>
5:13 pm - Monday April 19, 6726

ፈረንሳይና ኢትዮጵያ . . .  ምንና ምን?! (አሰፋ ሀይሉ)

ፈረንሳይና ኢትዮጵያ . . .  ምንና ምን?!

አሰፋ ሀይሉ

 

“የሰው ሀገር መሪውን ማክሮንን ‹‹እስልምናዬን ነካብኝ›› ብለህ አወገዝከው? አሉ¡¡¡ ምነው አጠገብህ ያለውን የራስህን አራጅ – ሙርተድ –  በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖችህ በአራጆች ሲጨፈጨፉ እጁን አጣጥፎ ‹‹በለው ግደለው!›› ያለውን አብይ አህመድን ማውገዝ ነው የሚቀድመው? ወይስ…   ምነው ግን  እሱን ረሳኸው? ስሙ ያንተን ስለሚመስል? ወይስ…?!?” 
 
         (- ጥያቄ ለሠልፈኛው!)
ሰሞኑን አንድ ያሜሪካ ፕሮፌሰር የጻፈውን መጽሐፍ እያነበብኩ ገርሞኝ አላባራ አልኩ፡፡ ‹‹ዘ ዳምበስት ጀነሬሽን›› ይላል ርዕሱ፡፡ ‹‹ድንዙዙ ትውልድ›› አልኩት ለራሴ፡፡ ጫን ብዬ ከተረጎምኩት ግን ‹‹ድንጋይ-ራሱ ትውልድ›› ሊሆንብኝ ሆነ፡፡ እና ተውኩት፡፡ ይህ የዲጂታልና የዓለማቀፍ የዜና አውታሮች የቃኘው (ያወናበደው፣ አሊያም ያናወዘው) ትውልድ እውነትም ‹‹ዳምብ›› ቢባል (ብንባል) አያንስበትም መሠለኝ፡፡ ደራሲው ‹‹ዳምብ›› ያለው ወዶ አልመሰለኝም፡፡ ብዙ ምክንያቶች አሉት፡፡ ብዙ ጊዜ የሚመጡብኝን ሂሳዊ ሀሳቦች ነው ከሚገርሙ ማዕዘኖች እየመተረ ያብራራልኝ፡፡ አሁን የእኛ ሀገር አስገራሚ ጉዶችን ስመለከት፣ ከመጽሐፉ ጋር ተገጣጠመብኝ፡፡ አሁንስ ድንዙዝነታችን ጥግ አጣ፡፡
ስንት ሺህ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን – አጠገባችን – እዚያው ሀገራችን ላይ – ‹‹መንግሥት›› ነኝ በሚለው ዓይንያወጣ ኃይል ሽፋንና ከለላ እየተሰጣቸው – ‹‹ቄሮ›› ነኝ በሚሉ ወሮበላ ቀውሶች – በጠራራ ጸሐይ ሲታረድ፣ ንብረቱ ሲወድም፣ ከኖረበት ቀዬ ሲፈናቀል፣ ዕለት በዕለት በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች ‹‹አማራ›› ‹‹ነፍጠኛ›› እየተባለ፣ ሰው እንደ እንስሳ በዘሩ እየተመረጠ በቀስት ሲወጋና በቢላዋ ሲታረድ፣ በጥይት በጅምላ ሲረሸን – እያየን፣ እየሰማን፣ ዕለት ዕለት ትኩስ የሐዘን ዜና እየሰማን – ያልሞቀን፣ ያልበረደን፣ ያላንገበገበን ዜጎች – አሁን የምንሰራው ስናጣ – እና ድንዙዝነታችን ጣራውን ሲነካ – ባህር ተሻግረን አውሮፓን አልፈን – ሰው ሀገር ገብተን – የፈረንሳዩ መሪ ኢማኑኤል ማክሮን ቤተክርስትያን ውስጥ ጭምር ገብተው የሴቶችን አንገት ያረዱ፣ በሐይማኖትና በጥላቻ የሰከሩና አቅላቸውን ያጡ ሰዎችን በከረሩ ቃላት ስላወገዘ – አዲስ አበባ ቤቴል ላይ ተሰባስበን – ማክሮንን የሚኮንን የቁጣና የተቃውሞ ሰልፍ አደረግን! – ሲባል ስሰማ – ስመለከት – የምለው ጠፋኝ! ኡኡኡኡኡይ…!! ‹‹የት ሂጄ ልፈንዳ!›› ነው ያለው ሰውየው?
የቁጣው ሰልፍ ምክንያት ደሞ ማክሮን ሐይማኖታችንን አናናቀ፣ ነቢያችንን ነካ – እኮ ነው! ወንድሜ!? ከሳምንታት በፊት በፓሪስ ከተማ አፍንጫ ሥር አንድ መምህር የነቢዩ መሀመድን (ሰ.ዓ.ወ.) የካርቱን ሥዕል በወረቀት ላይ ሥሎ በክፍል ውስጥ ‹‹የመናገር ነፃነትን ቀን›› አስመልክቶ በተዘጋጀ ክፍለጊዜ ላይ ለተማሪዎቹ ስላሳየ – በአንድ እስላም አክራሪ ሰው ምንድነው የተደረገው? አንገቱ በቢላዋ እየተገዘገዘ ነው የታረደው፡፡ ያውም እየተቀረጸ፡፡ እንዴ!? አውሬ እንኳን ሲበላህ እኮ የዚህን ያህል ጥላቻና ጋጠወጥነትን ተላብሶ እኮ አይመስለኝም! እንዴ! እንዴት ያለ እብደት ነው? ሐይማኖት ሰብዓዊነትን እንዲህ ካደነዘ ‹‹ባይበላስ ቢቀር››?፡፡ ማክሮን ታዲያ ምንድነበር ያደረገው? ‹‹ኢሚዲዬትሊ›› – ደቂቃ ሳያባክን – ያንን አራጅ ነፍሰበላ የገባበት ገብቶ አድኖ አገኘው፡፡ እጅ ሥጥ ተባለ በፖሊስ፡፡ አራጁ ግን ተኩስ ከፈተ፡፡ ‹‹ጨዋታህ ገና አላለቀም?›› ብለው – እዚያው ግንባሩን ብለው ገላገሉት፡፡
አሁን ደሞ መጡ አክራሪ እስላሞቹ፡፡ ባለፈው ኒስ የምትባለዋ የፈረንሳይ ከተማ – በትልቅ መኪና የሰውን ልጅ መንገድ ለመንገድ እየረመረመ ጨፈላልቆ የጨረሰን አውሬ አሸባሪ ያስተናገደች ከተማ ነች፡፡ አሁን ደሞ – ያ አስተማሪውን ያረደው እስላም በተገደለ በቀናት ልዩነት – በዚያች በፈረደባት በኒስ ከተማ – ኖትርዳም ባሲሊካ የሚባለው ታዋቂ ቤተመቅደስ ውስጥ ቢላዋ የያዘ አራጅ አክራሪ ሰተት ብሎ ገብቶ በሰላም ፈጣሪዋን የምታመሰግንን ወይዘሮ አንገቷን በምዕመኑ ፊት ገዝግዞ አረዳት፡፡ እንዴ? የሆነ ግን ዓለማችን ላይ የተረጨ የሆነ የቄሮ መርዝ አለ እንዴ ግን? ከመሬት እየተነሳህ ሰዎችን እረድ እረድ የሚል? እንደ ቫምፓየር የደም ጥማት የሚለቅብህ? – የምሬን እኮ ነው፡፡ እንጂ የሰው ልጅ በጤናው እንዲህ ያለ አስነዋሪና የሰው ልጅ ያደርገዋል ተብሎ የማይታሰብ አውሬነት አይፀናወተውማ!!
ደሞ ሰውየው (ከቱኒዚያ ወደ ፈረንሳይ የመጣ እስላም ነው ተብሏል ግለሰቡ) – ሰውየው – እኮ አንዲት ሴትን አርዶ አልበቃውም፡፡ ሌላዋንም ጉሮሮዋን አንቆ በቢላዋ ሊያርዳት ጀምሯት ነበር፡፡ ሰዉ ሆ ብሎ ሲያስጥለው ራሱ – ሌላ ሴትን ደሞ ይዞ ይታገል ነበር፡፡ ይሄ ልክፍተኛ ሰይጣን! የፈረንሳዩ መሪ ኢማኑኤል ማክሮን – ሰብዓዊ ዓዕምሮ እንዳለው ሙሉ የሰው ልጅ – የሰው ልጅ መታረድ የሚዘገንነውና የሚያንገፈግፈው ሰው ስለሆነ – አሁንም ደቂቃ አላባከነም – ሰባት ሺህ ፖሊስ ነው በደቂቃዎች ውስጥ የእስላም አሸባሪዎቹ በቢላ ሰውን የመውጋትና መሣሪያ የመተኮስ ሙከራ ባደረጉባቸው ሶስት ከተሞች ያሰለፈባቸው፡፡ ሰባት ሺህ ፖሊስ፡፡ ሶስት አራጆችን ሊፈልግና ሊያስቆም ነው የተሰማራው፡፡ በደቂቃዎች ልዩነት፡፡ አራጁን እዚያው ብሽሽቱን በጥይት ቦትርፈው አጋደሙት፡፡ ሌሎቹን አንዱን ቅልጥሙን ቀልጥመው፣ ሌላውን የደገነውን መሣሪያ ገና ቃታውን ለመሳብ እንኳ ሳይታደል ነው – ባፍጢሙ ደፍተው ከነህይወቱ የማረኩት፡፡ ማክሮን ማለት ይሄ ነው! ጀግና! የዜጋ ሞት ተቆርቋሪ! አኩሪ ደም-መላሽ መሪ! የሰው ልጅ! ምርጥ የሰው ልጅ!
ይሄን የሰው ልጅ ነው እንግዲህ የኛ ድንዙዞች በቤቴል ተሰብስበው የሚያወግዙት፡፡ ምክንያት? እስልምናን ነካብን! የነብያችንን ክብር ነካብን! …. ወዘተ፡፡ ወቸ ጉ….ድ! ድንዙዙ ትውልድ – ትሰማኛለህ? አንተ አልነበርክም ወይ – ሶስት መቶ ኢትዮጵያውያን ታርደው፣ ተፈላልጠው፣ ተተልትለው፣ በጠራራ ፀሐይ ሲገደሉ – አራጆቹን አይዟችሁ እያሉ – ከተሞቹን ከፖሊስና ከጦርሠራዊት እንቅስቃሴቴ አፅድተው – ሲያስገድሉና ሲያስጨፈጭፉ የነበሩትን የክልል መሪዎች አቅፎና ደግፎ አለሁ የሠላም ኖቤል ተሸላሚ፣ የሀገር መሪ ነኝ የሚለውን አብይ አህመድ አሊን – ስሙ የእስላም ይመስላል በሚል ብቻ – ስታሽቃብጥለትና ሺኅ ዓመት ይግዛኝ ስትል የነበርከው? አንተ ራስህ አይደለህም ወይ ትውልዱ? ንገረኝ እንጂ! እና የራስህ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአራጆች ሲጨፈጨፉ እጁን አጣጥፎ ‹‹በለው ግደለው!›› ያለውን አብይ አህመድን ማውገዝ ነው የሚቀድመው? ወይስ እዚያ ማዶ ሀገር ተሻግረህ – ያልዋልክበትን ኩበት መልቀሙ ነው የሚቀድመው?
ለመሆኑ ሩቅ ካለውና ከማትደርስበት፣ ከነመፈጠርህም ከማያስታውስህ ከማክሮንና – አጠገብህ ተጎልቶ ‹‹እኔን ብትነኩ እዚህ አዲስ አበባ ላይ በአንድ ቀን መቶ ሺህ ሰው ታርዶ ያርዳል!›› እያለ በአራጆቹ እያርበደበደ ከሚገዛህ ማክሮን – ለነቢዩ መሀመድ (ሰ. ዓ. ወ.) ትዕዛዝና ምግባር የቀረበው ማነው ለመሆኑ? እስልምና ወገኖችህ ሲታረዱ መሪው እጁን አጣጥፎ ይመልከት ይላል? እስልምና ዜጋህን በአራጆች እፈጅሃለሁ እያልክ እያስፈራራህ ግዛ ይላል? ለመሆኑ የተቃውሞ ሰልፍ ከወጣህበት ከኢማኑኤል ማክሮንና እዚሁ ፊትህ ከተጎለተው አብይ አህመድ አሊ የትኛው ነው እስልምናን ያንቋሸሸው? ማክሮን ሲጀመር ካፊር ነው! አብይ አህመድ አሊስ? ሙርተድ ፊጥሪ አይደለም ወይ? የአባቱን ሐይማኖት የከዳ – ከካፊሩም በላይ እስልምናን ክዶ ያንቋሸሸ – የወጣለት ሙርተድ!?
እና ድንዙዙ ትውልድ! ንቃ! ሩቅ ሄደህ ባህር ተሻግረህ የሰው ሀገር መሪ ዓይን ላይ ጣትህን ከመጠንቆልህ በፊት – መጀመሪያ አጠገብህ ላይ ካለው የምታመልከው መሪ ዓይን ላይ ያለውን ጉድፍ ጠንቁል!! ሩቅ ሄደህ ዜጎቹን ከአውሬ አራጆች የተከላከለን የሰው ሀገር ድንቅ መሪን ከመዝለፍህ በፊት – የራስህን ሀገር የአውሬ አራጆች የበላይ ጠባቂ፣ የራስህን ሀገር በአውሬ አራጆች እያስፈራራ የሚገዛህን መሪ ቀና ብለህ ተመልከት! ማክሮን ይቀናበታል እንጂ – አይኮነንም! የሚኮነነውን አጠገብህ ያለውን ፈልግ! የምለው ይሄንን ነው!
በ ‹‹ዘ ዳምበስት ጀነሬሽን›› መጽሐፍ እንገናኝ!
 
ኢንሻላህ!
አበቃሁ!
Filed in: Amharic