>

ኤርሚያስ ለገሰ:- ለጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

በቅድሚያ መመጽሓፉን ጊዜ ሰጥተህ በማንበብ አስደማሚ ምልከታ በመስጠትህ ከልብ አመሰግናለሁ ። የተጻፈበትም አንዱ አላማ ይህ ስለሆነ። ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በእይታህ ላይ እነዚህ ጉድለት ይታይባቸዋል ብለህ ያነሳኸው እና የወደፊት ግምቶችህ ላይ የተወሰነ አስተያየት ለመስጠት የሚጋብዙ ስለሆነ ትንሽ ማለት ፈለኩ። በዚህ አጋጣሚ ሌሎች በመጵሀፉ ይዘት ላይ ዝርዝር ግምገማ ላደረጉ ሰዎች ምስጋናዬ ይድረሳችሁ። ለእያንዳንዱ አስተያየት መስጠት ከጊዜ አኳያ በጣም አስቸጋሪ ስለሆነ የማልዘልቅበትን መንገድ ልጀምረው አልፈለኩም ። የጋዜጠኛ ተመስገንን በልዩ ሁኔታ መመልከት የፈለኩበት የራሱ ምክንያቶች አሉት። ተመስገን ሀገር ቤት ባለ አስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ በድፍረት መጵሀፉን ማንበቡን በአደባባይ ገልጶ በመጵሄት ሳይቀር መክተቡ ልዩ ያደርገዋል ። አንዳንድ የቀድሞ ” የትግል ጓዶቼ! ” በሚስጥር ቢሮ እየቆለፉና እቤታቸው እየደበቁ ባነበቡበት ሁኔታ የተመስገን ፊትለፊት ማውራት ምንያህል የህሊና ራስ ምታት እንደለቀቀባቸው ማሰቤ ሁለተኛ ምክንያት ነው( ቢያንስ ሁለት “ሚኒስቴር ደረጃ ያሉ ሰዎች ” የተፃፈው ሐቅ ስለሆነ ማስተባበል አይቻልም ” የሚል አስተያየት መስጠታቸውን እርግጠኛ ከሆነ ምንጭ ሰምቻለሁ ። ማረጋገጥ ለምትፈልጉ ” የዲሞክራሲ ሐይሎች” በውስጥ በኩል ጠይቁኝ) ከዚህም በተጨማሪ ከወደ ካሊፎርኒያ የደረሰኝ ዜና የስርአቱ ደጋፊ የሆኑ ሰዎች መጵሀፉን ሲያዙ በአንድ ጊዜ እስከ ሀምሳ ኮፒ መጠየቃቸውን ነበር( መረጃውን ያደረሰኝ የዘወትር ተባባሪዬ ሔኖክ የሺጥላ ” እነዚህ ሰዎች ሊያነቡት ነው ወይስ ሊያቃጥሉት?” የሚል ጥያቄ ቢጠይቀኝም መልስ መስጠት አልቻልኩም ። መልስ ካላችሁ ተባበሩኝ።)  ሦስተኛው ምክንያት የተመስገን ፅሁፍ ሐገር ቤት በመጵሄት መልኩ ቢሰራጭም የመለስ ” ትሩፉቶች” ግን ህጋዊ በሆነ መንገድ እንድትባዛ ብትጠየቅም ሐገር ቤት ያሉ (ጥያቄው የቀረበላቸው) አሳታሚዎች ፍቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል ። በዚህም ምክንያት ወደ ህዝቡ በሰፊው መሰራጨት አልቻለም። ( በዚህ አጋጣሚ ነጳነት አሳታሚ ኢትዮጵያ ለሚያሳትም ሰው ስክሪፕቱን በነፃ ለመስጠት ፍላጐት እንዳለው ገልጶልኛል።) ይህን እንደ መንደርደሪያ ካነሳሁ ዘንዳ የጋዜጠኛ ተመስገን ምልከታዎች ላይ ያሉኝን አስተያየቶች ላስቀምጥ።

1• “መፈንቅለ መንግሥት”

ተመስገን ከሐገር የወጣሁበት ዋነኛ ምክንያት በአንድ ወቅት የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተደርጓል ብዬ መናገሬ አቶ መለስን እንዳስቆጣው እና አቶ በረከት ይህን ተከትሎ ያለስራ እንዳንሳፈፈኝ፣ በዚህም ምክንያት ቅሬታ ቋጥሬ በትምህርት ሰበብ ከሐገር መኮብለሌን ገልፆአል ። ይህን ክስተት በመጵሀፉ ላይ መገለጵ እንደነበረበት አመላክቷል ።ይህ የተዛባ መረጃ ነው። ኢንፎርሜሽኑ ከውስጥ ወደ ውጭ ስለሆነ መዛባቱ ብዙም አልገረመኝም።

ጋዜጠኛ ተመስገን በመጵሀፉ የመጀመሪያ ገፅ ላይ ” የአሳታሚው ማስታወሻ” የሚለውን ክፍል ያነበበው አልመሰለኝም ። አሳታሚዎቹ ግልፅ በሆነ ሁኔታ በመጀመሪያው መፅሐፍ ትኩረት የተደረገባቸውን የአዲሳአባና ተያያዥ ጉዳዬች ብቻ እንደሚያሳትሙ ፣ በቀጣይ በሌሎች ጉዳዬች ( መፈንቅለ መንግስቱን ጨምሮ) እንደሚመለሱ ገልፀዋል።

በማሰከተል ” የመንግሥት ግልበጣ” የምትለው ማእከላዊ መልእክት ጣጣ እንዳመጣችብኝ መገለጱ ነው። እንደ እውነቱ ከሆነ ውሸት የመናገር ፍላጐት ቢኖረኝ ኖሮ ይህን የተመስገን አስተያየት ልክነው እል ነበር። ይህን የሚያክል ሀገርና አለም የሚያናውጥ መልእክት ቀርጬ የማስተላለፍ ስልጣን ቢኖረኝ ኖሮ ፣ የሃገሪቷን ስልጣን ” ከትግራይ የፈለቀው ገዥ መደብ” ጠቅልሎ ይዞታል የሚል አንደበት አይኖረኝም ነበር። እንደዚህ አይነት ማእከላዊ መልእክት የመቅረጵ ሚና ትላንትናም ሆነ ዛሬ እኔ፣ ሽመልስ ከማል፣ሬድዋን ሁሴን የለንም ። ጠቅላይ ሚኒስትር ሐይለማሪያምም የላቸውም / አይኖራቸውም ። በመሆኑም ከ ” መፈንቅለ መንግስት” ወደ ” ባለሥልጣናት ግድያ” ከዛም ወደ ” ቀቢፀ ተስፉ ” የሚል መልእክት የተቀረፀው ከአንድ ግለሰብ ነበር። መቼም ለምን? እንዴት? ምን ለማትረፍ የሚለው ጥያቄ አሁን እንደማይነሳ ተስፉ አደርጋለሁ ።

በማስከተል የአሜሪካ ጉዞዬን በተመለከተ ትምህርት የሚባለው መንግሥት ተደናግጦ በመጀመሪያው ሰሞን ያስተላለፈው ነበር ( በቅርብ ቀን ደግሞ ሌላ ነገር ብለዋል።) ሲጀመር ወደ አሜሪካ እንደምመጣ የተነገረኝ ኮሙዩኒኬሽን ጵ/ ቤት ከመቋቋሙ በፊት አደረጃጀቱን ለማስተካከል ስለ “Situation Room” አሰራር ለመመልከት አስቀድሞ የተያዘ ፕሮግራም ነበር። እኔ ብቻ ሳልሆን ከውጭ ጉዳይም ሌላ ሐላፊ አብሮኝ ነበር። በታህሳስ የታቀደው ጉዞ በአጣዳፊ ስራዎች ምክንያት ተላልፎ ሰኔ መጨረሻ ተቆረጠ።በርግጥ እንደ ማስታወሻ ፀሐፊ እስከ ሰኔ መቆየቴ አልከፉኝም( ድርጊቶቹ የግድ መፈፀማቸውና ሰለባዎች መኖራቸው እስካልቀረ ድረስ።) ወንድም ተሜ! መቼስ እንደራስህ የምትወዳቸውን እስክንድርና ሲሳይ አጌና ከውስጥ ወደ ውጭ ምን አይነት ሴራ ሲጠነሰስባቸው እንደነበር መስማት ትፈልጋለህ፣ መቼስ! የክቡር ዶክተር አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ የቀብር ስርአት ላይ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት አታካራ መስማት ትፈልጋለህ( አንተም ቢሆን በፍትህ ጋዜጣ ላይ ” ለምን አባረህ በለው ያንን አመጸኛ… ” ብለህ የጳፍከውን የፀቡ አንድ ክፉይ መሆኑን ቀብድ ያዝልኝ ፣ መቼስ! የአልበሽር ፣ የብርቱካን ሚደቅሳ፣የቴዲ አፍሮ፣… ወዘተ ጉዳዬች የወቅቱን የፓለቲካ ምህዳር አጣበውት እንደነበር አይዘነጋም። እናም ስለእነዚህ እና ሌሎች ጉዳዬች ለማውጋት እድሉን በማግኘቴ ጊዜውን እንደባከንኩ ይቆጠር ይሆን?

2• የፍትህ ጋዜጣ ባልደረባ ስለነበረው ማስተዋል ብርሐኑ በተመለከተ፣

ጋዜጠኛ ማስተዋል እንደገለፀው ቢሮ ጠርቼ አናግሬዋለሁ። እንደ ማስፈራራትም ከተመለከተው የስርአቱ ባህሪና እኔም የዛ ስርአት ውላጅ ስለነበርኩ ከዛ ውጭ ልሆን አልችልም። ለደረሰበት የስነ ልቦና ጫና ይቅርታዬን አድርስልኝ።( በነገራችን ላይ ስርአቱ ውስጥ በነበረኝ አስተዋጽኦ ይቅርታ መጠየቁ ችግር ያለብኝ ሰው አይደለሁም ።በተለይ በግለሰብ ደረጃ ከይቅርታም አልፌ በመጵሀፉ ምእራፎች መታሰቢያ ያደረኩት አለ። ” እውን ታሪክ ራሱን ደገመ? ” የሚለውን ምእራፍ ልብ ይሏል።)  ነገር ግን ከሃላፊነት ራሱን እንዲያገል ጠይቆኝ ነበር የሚለው ትክክል አይደለም ። እንደውም በወቅቱ የነበረው አቅጣጫ ጋዜጠኛን ወደ ኢህአዴግ መሳብ ስለነበር በተቃራኒው ሊሆን ይችላል ። መቼስ ወንድም ተሜ!ከፍትህ ጋዜጣ ጋር ኢሕአዴግ ለምን ተጣላ? ጋዜጠኛ ማስተዋልን በምን ጉዳይ አናገርኩት? ጋዜጣው ላይ ለምን እርምጃ ተወሰደ ( የነበርኩት ጥንስሱ ላይ ነበር)የሚለውን ቁምነገር አሁን እንደማትጠብቅ ተስፉ አደርጋለሁ። በነገራችን ላይ በጋዜጣህ ላይ እኔና ጋዜጠኛ ሳምሶን ( ካልጠፉ ሰው!!) አጃምላችሁ ” ሚኒስትር ዴኤታውና ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞ ሊከሰሱ ነው!” ብላችሁ በፊት ገፅ ያወጣችኃት በሀገረ አሜሪካ ኢምግሬሽን ጵ/ ቤት የጥያቄ መአት አዥጐድጉዳለች። ሂሳብ ማወራረድ ሳይጠይቅ አይቀርም!! እውነት እውነት እልሃለሁ የበግ ለምድ ከለበሰው ተኩላና ከጅምሩ ከምጠየፈው ሰው ጋር ማጃመላችሁ አሳዝኖኛል ። ጋዜጣዋ የወጣች እለት ለእሱ የወገንተኝነት ማረጋገጫ ብስራት፣ ለእኔ ደግሞ ሐዘን ነበር።እውነቴን ነው የምልህ ጋዜጠኛ (?) ሳምሶንን ኢህአዴግ ቢሮ ጀምሮ እጠየፈዋለው። ታዲያ እኔ ብቻ እንዳልመስልህ?…

3• የፓለቲካ ሁለተኛ እድል

ይህቺ አስተያየት የአንተ አይደለችምና ጣላት ። ነው ካልከኝም በድፍረት እነግርሀለሁ ። ተሳስተሀል። ይህ አጀንዳ ሆን ተብሎ በኢህአዴግ እና እጅግ በጣም ጥቂት የራሳቸው ሚና ያነሰ የመሰላቸው ( self ego) ባላቸው ሰዎች የሚቀነቀን ነው። አልፎ አልፎም ” የማንነት ሰርተፍኬት ሰጪና ነፉጊ ” አድርገው ራሳቸውን ከቆጠሩ ግለሰቦች የሚመነጭ ነው። ከኢህአዴግ ውጭ ያሉት የተዛባም ቢሆን ምክንያትና ተጨባጭ ተሞክሮ ስላላቸው የሚጣል አይደለም ። ተገቢ የማይሆነው ኢህአዴግ ይህን እንደ መደላድል እንዲጠቀም ለም መሬት ሆነው ማገልገላቸው ነው። ወንድም ተሜ! ወጋችን ካንተ ጋር ስለሆነ ወደዛው ልመለስ ። እስቲ አንድ ጥያቄ ልጠይቅ? ከዚህ በፊት ከኢህአዴግ ጋር ከሰሩ እና ጥለው በመውጣት ተቃዋሚን ከተቀላቀሉ ግባብዳ ካድሬዎች ላይ ይህን እኔ ላይ ያነሳኸውን ጥያቄ አንስተሀል? ግራም ነፈሰ ቀኝ እኔን በተመለከተ የየትኛውም ፓለቲካ ፓርቲ አባል አይደለሁም። አባል ያልሆንኩት ለጊዜው የድርጅት ተልእኮ የመሸከም አቅም ስለሌለኝ ነው ።ከዚህ በተጨማሪም ለተወሰነ ጊዜ ( ቢያንስ የጀመርኳቸውን መፅሐፍት እስክጨርስ) ያለድርጅት ተጵእኖ ነፃነቴን ጠብቄ መኖር ስለምፈልግ ነው። የድርጅት አባል መሆን ( በተለይ የተቃዋሚ) ቁርጠኝነት ፣ የአላማ ጵናት፣ ጊዜን መስዋዕት ማድረግ፣ ግለኛ አለመሆን… ወዘተ ይጠይቃል ። ለእንደዚህ አይነት ሰዎች( የትኛውንም የትግል ስልት ለሚጠቀሙ ) ልዩ አክብሮት አለኝ። መደገፍ አለባቸው የሚል እምነት አለኝ። እንግዲህ በመጀመሪያው ምልከታህ ላይ ያሉኝ አስተያየቶች ከሞላ ጐደል እነዚህ ናቸው። ሁልግዜም የተላበስከውን የቁርጠኝነት ፀጋ አብሮህ እንደሚዘልቅ እምነቴ ነው።

Filed in: Amharic