>

ከህውሃት ጋር የመደራደር አደገኛ የሚያደርጉት አስር ምክንያቶች...!?! (ኤርሚያስ ለገሰ)

ከህውሃት ጋር የመደራደር አደገኛ የሚያደርጉት አስር ምክንያቶች…!?!

ኤርሚያስ ለገሰ

የዩጋንዳው ፕሬዝዳንት ሙሶቬኒ “ድርድር መኖር አለበት” ብለው ነበር። አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ደግሞ የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ኦሊሶንጐ ኦባሳንጆ ህውሃትና መንግስትን ለማደራደር አዲስ አበባ መግባታቸውን ዘግቧል። Reuters በበኩሉ በርካታ የአውሮፓና የአፍሪካ መንግስት ከመጋረጃ ጀርባ ለማደራደር ጥረት እያደረጉ መሆኑን አትቷል። በአጠቃላይ መልኩ የተደራደሩ ሃሳብ እያየለ መጥቷል።
አሁን ጥያቄው በሆነ አጋጣሚ ድርድሩ ቢጀመር ምን አደገኛ ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል የሚለው ነው። እነዚህ አስር ምክንያቶች ይታዩኛል፣
፩: ጠቅላይ ሚኒስትሩን “ቃል-አባይ” ያደርጋል። በጦርነቱ ላይ ከጠሚሩ የሚተላለፉ መልዕክቶች አመኔታ ያጣሉ። (ወትሮም ጠሚሩ የማይታመኑ እና እንደ አየሩ ሁኔታ የሚናገሩ መሆኑ ልብ ይሏል።)
፪: ጦርነቱን የደገፉት በርካታ ኢትዮጵያውያን “ህውሃት ከምድረ-ገጽ ይጠፋል” ከሚል እሳቤ ነው። ድርድር ከተጀመረ ህውሃት በፓለቲካው ዘርፍ አፈር-ልሶ ይነሳል። ድርጅቱ በሽብርተኝነት አይፈረጅም። አመራሩ በጄኖሳይድ አይከሰሱም። ንብረታቸውም አይወረስም።
፫: የአማራ ማህበረሰብ ለአራት አስርተ አመታት የትግል-ማዕከል ብለው የተዋደቁለት “የወልቃይት-ጉዳይ” ከአጀንዳነት ይቀነሳል። የአማራ ልዩ-ሃይልና ሚሊሻ ነባር ርስቴን ማስመለስ በሚል ያፈሰሰው ደም “ደመ-ከልብ” እንደሆነ በመቁጠር የመከዳት ስሜት ይሰማዋል።
፬: መከላከያው የፓለቲካ ውሳኔ የመቀበል ግዴታ ቢኖርበትም በውስጡ የመካድት ስሜት ይፈጥርበታል።
፭: የመጀመሪያው ድርድር የሚካሄደው ብልጽግና እና ህውሃት መካከል ስለሚሆን የህውሃት አመራሮች የሞራል የበላይነት ይይዛሉ። ከወዲሁ በፕሮፐጋንዳ ማሽናቸው “ዓብይ አህመድ ዳግማዊ ፀሀይ-ግባት” ይከናነባል ማለት ጀምረዋል።
፮: ድርድሩ “ሕገ-መንግስቱ ይከበር!” ወደሚል ተንሸራቶ ስለሚወድቅ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ገደል ይገባል። የጐሳ ፌዴራሊዝሙ ተጠናክሮ ይቀጥላል።
፯: የቀጣዩ የኢትዮጵያ ፓለቲካ መደራደሪያ አጀንዳዎች ህውሃት ከዴሞክራሲ ኃይሎች የሰረቀውን( ለጊዜው ማታለያ ) ይዞ ስለሚመጣ በተለያዩ የውስጥና የውጭ ኃይሎች ቅቡልነት ያገኛል። እነዚህ ከዴሞክራሲ ኃይሎች ለጊዜው ማምለጫ የተነጠቁ አጀንዳዎች : የፓለቲካ እስረኞች በሙሉ ይፈቱ፣ ሁሉም የፖለቲካ ፓርዎች የሚሳተፉበት ድርድር ይካሄድ፣ ገለልተኛ የባለአደራ መንግሥት ይመስረት የሚሉ ናቸው።
፰: በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ከብልጽግና እና ህውሃት ውጪ ሌላው ድርጅት እና ፓርቲ ትርጉም አልባ (ኢሪሊቫንት) ይሆናል።
፱: ኦሮሙማ በተለይም ወታደራዊው የኦነግ ክንፉ ተጠናክሮ ይወጣል።
፲: በህውሃትና የኦሮሚያ ብልጽግና (ኦህዴድ) ስምምነት አዲስ አበባ የኦሮሙማ ባለቤት ትሆናለች።

ህውሃትና ኦነግ-በሽብርተኝነት ይፈረጁ!

•የህውሃትና ኦነግ-አመራሮች በጄኖሳይድ-ይከሰሱ!

•ከህውሃትና ኦነግ ጋር መደራደር ፀረ ኢትዮጵያዊነት-ነው!

Filed in: Amharic