>

እምቦጭን ከነአካቴው የሚያጠፋ መድሐኒት ሙሉ እውቅና አግኝቶ ወደ ስራ ተገባ!!! (ሔኖክ አስራት)

እምቦጭን ከነአካቴው የሚያጠፋ መድሐኒት ሙሉ እውቅና አግኝቶ ወደ ስራ ተገባ!!!

ሔኖክ አስራት

* የእምቦጭን አረም በሀገር በቀል እውቀት በመታገዝ ከነአካቴው ለማጥፋት የሚያስችል ፀረ-እምቦጭ መድሐኒት መገኘቱን የኢትዮጵያ ሊቃውንትና ምሁራን ማህበር ዛሬ በሰጠው መግለጫ አብስሯል።
* ይሄ በፈሳሽ መልክ የተዘጋጀ ፀረ እምቦጭ መድሐኒት በተረጨ በ 24 ሰአታት ውስጥ የአምቦጭ አረምን ለማክሰም ይችላል የተባለ ሲሆን በ 30 ቀናት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ያስወግደዋል ተብሏል።
መድሐኒቱ የተገኘው ስለ ዕፅዋት ከሚመራመረው ዕፀ ሕይወት የዕፅዋት ጥናትና ምርምር ማዕከል መሆኑን መግለጫውን የሰጠው የኢትዮጵያ ሊቃውንትና ምሁራን ማህበር ያስታወቀ ሲሆን መድሐኒቱን ወደ ተግባር አስገብቶ እምቦጭን በቀጣይ 3 አመታት ለማስወገድ ሕጋዊ ስምምነት ማድረጉን ገልጿል።
ፀረ እምቦጭ ዕፅዋቱን ያገኘው ማዕከል መስራች መሪ ጌታ በላይ አዳሙ ዕውቀቱን የቀሰሙት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክ ስር ከሚገኙ ጠበብት ሊቃውንት መሆኑን በዕለቱ ተናግረዋል።
ፀረ እምቦጭ መድሐኒቱ ኦርጋኒክ በመሆኑ በሰው ላይም በስነ ፍጥረት ላይም ምንም አይነት የቀጥታም ሆነ የጎንዮሽ ጉዳት አያስከትልም ብለዋል።
አረሙ ከዚህ በላይ ሳይስፋፋ በተፈለገው ፍጥነት ወደ ትግበራ ለመግባት ይረዳን ዘንድ ለምናደርጋቸው አውደ ጥናቶችና ተያያዥ ተግባራት በተለይ የመንግስት አካላትና የግል ባላሀብቶች እንዲሁም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የራሱን አስተዋፅኦ በማድረግ ከጎናችን እንዲቆም ጥሪ እናስተላልፋለን ሲል ማህበሩ መልዕክቱን አስተላልፏል።
ጣና ሀይቅ 3 ሺህ 672 ኪሎ ሜትር ስፋት የነበረው ሲሆን ወደ 3 ሺህ ኪ.ሜ ወርዷል። በእምቦጭ ምክንያት፤ የሀዋሳና የዝዋይ ሀይቅ ተደምሮ የሚያክለው የሀይቁ ክፍል ወይም 125 ሺህ 579 የእግር ኳስ መጫወቻ ሜዳዎችን የሚያክል የቦታ ስፋት ወደ የብስነት መቀየሩን መረጃዎች ያሳያሉ።
Filed in: Amharic