>
5:13 pm - Saturday April 20, 3371

እዛም ቤት እሳት አለ...!!!   አለቃ ገብረሀና

እዛም ቤት እሳት አለ…!!!   አለቃ ገብረሀና

ሰዋሰው ዶትኮም
አለቃ ገብረሀና – ( 1814 – 1898 ዓ.ም.)

——————

አለቃ ገ/ሀና በ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩ ሊቅ ናቸው። የተወለዱት በወርሀ ኅዳር 1814 ዓ.ም ባሁኑ አጠራር በደቡብ ጎንደር ዞን፣ በፎገራ፣ ወረታ አከባቢ ነው። አባታቸው ደስታ ተገኘ፣ እናታቸው ደግሞ ው/ሮ መልካሜ ይልማ ይባላሉ። ብዙዎች አለቃ ገብረሀናን በዚህ ምድር በህይወት ያልተመላለሱ የምናብ ገጸባህሪ እንደሆኑ ያስባሉ። ይሁንና አለቃ በህይወት የነበሩ ሰው ለመሆናቸው ብዙ መረጃዎችና ማስረጃዎች አሉ። መሰለ ለማ ኃብተወልድ የተባሉ ጸሀፊ የአለቃ ገብረሀናን ህይወትና ስራዎች በዳሰሱበትና በተነተኑበት “ሊቁ አለቃ ገብረሀና ” በተሰኘች መጽሀፋቸው ላይ ይህን ይላሉ….
“የአለቃ ገብረሀናን ሕይወት ታሪክና ገድል እንደ ህያው ፍጡር ድርጊት አድርጎ መቀበል ለአብዛኞቹ ኢትዮጵያዊያንና አንዳንድ የታሪክ ጸሀፍት ችግር ነበር….”
እኝህ ጸሀፊ ይህን ይሉና ስለ አላቃ ገብረሀና ህያውነት ያስረዳሉ ያሏቸውን ማስረጃዎች ሲጠቅሱ የዋልዳው አስጋኸኝ ለአንቶን ዲአባዴ አጼ ቴዎድሮስ በአለቃ ተናደው እንደመቷቸውና ‘እኔ ወደማልገዛው ምድር ሂድ ።’ ብለው እንዳባረሯቸው ጠቅሰው የጻፉትን ደብዳቤ፣ በእንጦጦ ራጉኤል 125ኝእ ዓመት መታሰቢያ መጸሄት ላይ የአለቃ ገብረሀና ስም መጠቀሱን፣ የአላቃ ገብረሃና መቋሚያ፣ሸማ እንዲሁም ጸናጽል መገኘቱንና አራተኛ ትውልዳቸው ዛሬም ድረስ በጎንደር መኖሩን ያነሳሉ። ሌላው የአለቃን ህያውነት የሚያስረግጥ ማስረጃ የአለቃ ለማ ኃይሉ የቃል ምስክርነት ነው። አለቃ ለማ ለልጃቸው አብዬ መንግሥቱ ለማ በተረኩለትና መንግሥቱ “መጽሐፈ ትዝታ ዘአለቃ ለማ ኃይሉ ወልደታሪክ” ብለው ባሰናኙት መጽሐፍ ላይ ስለ አለቃ ገብረሀና ሲናገሩ…https://www.sewasew.com/p/አለቃ-ገብረሀና-(-1814-1898-ዓ-ም-)
*     *      *
“በጠማማ ጣሣ ሰባት ሰባት ነው”
በቀልደኝነታቸውና በዋዘኝነታቸው ስለሚታወቁት ስለ አለቃ ገብረሃና ብዙ ተወስቷል፡፡
አንዳንዴ እሳቸው ያላሉትም የእሳቸው ተደርጐ ይተረካል፡፡ ለማንኛውም የሳቸው ከተባሉት ጥቂቶቹን እንጥቀስ፡፡
አንድ ቀን አለቃ ወደ ገበያ ይሄዳሉ፤ አሉ፡፡
ገበያው ደርቷል፡፡ የአለቃን ተረበኛነት የሚያውቅና የሚወድ አንድ ተጨዋች ሰው ይመጣል፡፡
ሰውዬው እግሩ ገደድ ያለ ነው፡፡
አለቃን እንዳገኛቸው፤
“አለቃ እንደምን ዋሉ?” አላቸው፡፡
“ደህና ውለሃል ወዳጄ?” አሉ አለቃ፡፡
“ከየት እየመጡ ነው?”
“ሰው ሳስታርቅ ውዬ፣ የፍንጥር ምሣ በልተን ገና አሁን ተለያየን፡፡”
እግረ-ጠማማው ሰውዬ፣ አለቃ አፍ ላይ የተልባ ፍሬ ያያል፡፡ አለቃ ምሣ የበሉት በተልባ ወጥ መሆኑን በመገመት፤ ጥቂት ሊተርባቸው ፈልጐ፤
“ለመሆኑ ተልባ ስንት ስንት ዋለ፤ አለቃ?” አለ፡፡
አለቃም ወደ ሰውዬው እግር መልከት ብለው፤
“በጠማማ ጣሣ ሰባት ሰባት ነው” አሉት፡፡
*   *   *
“…. ምን ብንወዳት እወጥ ውስጥ አንጨምራትም?” 

አንድ ቀን ደግሞ፤ ጐጃም ውስጥ፣ አንድ ሰው ከወደ ሞጣ ሲመጣ አለቃ ያገኙታል፤ በእጁ በትር ይዟል፤
አለቃ – “እንደምን ዋልክ ወዳጄ?”
ሰውዬው – “ደህና እግዚሃር ይመስገን፡፡ ደህና ውለዋል አለቃ?”
አለቃ – “ደህና ነኝ፡፡ ከወዴት ትመጣለህ ወዳጄ?”
ሰውዬው – “ከምፃ” አላቸው…(“ጣ” የሚባለው “ፃ” አለው ማለት ነው)
አለቃ – “ምን ይዘሃል?”
ሰውዬው – “ድግፃ”…(ድግ “ጣ” የዛፍ ዓይነት ነው)
አለቃ – “በል መንገድ መትቶሃል፤ ምሣ እንብላ” አሉትና ተያይዘው ወደ አለቃ ቤት ሄዱ፡፡
ምሣ ቀርቦ እየበሉ ሳሉ፣ ሰውዬው ወጡ ጨው እንደሌለው ልብ ብሏል፡፡
ወደ አለቃ ቀና ብሎ፤
“ትንሽ ፀው ያስፈልጋል – ፀው አምጡ; አለ፡፡
ይሄኔ አለቃ፤
“አይ እንግዲህ! “ፀ”ን ምን ብንወዳት እወጥ ውስጥ አንጨምራትም?” አሉት፡፡
*   *   *
“….እዛም ቤት እሳት አለ.”
አለቃ በሚስታቸው በወይዘሮ ማዘንጊያ ላይ መሄድ ለምደው ኖሮ አንድ የገበያ ቀን ወይዘሮ ማዘንጊያ  ማልደው መውጣታቸውን ያዩት አለቃ ወደ ጓሮ ብቅ ብለው ምልክት ሲሰጡ የለመደች የጎረቤት ውሽሚት ልጇን አቅፋ ትመጣና አስተኝተውት ሁለቱ የፍቅር አለማቸውን እየቀጩ ሳይታወቃቸው ጊዜው ሄዶ ኖሮ ወይዘሮ ማዘንጊያ ድንገት ከተፍ ይላሉ ፤ ድምጻቸውን የሰማችው   የጐረቤት ውሽሚት በጓሮ በር እግሬ አውጭኝ ትላለች፤ ከተተራመሰው መደብ ጥግ ላይ የጎረቤታቸውን ህፃን ልጅ ጧ ያለ እንቅልፍ ተኝቶ ያዩት ወይዘሮ ማዘንጊያ ነገሩ ገብቷቸው ሳለ ምንም ሳይናገሩ ወደ ምድጃቸው በመሄድ እሳቱን ገለብለብ አድርገው ካቀጣጠለ በኋላ ያን ህጻን አንስተው በአስፈሪ ቁጣ  “አለቃ ልጨምረው?!?” ቢሏቸው አለቃም በማስተዛዘን ….
“ተይ ማዘንጊያዬ እዛም ቤት እሳት አለኮ!” ብለው ነገሩን አበረዱት።
*   *   *
ጥፋት ለማንም አይበጅም፡፡ ለጥፋት መቆም መጨራረስንና ውድመትን እንጂ የሚያመጣው ረብ – ያለው ነገር አይኖርም፡፡ ለረዥም ዘመን የኖረ ጐረቤትን ማጥቃትም ሆነ ማጥፋት ምላሹን መርሳትና የእርስ በርስ እልቂትን መደገስ ነው!
“የማ ቤት ጠፍቶ፣ የማ ሊለማ
የማ ቤት ጠፍቶ፣ የማ ሊበጅ
የአውሬ መፈንጫ፣ ይሆናል እንጅ”
የተባለው ለተራ ፉከራና ቀረርቶ እንዳልሆነ ትክክለኛ አዕምሮ ያለው ሚዛናዊ ሰው ልብ ይላል፡፡
ወትሮውንም ቢሆን፤
ለጥፋት የቆመ፤ ዐይኑ ያለጥፋት አያይም፡፡
የጐረቤቱ ዕድገትና ልማት አይጥመውም፡፡
“እኔ ዶሮ ሳረባ አይቶ፣ ጐረቤቴ ሸለ-ምጥማጥ ያረባል!” ይላል አበሻ፤ ምቀኛን ሲገልፀው፡፡
ልማትን ልፋት ለማድረግ፣ ለውጥን ነውጥ ለማድረግ መሻት ከንቱና እኩይ ተግባር መሆኑን ልብ ያለው፣ ልብ የሚለው፣ ማንም ጅል የማይስተው፣ ጉዳይ ነው፡፡
ሉዓላዊነቱንና ህልውናውን ቸል ብሎ ሲነካ ዝም የሚል፣
“ባለቤቱን ካልናቁ
አጥሩን አይነቀንቁ!” የሚለውን ምሣሌያዊ አነጋገር የማያውቅ ብቻ ነው!
አያሌ መንግሥታት ሁለት ዋና ነገሮችን ሲስቱ ለውድቀት ይዳረጋሉ፡- አንድም የዕብሪትና የንቀት፤ አንድም የድንቁርናና የአጓጉል ዕውቀት ሰለባ ሲሆኑ፡፡ የሁሉም ውጤት ድቀት ነው!
“ዐባይ ሞልቶ፣ ጣና ሞልቶ፣
ላጨኝ በደረቁ
እራሴን ሳያመኝ፣
ነደደኝ መናቁ!”…
(“መ” እና “ና” ይጠብቃል) የሚልን ህዝብ እሳቤ የማያውቅ የውጪ ኃይል ታሪክንም፣ ጂኦግራፊንም፣ ባህልንም የዘነጋ ነው፡፡
የውስጥን ችግር ለማስታገስ፣ ወደ ውጪ መተንፈስ የአብዛኛዎቹ የአፍሪካ መንግሥታት የፖለቲካ መላ ነው፡፡ ሆኖም የዘመነ – ብሉይ እንጂ የዘመነ – ሐዲስ ፖለቲካ አይሆንም፡፡ “አሮጌ ወይን በአዲስ ጋን” ነው፡፡ በሁሉም ረገድ ክፉና ደግ ያየች እንደኛ ያለች አገር፤ ከእነ ህዝቦቿ ህልውናዋን ለማስጠበቅ፣ ብልህነትን ከትዕግሥት፣ ዕውቀትን ከድፍረት አቅፋ የምትራመድ ታሪካዊ አገር ናትና፣ ዋና ማዕቀፏን ዲፕሎማሲያዊነቷን አድርጋ የምትጓዝ የጀግኖች ምድር ናት:: ባንድ ፊት ድህነትን፣ ባንድ ፊት ኮሮናን እየተዋጋች በጥኑ ልብ የምትቀጥል፤ አንድ አራሽ፣ አንድ ተኳሽ፣ አንድ ቀዳሽ ያሏት አገር ናትና ያሻችውን ሳትቀዳጅ፣ የጀመረችውን ዳር ሳታደርስ ከቶም ወደ ኋላ አትልም!
Filed in: Amharic