>

የብርሃነ መስቀል አበበ ሰኚ አስቂኝ  ጭውውት በOMN አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)

የብርሃነ መስቀል አበበ ሰኚ አስቂኝ  ጭውውት በOMN

አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)


ብርሃነ መስቀል አበበ ሰኚ የሚባለው ዐይነ ደረቅ አክራሪ ብሔርተኛ “አማርኛ በኢትዮጵያ 29 በመቶ ብቻ ተናጋሪ ሲኖረው ኦሮምኛ ግን 71 በመቶ ነው፡፡” እያለን ነው፡፡ የት ሄዶና መቼ ይህን ጥናት እንዳደረገ አልገለጸም፡፡ ስድስት ሚሊዮኑን ትግሬ፣ ስድስት ሚሊዮኑን ሶማሌ፣ ስንት ሚሊዮኑን ደቡቤ፣ ስንት ሚሊዮኑን ሽናሻ፣ አገው፣ አኙዋክ፣ በርታ፣ ጉሙዝ ወዘተ. ከአማርኛው ይሁን ከኦሮምኛው የቋንቋ ቅርጫት በየትኛው ውስጥ እንደከተታቸውም አልጠቆመም – ፍጹማዊ የኅሊና መታወር ማለት ይቺ ናት እንግዴክ፡፡ በዚህ ሰውዬ ጥናት መሠረት – ይህንን ከእንስሳም የወረደ ስብዕና ሰው ብሎ መጥራት እንኳን ይቸግረኛል በውነቱ –  ከኢትዮጵያ ሕዝብ 71 በመቶው ኦሮሞ ሲሆን 29 በመቶው ደግሞ አማራ ነው፡፡ አዲዮስ ሸዋ! አዲዮስ የለማ አገር ቅምብቢት! አዲዮስ ትላልቅ ከተሞች! አዲዮስ ጎንደር፣ ወሎና ጎጃም! አዲዮስ ፊን… ማናት አዲስ አበባ! 

በጣም አስቂኙ የዚህ ጅል ሰውዬ ድርጊት ይህን ነገር መናገር የነበረበትና ያለበት “ብዙ አድማጭ” ባለው ወይም እንዳለው በራሱ ጥናት በደረሰበት በኦሮምኛ ቋንቋ መሆን ሲገባው በአማርኛ መሆኑ ነው – ሊያውም ጥርት ባለች አማርኛ! አማርኛን የሚችለው የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር 29 በመቶ ብቻ ሆኖ ሳለ ለዚያውም በጽንፈኛ ቲቪ እንዴት በአማርኛ እንደሚናገር ራሱ ዕንቆቅልሽ ነው፡፡ በጥናቱ እውነትነት አልተማመነም ማለት ነው፡፡ ራሱ ያላመነበትን ጥናት ደግሞ እኛን ሊያሳምን መድከም አልነበረበትም፡፡ ከዕውቀት የጸዳ ባዶ ጭንቅላት፡፡

በዘረኝነት መንፈስ ካበዱ አይቀር እንደዚህ ነው፡፡ የምን ትዝብት፣ የምን ይሉኝታ፣ የምን ትምህርትና ዕውቀት፣ የምን ምናምን… ለያዘው ክርክር  ማሸነፊያ መስሎ የታየውንና አፉ ላይ  የመጣለትን ብቻ መዘላበድ ነው፡፡ እነዚህ አክራሪ ኦሮሞዎች ግዴላችሁም አክራሪ ትግሬዎችን ሊያስከነዱና የተፋነውን ሊያስናፍቁንም ነው መሰለኝ፡፡ ይሄው የፈረደበት አማራ “አንዱን ካላዩ አንዱን አይሰዩ” (አያመሰግኑ?) የሚለው “ወደው አይስቁ” ጋር ተዳምሮ በጣም ትክክል ነው፡፡ ለነገሩ ጅል አይሙት እንዲያጫውትም ይባላልና እንደዚያ ነው ነገሩ፡፡

እኔ በመሠረቱና እንደእውነቱም ከሆነ የአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ 29 በመቶ ሆነ 0.01 በመቶ ጉዳየ አይደለም፡፡ አንድን ቋንቋ ከተናጋሪው ማንነትና ምንነት ጋር በማያያዝ በሥነ ልቦና ደዌ ለማይቸገር ሰው ይህ ነገር ተራ ነው፡፡ አማርኛም ሆነ እንግሊዝኛ ወይም ኦሮምኛ መገልገያ መሣሪያ እንጂ እንደአክራሪ ብሔርተኞች እምነት በአንድ በዘር ሐረግና በደምም ሆነ በንክኪ በማይወረስ ተራ የመግባቢያ መሣሪያ ይህን ያህል በማያባራ አርማጌዴዖናዊ ጦርነት ውስጥ ተዘፍቆ ለያዥ ለገራዥ ማስቸገር የበሽታ እንጂ የጤንነት ምልክት አይደለም፡፡ እናም ችግሬ እሱ ሊሆን አይችልም፡፡ በዓለም ያለው ወደ ሰባት ሽህ ገደማ የሚገመተው ቋንቋ ሁሉ የኔ(ም) ነው – ኦሮምኛ ይቅርና፡፡

… ግን ግን ኦኤምኤን ራሱ ለምን በአማርኛ ይናገራል? ለ29 መቶኛ ሕዝብ ለመድረስ ይህን ያህል ለምን ተጨነቀ? ትግራይ ቲቪስ ለምን በአማርኛ ይናገራል? ዋሽንግተን ዲሲ ለምን አማርኛን አምስተኛው ኢፊሴየል ቋንቋ ያደርጋል? ጀርመንና ብዙ ያደጉ የአውሮፓና አሜሪካ ሀገራት ለምን በአማርኛ የከፍተኛ ትምህርት መርሐ ግብሮችን ይሰጣሉ? ሰሞኑን ደግሞ ቻይና ለምን አማርኛን በዲግሪ ደረጃ እንዲሰጥ ወሰነች? ወያኔዎችና ቱባ ቱባ የኦህዲድ ባለሥልጣኖች ለምን ልጆቻቸውን በአማርኛ ያሰለጥኗቸዋል? አሰለጥ የዘር ፖለቲከኞች ለራሳቸው የሚመርጡትን ነገር እንወክለዋለን ለሚሉት ወገን ለምን ይከለክላሉ? እነጃዋር አማርኛን ምናልባትም አማራ ከሚባለው በበለጠ ለምን ይራቀቁበታል? እነፀጋየና ሕዝቅኤል ለምን በሚጠሉት ቋንቋ በአማርኛ ይናገራሉ? የፌዴራል መንግሥት፣ ስብሰባዎችን በኦሮምኛ ወይም በእንግሊዝኛ ለምን አያደርግም? ፌዴራሊስት ተብዬዎቹ ለስብሰባም ሆነ ለሆነ ጉዳይ ሲገናኙ ለምን አማርኛን መርጠው ይጠቀማሉ? የየጁው ራስ አሊ፣ ትግሬው አፄ ዮሐንስ፣ አፄ ቴዎድሮስ፣ አፄ ምኒልክ፣ አፄ ኃይለ ሥላሤ፣ ኮ/ል መንግሥቱ፣ አፄ መለስ ዜናዊ … ሌሎችም ቀደምትና የቅርብ ጊዜ የኢትዮጵያ ገዢዎች አማርኛን የተገለገሉት የአማራ ሕዝብ እግራቸው ሥር ተደፍቶ “እባካችሁን ይህን ጉሮሮ የማይቧጥጥ፣ ድድ የማያሳብጥ፣ ከንፈር የማይጎረብጥ፣ ለጽሑፍና ለታሪክ ድርሳን የሚመች አማርኛ ቋንቋየን ተጠቀሙ!” ብሎ ለምኗቸው ይሆን?  ማን ያውቃል! እንደአሁኑ የአክራሪ ኦሮሞዎች መቅነዝነቀዝ ከሆነ በርግጥም ያስብላል – እባካችሁን እነዚህ ቂሎች ስለቋንቋና ማኅበረሰብ ምንነትና ዘፈቀዳዊ ግንኙነት እንዲያነቡ ምከሯቸው፡፡ 

ተቃራኒውን ልንገራችሁ ይልቁንስ፡- አማራነት በውድም በግድም የተለጠፈበትና ይህን ከኢትዮጵያዊነት ማዕረግ የወረደ ልጠፋ አምኖበትም ሆነ ሳያምንበት የተቀበለው ሕዝብ በጉልበቱ ተንበርክኮ “አማርኛ የሥራም ሆነ የጋራ ቋንቋ እንዳይሆንብን መንግሥት ዐዋጅ ያውጣልንና እኛንም ያሳርፈን” ብሎ ቢለምን አይሣካለትም፡፡ ምክንያቱም ተወደደም ተጠላ አማርኛ የ86 ነገዶች የጋራ መግባቢያ የሆነው በዐዋጅና በጦርነት ሳይሆን ለበርካታ ምዕተ ዓመታት በተደረገ የርስ በርስ መስተጋብርና ማኅበረሰብኣዊ ስምምነት ነው፡፡ ዛሬ ተነስተህ፣ “ሁሉም በጄ፣ ሁሉም በደጄ” ብለህ ወጧ እንዳማረላት ሴት ከአውሮፓ አሜሪካ እያሽቃነጥክ “የኔ ቋንቋ አገሩን ይግዛ” ብትልና በጠበንጃና በቀስት ሕዝብ ብታስፈጅ ያገኘኸውን ዕድል አበለሻሽተህ የታሪክ ተወቃሽ ትሆናለህ እንጂ እውነቱን ልንገርህ ምንም አታመጣም፡፡

ኧረ ግን ብርሃነ መስቀል አበበ ራሱ ስሙን ለምን አይቀይርምና “ፈይሣ ጉርሜሣ ሰኚ” አይባልም? ትግልን መጀመር የሚያምረው ከራስ ነዋ! ማን በዚህ ስም እንዲጠራ አስገደደው? … እነፀጋዬ ገ/መድኅን ዋቀዮ፣ እነፊታውራሪ ኃ/ጊዮርጊስ ዲነግዴ፣ እነጄኔ. ደምሴ ቡልቶ፣ እነጄኔ. ጃጋማ ኬሎ፣ እነጄኔ. ታዬ ባልኬር፣ እነሽመልስ ማነው እነአብዲሣ አጋ፣ እነበዓሉ ግርማ፣ እነጥላሁን ገሠሠ፣ እነጄኔ. መርዳሣ ሌሊሣ፣ እነለማ ጉያ፣ እነለማ ጉተማ፣ እነደበላ ዲንሣ፣ ስንቶቹን ጠርቼ (አማሮች ግን እነማናቸው በል? የትስ አሉ በሀገራችን ታሪክ? እ? ) … እነዚህ ሁሉ ኢትዮጵያውያን ከሌሎች ወገኖቻቸው ጋር ለዘመናት የገነቧትን ሀገር፣ ወፍ ዘራሾች ድንገት ተነስተው በ30 እና በ40 ዓመታት ውስጥ ያፈርሷታል ማለት ዘበት ነው፡፡ ሙከራው ግን ብዙ ጠባሳ አያሳድርም ማለት እንዳልሆነ በግልጽ እያየን ነው፡፡ ለማንኛውም “አባት ሳለ አጊጥ ጀምበር ሳለ ሩጥ” ነውና እነውድ አክራሪዎች ሆይ፣ አሁን አራት ኪሎ የተገሸረው ሰውዬ ሳያመልችጣሁ ቶሎ ቶሎ ሩጡ! በርቱ!!

Filed in: Amharic