>
5:13 pm - Monday April 19, 8726

መሪውን አስሮ እቅዱን መስረቅ -  ልንቃወመው የሚገባ ነውረኛ የሌብነት ተግባር....!!! (ኤርሚያስ ለገሰ)

መሪውን አስሮ እቅዱን መስረቅ –  ልንቃወመው የሚገባ ነውረኛ የሌብነት ተግባር….!!!

ኤርሚያስ ለገሰ

የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ በህግ ከተቋቋመ እለት አንስቶ የተለያዩ የፓሊሲ ዶክመንቶች እያዘጋጀ እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገልጽ ነበር። ከእነዚህ ዶክመንቶች ውስጥ በአዲስ አበባ ህዝብ ሲመረጥ በአምስት አመታት ሊሰራቸው የሚፈልጋቸውን የቃል-ኪዳን (ማኒፌስቶ) ተግባራትን የሚዘረዝር ሰነድ ነበር።
በዚህ ማኒፌስቶ ላይ አስተያየት እንድሰጥበትና ማዳበሪያ ሀሳቦች እንዳቀርብ እድሉን አግኝቼ ነበር። በወቅቱ ይህንን ዶክመንት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ከተወያየን በኃላ ሁለት ስጋቶቼን ገልጬ ነበር።
፩: ጠቅላይ ሚኒስትሩ ” ግልጽ ጦርነት” በማለት ያስፈራሩትን ወደ ተግባር በመቀየር መሪዎቻችን ወደ ማሰር ይሸጋገራሉ።
፪: ባልደራስ በማኒፌስቶው የጠቀሰውን ቁምነገሮች በርብሮ በመውሰድ ከፊሉን ከምርጫ በፊት ብልጽግና በራሱ ይፈጽማል። ከፊሉን “ለተደጋፊ ተደማሪ” ፓርቲዎችና ሌሎች የማይታወቁ የሚፈበርካቸው ሲቪክ ተቋማት ይሰጣል የሚል ነበር።
እነሆ! ዛሬ ብራ መብረቁ የሆነ የህገ-መንግስት ቅቡልነት የዳሰሳ ጥናት ከአንድ ተቋም ሰማን። በማስከተል አዳነች አቤቤ ጠንካራ የኮሙዩኒቲ ፓሊስ እንደምታደራጅ ይፋ አደረገች። ዛሬ ደግሞ የሰላምና ደህንነት ምክር-ቤት ማቋቋሟን አዳመጥን።
እርግጥ መሪን አስሮ ሀሳቡን ሰርቆ በተበጣጠሰ መንገድ መፈፀም በኢህአዴግ (ብልጽግና) ደጃፍ አዲስ ባይሆንም ፤ ይሄን ነውረኛ የሌብነት ተግባር ማጋለጥ ያስፈልጋል።
 በመሆኑም ለዛሬው ባልደራስ ከስድስት ወር በፊት ባዘጋጀው የአዲስ አበባ ማኒፌስቶ( 2013-2017) ውስጥ በምክር ቤቱ የመክፈቻ ቀን እና በተከታታይ 100 ቀናት ሊከናወኑ ከታሰቡት ቁልፍ ተግባራት ውስጥ በረቂቅ የቀረበውን ከብዙ በጥቂቱ ላካፍላችሁ። አጠቃላይ ማኒፌስቶውና ዝርዝር ተግባራቱ ረቂቁ(መነሻ) ሀሳቡ በምክር-ቤቱ ተሻሽሎ ሲፀድቅ ለህዝብ ይፋ እንደሚሆን የባልደራስ የውጭ አመራሮች አጫውተውኛል።
አዲስ-አበባ-ግዛት-ትሆናለች!
አዲስአበቤነት-ይለመልማል!
Filed in: Amharic