለምን እውነቱን እንደማያወጡ፣ ለምን እንደማይከላከሉ፣ ለምን አሚን ብለው  እንደሚቀበሉ ይገርመኛል፤ ወይስ ያ ትውልድ  ሙቶ አልቆ  ይሆን? 

 

ከመንግሥቱ በኋላ ላለው ትውልድ ስለመግሥቱ  ያልተዛባና ትክክለኛ ገጽታ  የማስበጥ ሃላፊነት ያለብን ይመስለኛል።  ፋሽስቱ መንግሥቱ ሲሞገስ፣ሲውደስ፣ያልሰራውን ሠራ፣ ያላደረገውን አደረገ ሲባል ፣የእርሱ ያልሆነውን ክህሎት ሲሰጠው ወዘተ.. ስሰማ ዝም ማለት ስለማያስችለኝ ፤ከዚህ ጽሁፍ በሰፋም ባነስም  መጠንና ይዘት፤  ስለመንግሥት ደጋግሜ ጽፌአለሁ። 

Filed in: Amharic