>

መተከል - ብአዴን - አምስት ሳንቲም ! (ሀብታሙ አያሌው)

መተከል – ብአዴን – አምስት ሳንቲም !

ሀብታሙ አያሌው

* እናትና ልጅን በቀስት ከሚያጣብቁ አውሬዎች (ዘላኖች) ጀርባ የማን አጀንዳ እየተተገበረ እንደሆነ ግልጽ ነው፤ መተከልን ከአማራ ማጽዳት ከዛም መሰልቀጥ…!
እነዚህ ትከሻቸው ሸክም የለመደ የብአዴን ጉዶች ለጊዜው ከነቤተሰቦቻቸው አዲስ አበባ እየተገማሸሩ በሞታችን መሳለቅ መርጠዋል።  ይህ ግብዝነት ግን ከንቱ ነው የ4 ኪሎ የብረት አጥር ህወሓትንም አልታደጋት።
ለማንኛውም ኦዴፓ (የኦሮሞ ብልፅግና)  የነደፈውን ቤንሻንጉልን ከአማራ ተወላጆች የማፅዳት ዘመቻ  የሚያቀላጥፉት ዘላኖች (ዘላን የሚለው ቃል ካነሰ አውሬዎች በሚል ይተካ)  ህፃንና አዛውንት ሳይለዩ ማረድ ግብራቸው የሆነ  ኦነጋውያን ሁሉንም አይነት መሳሪያ እንደተጠቀሙ ይመዝገብ። ከሜንጫ እስከ ገጀራ ከጥይት እስከ ቀስት፣ በእሳት ከማቃጠል በአውሬ እስከማስበላት . . . ሁሉንም።
ፓርክ ለመመረቅ በፖራሹት አስወርዶ የኋላ ዙር ጫማ ጥፊና  በተር ፍላይ ኪክ ያሳየን ኮማንዶ የተሰኘው የአብይ አህመድ ጉጅሌ አራት ኪሎ እየተቀለበ ቤንሻንጉል ላይ ለ5ኛ ጊዜ በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ወንጀል  የ89 ሰዎች ሕይወት ቀስት በወደረ ዘላንን ሲቀጠፍ ማስቆም የሚችል ኃይል ጠፍቶ እንዳልሆነ ለማስረዳት ቃላት አላባክንም።
አየህ !  ሻሸመኔ  የእርድ ፕሮግራሙን በሰላም አስጀምረው በሰላም ላጠናቀቁት ባህርዳር ላይ  ካባ የደረቡለትን ብአዴኖች  አቅፈህና ደግፈህ  ከዚህ በኋላ  አብይ ላይ ብትጮህ እንጥልህን ከማውረድ በቀር ፋይዳ እንደሌለው ብቻ ተረዳኝ ።   ሌላው እዳው ገብስ ነው።
እውነት እልሃለሁ መተከል ተወልዶ ካደገው ከደመቀ በላይ  አብይን ቀዳሚ ጠላት ማድረጉ ብዙ ፋይዳ የለውም። ገዱ አንዳርጋቸውም ሆነ ብናልፍ አንዷለም ከዚህ በኋላ ቢታጠቡት በማይነፃ ደም እጃቸው ተጨማልቋል፤ አገኘሁ ተሻገር የቀረህ ጀግና ካለ አድኖ እስኪገድል፣ ተመስገን ጥሩነህ የነ አስቻለው ደሴን መቃብር እስኪያቃጥል ልጠብቅ ካላልክ በቀር ብአዴን የሚባል ቡድን መንግስት ሆኖ እስከቀጠለ ድረስ መከራው በጥፍ ይጨምራል እንጂ አይቀልም።
የአማራ ህዝብ መጻኢ እድሉን የመበየን ኃላፊነት በእጁ ላይ ነው። ህዝብ ግን ታግሎ የሚያታግለው ቁርጠኛ መሪ ይፈልጋል።  እናም ቁጭት ላንገበገበህ የወዳጅ ምክር ልንገርህ  ወደ አይንህ የተጠጋች 5 ሳንቲም አለምን እንዳታይ የመጋረድ አቅም አላት።  ሳንቲሟን ወዲያ አሽቀንጥረህ ዓለምን ተመልከት።  ብአዴን የሚባሉትን አምስት ሳንቲሞች ለማሽቀንጠር ትጋ።  እስከሬን እየቆጠሩ ማልቀሱ እንዲበቃ የመጨሪሻ እንባህ ጎርፍ ሆኖ የብአዴንን ከፍተኛ አመራር ይጥረገው።
Filed in: Amharic